ሀገራዊ እሴቶቻችን በርካታ ናቸው። በብዛታቸው ልክም ጥበቃን እያደረጉልን ይገኛሉ። የማንነታችን መሠረትና መለያም በመሆን ዘመናትን እንድንሻገር ያደርጉናል። በትናንት መነጽር ሳይቀር ራሳችንን እንድናየው ያስችሉናል። ዘመናትንም መመልከቻ መነጽሮቻችን ናቸው። ‹‹ አይ ትናንት ምናልባት ተመልሶ ቢመጣ ›› ያስብሉናል።
ምክንያቱም ትናንት የባሕል ወረርሽኝ ሳይኖርብን በመቻቻል ነገሮችን አልፈናል። ትናንት ችግር ሲያጋጥመን ተደጋግፈን አሳልፈነዋል። ትናንት የወደቀ ስናይ ጎንበስ ብለን ማንሳት እንጂ እረግጥን መሄድን አናውቅም። ትናንት ለእኔ ሳይሆን ለእኛ ብቻ መለያችን ነው። ይህ የተገነባው ደግሞ በይሉኝታ ባሕላችን መሆኑን ማንም አይክደውም።
ሰው ምን ይለኛል ስንል ጎረቤት እናግዛለን፤ ከጎረቤት እንዳንለያይ የተቻለንን ሁሉ እናደርጋለን። በተለይም ከባሕሉ ላለማፈንገጥ የምናደርጋቸው ነገሮች ብዙ ናቸው። ይህ ደግሞ የሰዎችን ደስታና ኃዘን መካፈልን፤ ለሰዎች በችግራቸው ጊዜ መድረስን ያሰፋልናል። የአቅምን ያህል ማድረግንም ያበረታታልናል። ለራስ ደስታን መፍጠርንም ይጨምርልናል። ሰዎችን ማክበርም የተለየ ልምዳችን ይሆናል።
በይሉኝታ ሰበብ ለሰዎች መድረስን ልምዳችን እናደርጋለን፤ ለሌሎች ደስታም እንጨነቃለን። ሌሎችን እንድናስቀድም እንሆናለንም። ይህ ደግሞ በግል ሕይወታችን ጭምር ይጠቅመናል። ለአብነትም በሌሎች ሰዎች ዘንድ ያለን ተቀባይነትና ትኩረት ከፍተኛ ይሆናል። ሌሎች ስለእኛ እንዲያስቡ ያደርጋል። የውስጥ መረጋጋትንም ይሰጠናል። ከሆነው ሁሉ ደግሞ ያደግንበት ቤተሰብንና ማኅበረሰብን እንድናመሰግንም ያደርገናል። ከሁሉም በላይ ሀገር ወዳድ ዜጋ እንድንሆን የሚያስችለን ነው።
እንደሚታወቀው ማኅበረሰባችን በማንኛውም መንገድ ቢሆን በመረዳዳት፤ ያለንን ለሰዎች በማካፈልና “እሺ ባይነትን” እንደ መልካም ባሕሪያት አድርጎ ይወስደዋል። ይህ ደግሞ የበለጠ የሚጎለብተው ይሉኝታ ያለው ሰው ስንሆን ነው። የእኔ ብቻ የምንል አለመሆናችን ግለኝነትንና እምቢ ባይነታችንን ያርቅልናል።
ይሉኝታ ያለው ሰው የሃሳብ ልዩነቶችንና ግጭቶችን ጭምር የሚያረግብና በመልካም ባሕሪ የሚቃኝ ነው። በዚህም ከሰዎች የሚጠብቀው ምላሽ ምንም አይኖርም። ምላሹ በራሱ ሕይወት ላይ የሚመጣው ለውጥ እንደሆነ ያምናል። የይሉኝታን አረዳድን ግን መገንዘብ ያስፈልጋል። ይሉኝታ ለምናደርገው ነገር ከስሜት ይልቅ ምክንያታዊነትን ማስቀደምን ይጠይቃል። ለምንድን ነው ይህን ጉዳይ የምፈጽመው? ሰው ምንይለኛል ብዬ ስለፈራሁ? ወይስ ስለሚያስደስተኝ? ወይስ ኃላፊነት ስለሚሰማኝ? የሚሉ ነገሮችን መመለስ ይገባል።
ይሉኝታ በጥበብ መያዝንና መራመድንም ይፈልጋል። በተለይም አሁን ያለንበት ዘመን ላይ ተቀምጠን በቸልታ ከተጓዝንበት ብዙ ዋጋ ያስከፍለናል። ከዚያም አልፎ ቂመኛና በቀለኛ ያደርገናል። የምንተማመንበትን መልካምነት ያሳጣናል። ምክንያቱም ለሰው ብለን እንጂ ለመልካሙ ባሕላችን አስበን አይደለምና ያደረግነው። በዚህም በቀላሉ በአንዳንድ “አጥማጆች” እንያዛለን። መልካምነታችን በመጥፎ ይተረጎምና እንዳንነሳ ሆነን እንወድቃለን። ልባችን የሚራራለትና ሆዳችን የሚያባባው የሰዎች ሁኔታ ቀጥታ ውድቀታችን ይሆናል።
እንደ ርህራሄ ያሉ ጠንካራ ስሜቶች በጥንቃቄ መያዝ አለባቸው። ከምክንያታዊነት ጋር መተሳሰር ይገባቸዋል። ያ ካልሆነ ግን ከፍ ያለ ርህራሄ ስለሚያሳውረን ማስተዋልና ጥበብን ሳንይዝ ዘው ብለን እንድንገባ ያስገድዱናል። ይህ ሆነ ማለት ደግሞ ከይሉኝታ ልናገኝ የምንችለውን ጠቀሜታ ያሳጣናል። ሰውን አለማመን ጭምር እንዲጠናወተን ያደርገናል።
ይሉኝታ እንደሀገር ያለን ተጽዕኖ ፈጣሪ እሴታችን ነው። ትልልቆችን የምናከብርበት፤ ሰዎችን ለመርዳት ያለንን ጽኑ ፍላጎት የምናሳይበት፣ ለተለያዩ ችግሮች ምላሽ የምንሰጥበት፤ ከመልካም ባሕሪያችን በረከቶችን የምናፍስበት። እናም ይህንን ባሕላችንን የሚሸረሽረውን ማንኛውንም ነገር ከሕይወታችን ማስወገድ አለብን። ያ ካልሆነ ግን ይሉኝታ ከሕይወታችንና ከአካባቢያችን የራቀ አይደለምና ኑሯችንን ያመሰቃቅለዋል።
ሁላችንም በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ የይሉኝታ ስሜት እንዲሰማን ተደርገን ተቀርጸናል። በዚህም ሰው ስለእኛ የሚለው ነገር፤ ሰው ስለ እኛ የሚያስበው ነገር ያሳስበናል። ብዙ ጊዜ ማድረግ የምንፈልጋቸውን ነገሮች ሰዎች ምን ይሉኛል ብለን ፈርተን ሳናረጋቸው እንቀራለን። ይህ ደግሞ ከመጥፎ ነገር የሚጠብቀን መልካም እሴታችን ነው። ማለትም አነጋገራችን፣ አለባበሳችን፣ ድርጊቶቻችንና ውሳኔዎቻችን በሙሉ ሰው የሚለውን ነገር በመፍራት ተጽዕኖ ስር የወደቁ ናቸው። በዚህም በእነዚህ ነገሮቻችን መልካሙን ጎዳና ብቻ እንድንከተል እንሆናለን።
ለአብነት አንድ ጉዳይ እናንሳ። አንድ ጋዜጠኛ ወደ ሥራ ሲሄድ አለባበሱ የተሻለ የሚያደርገው መሆን ይኖርበታል። ከተዝረከረከ ሥራውም በዚያው ልክ እንደሚሆን ይታሰባል። ስለዚህም ያ እንዳይሆን ሲል ለሰው ብሎ ያለውን አጥቦና ጸድቶ ወደ ሥራው ይሰማራል። በተመሳሳይ አንድ በእድሜ ከእኛ ተለቅ ያለ ሰው አጠገባችን ካለ ንግግራችን፣ አቀማመጣችን ሁሉ ይቀየራል። ለዚያ ሰው ያለን አክብሮትም በሥራችን ይገለጣል። ይህ ደግሞ መልካምነትን ማብዛት እንደሆነ ማንም አይክደውም።
መታዘዛችን ውስጥ ብዙ የይሉኝታ ሀሳቦች አሉ። መታዘዛችን ውስጥ ብዙ የሚጠቀሙ የሚገለገሉ ሰዎች አሉ። ከመታዘዛችን ጀርባ ብዙ የሚድኑ፣ የሚፈወሱና የሚጽናኑ ሰዎች አሉ። ይሄ እንዳይሆን ግን ይሉኝታ ቢስ የሆኑ ሰዎች ይገጥሙናል። በተለይም ዛሬ ላይ ግለኝነት በበዛበት በዚህ ዘመን በቀላሉ የማንመክታቸው ብዙ ችግሮች እያጋጠሙን ይገኛሉ።
እንደእኔ እምነት የኢትዮጵያ ሕዝብ ምንም ጠባቂም ጠበቃም አያስፈልገውም። ባሕሉ በራሱ የሚያስተዳድረውና ሰውኛ ባሕሪ ያለው ሕዝብ ነው። በዚህ ባህሉ ደግሞ ችግሮቹን ይጋፈጣል፤ መፍትሔ እየሰጠም ይሄዳል። ሰዎችን ለማራመድ እንጂ ለመጣል የሚጣርም አይደለም።
የአንድ ሰው ምርጫ ቃላቶቹ እና ተግባሮቹ ብቻ ሳይሆኑ ሀሳቦቹ፣ ስሜቶቹና ልምዶቹም ጭምር ናቸው። እነዚህ ነገሮች ደግሞ በይሉኝታ ውስጥ በስፋት የሚታዩ ሲሆኑ፤ በራሱ ንቃተ-ሕሊና ውስጥ እንዲገለጥ የሚደረጉ ናቸው። እስከዛሬ ባለው ነባራዊ ሁኔታ ደግሞ በሕዝቡ ዘንድ ተገልጠዋል፤ መፍትሔ ሆነዋል የሚል ሀሳብ አለኝ።
አላዋቂ እና ለተግባራዊነታቸው የማይታመኑ ሰዎች ብዙ ጊዜ ይሉኝታ የሚለውን ከራሳቸው ጥቅምና ፍላጎት ጋር ያስተሳስሩታል። አስፈላጊውን ልምድ እንዲዳብርም መንስኤ ይሆናሉ። በጣም ምቹ እድሎች ባሉበት የሕይወት ሁኔታዎች ውስጥ ተቀምጦ እንኳን ግለኝነት እንዲሰማው ያደርጉታል። ይህ ደግሞ መከባበር እንዳይሰፍን በር የሚከፍት ነው። ለሰው ብለን የምናደርጋቸውን ነገሮች እንድንቀንስ ያስገድደናል። በአጠቃላይ ሰዋዊ ባሕሪያችንን ይነጥቀናል። አሁን ያለንበት ዘመንም በዚህ ሁኔታ የተቃኘ ይመስለኛል።
ሰዎች ብዙውን ጊዜ ቁሳዊ እና ቁሳዊ ያልሆኑ ጥቅሞች ያሳሷቸዋል። በአንድ ሰው ፍላጎት ውስጥ በቅርበት ተሳስረውም ስለሌሎች እንዳይጨነቁ ሆነዋል። ውሳኔዎችን ጭምር ስንመለከት ተገቢነት እንደሌላቸው ብናይም መቃወም እንዳንችል ሆነናል። ምክንያቱም ለሰው ብለን የምንጨነቅ አይደለንም። ይሉኝታ ቢስነታችን ተራራ ነክቷል።
የመደሰት ፍላጎት ፣ በሌሎች ኪሳራ የግል ጥቅምን ማጋበስ ፣ አሉታዊ ግብረመልሶች ፤ ወቀሳ መፈለግ ፣ ከሌሎች የመለያየት ስሜት ለአብዛኛዎቹ ሰዎች መመዘኛዎች ሆነው ሲቀርቡ ይሉኝታ ቦታ አይኖረውም። ይህ ደግሞ ተፈጥሯዊ ግንኙነትን ሳይቀር ይሰብራል። ዛሬ እያየን ያለውም ይህንኑ ነው። ግንኙነታችን ከእኔነት አይበልጥም። ስንደራጅ እንኳን የእኔ ወገን ካልን ሰነባብተናል። በዚህም በከባድ ራስ ወዳድነት ዝንባሌዎች እና ፍላጎቶች ውስጥ ወድቀናል።
ማን ሊያወጣን ይችላል ከተባለ መልሱ አንድና አንድ ነው። የቀደመ ባሕላችን መመለስ። ለዚህ ደግሞ ሁልጊዜ ሰዎችን መፍራት ወደ ልባችን ማምጣት ያስፈልገናል። በአክብሮት ውስጥ ያለን መልካም በረከት ማጤንና ለአዕምሯችን መንገር ይገባናል። ሁሉም ነገር ያልፋል። ፍጥረት ሁሉ ያልፋል። እኛ ሰዎችም ብንሆን እናልፋለን።
ከዛሬ ሀያ ሠላሳና አርባ ዓመታቶች በኋላ ብዙዎቻችን ምድር ላይ በሕይወት አንኖርም። ዛሬ ላይ ግን የምናገለግለው ሀሳብና ፈቃድ አለን ማለት ይጠበቅብናል። ያ ደግሞ የይሉኝታ ሰው በመሆን ሲሆን፤ ሁሉም በተሰጠው መክሊት የሚያተርፍበትን መንገድ ያሳየናልና እንጠቀምበት።
ክብረ ነገሥት
አዲስ ዘመን መጋቢት 6 ቀን 2015 ኣ.ም