በሽግግር ወቅት አገር ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ይፈታተኗታል።ግጭት፣ አለመግባባት፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰት፣ ሙስናና አለመስከን ተደራርበው ዜጎችን እረፍት ይነሱታል። የጠራው እስኪሰክን፣ የጎደለው እስኪሞላ፣ የበደለው እስኪክስና እውነት ከፍትሕ ጋር እስኪታረቅ ብዙ ውጥንቅጦች ዙሪያዋን ይከቧታል።
“ግርግር ለሌባ ይመቻል” እንዲሉ በዚህ መሐል እዚህም እዚያም ግጭትና ዝርፊያን ምግባራቸው ያደረጉ ቡድኖች አጋጣሚውን መጠቀማቸው የማይቀር ይሆናል። ወንጀላቸውን ለመሸሸግ እላይ እታች የሚሉ ግለሰቦችም እንደዛው።
ኢትዮጵያ ላለፉት አምስትና ከዚያ በላይ ዓመታት ሀገርን አደጋ ላይ ጥለው የነበሩ አለመግባባቶችን አስተናግዳለች። ሉዓላዊነትን ፈተና ውስጥ የከተቱ አለመግባባቶች ተከስተዋል። በልዩ ልዩ አካባቢዎች ግጭቶች ተከስተው ዜጎች ለሞት፣ ለመፈናቀል እና ቤት ንብረታቸውን እስከማጣት ደርሰዋል።
በሰሜኑ ክፍል ለሁለት ዓመታት ያህል የዘለቀው ጦርነት አያሌ ዜጎችን የምድር ከርስ ውስጥ ከመክተት አልፎ በምጣኔ ሃብት፣ ማኅበራዊ ጉስቁልናና ለከፋ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ምክንያት ሆኖ አልፏል። ከዚያ ባለፈ ከታሪክ፣ ከወሰን፣ ከቆየ ቁስል፣ ከሕግ የበላይነት፣ ከጋራ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ወዘተርፈ ጋር በተያያዘ ሰፊ የአመለካከት ልዩነቶች የተስተናገዱበትና ሀገርን በስጋት እንደ ቆዳ የወጠሩበት ወቅት ነው።
ከላይ ካነሳነው ርዕሰ ጉዳይ ጋር ተያይዞ መንግሥት በሁሉም የኢትዮጵያ ክፍሎች የተከሰቱ አለመግባባቶች፣ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች፣ የቆየ ቁርሾና በዘመን ሂደት ውስጥ የተከሰቱ ልዩነቶችን በሰከነ መንገድ ለመፍታት ሁነኛው መፍትሔ “የሽግግር ፍትሕ” መሆኑን አምኖ ለመፍትሔው እየሠራ መሆኑንና ቁርጠኝነቱን እያሳየ እንደሚገኝ በተደጋጋሚ እየገለፀ ይገኛል።
በዋናነት በኢትዮጵያም ሆነ በመሰል ሀገራት ከግጭቶች በኋላ ሰላማዊ ሁኔታዎችን ለመፈጠር ሲሞከር ትልቅ ርዕሰ-ጉዳይ ሆኖ እንደ ዘላቂ የግጭት ማቆሚያ መንገድ የሚወሰደው “ያጋጠሙ የመብት ጥሰቶች እና ወንጀሎች በምን መልኩ ምላሽ ይሰጣቸው?” የሚለው ጉዳይ ነው። በዓለም አቀፍ ደረጃ ለዘመናት ሲከሰት በቆዩ አለመግባባቶች ውስጥ ይህ ጉዳይ ዋንኛ የውይይት ርዕስ ነው። ምሑራንን እና የፖለቲካ ቡድኖችን አተካራ ውስጥ የሚከተው አጀንዳም ይሄው ነው።
የጨቋኝ ተጨቋኝ ትርክት በተንሰራፋበት፣ ዜጎች ላይ ከፍተኛ የሞራልና የምጣኔ ሃብት ድቀት በተፈጠረበት፣ ሰፊ የአመለካከት ክፍተት ባለበት እና ፅንፍ የያዙና የማይታረቁ የሚመስሉ ሃሳቦች በበዙበት የሽግግር ወቅት “እውነትና ፍትሕን” አዛምዶ የሚይዝ፣ በተለያየ ጎራ የሚገኙ ቡድኖችን በተሻለ መልኩ አስታርቆ ለሀገርና ለዜጎች ደህንነት ሲባል በአንድ ዓላማ የሚያሰልፍ ሁነኛ መፍትሔ “የሽግግር ፍትሕ” እንደሆነ በብዙ የፖለቲካ ልሂቃንና ምሑራን ይታመናል።
ለዚህም ይመስላል ኢትዮጵያ አሁን የገጠማትን እንቅፋት በብልሃት ለማሸነፍና ወደ ሰከነውና ወደ ተረጋጋው ሐዲድ ውስጥ ለመግባት መንግሥትን በበላይነት እየመራ የሚገኘው ብልጽግና ፓርቲ፣ ተፎካካሪ ፓርቲዎችና ልሂቃን በጋራ እየሠሩ የሚገኙት። ለመሆኑ ይህ አካሄድ የትኛውን መጨረሻ ያሳየን ይሆን?
ጉዳዩን ከስር መሠረቱ ለማጥራት እንዲያስችለንና ፅንሰ-ሀሳቡን መለየት እንድንችል በቅድሚያ “የሽግግር ፍትሕ”ን ምንነትን መረዳት ይኖርብናል።
“የሽግግር ወቅት ፍትሕ አስከፊ ግጭት፣ ጭቆና እና የመብት ጥሰትን ተከትሎ ተጠያቂነት፣ ፍትሕ እና እርቅን በማረጋገጥ ዘላቂ ሰላም የሚፍጥሩ ሥራዎችን የሚያጠቃልል ሂደት” መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከፍተኛ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ያሰፍራል።
አንዳንድ ሰዎች ተጠያቂነት የሚያስገኘው ፍትሕ የተሻለ ሰላም ያመጣል ሲሉ፣ ሌሎች ደግሞ የሽግግር ወቅት ፍትሕን እንደ አማራጭ ያቀርባሉ። ኢትዮጵያ ውስጥ እንዳለው አለመግባባት ለመሰሉ ጉዳዮችና በልዩ ልዩ ዓለማችን ላይ የሚከሰቱ ግጭቶች የተሻለው አማራጭ የሽግግር ፍትሕ እንደሆነ ይታመናል።
የሚከተሉት ጉዳዮች ትኩረት ከተሰጣቸውና በአግባቡ ተግባራዊ የሚደረጉ ከሆነ ውጤቱ ያማረና ኢትዮጵያን ወደምንፈልገው የሰላም፣ የእድገት፣ የትብብርና አንድነት መንገድ እንደሚወስዳት ማረጋገጥ እንችላለን። ለዚህ ደግሞ የሽግግር ወቅት ፍትሕ ዓላማዎችን መገንዘብ ይኖርብናል።
የመጀመሪያው “እውነትን ፈልጎ ማወቅና በዚያ ዙሪያ መተማመን ላይ መድረስ ነው” በመሆኑም ኢትዮጵያ ውስጥ እስከዛሬ ድረስ ለተከሰቱ ችግሮች፣ ለደረሱ ጥፋቶች እውነተኛውን መንስኤና ተጠያቂነት ማረጋገጥ ያስፈልጋል። ይህንን ማድረግ ስንችልና በጠረጴዛው ላይ ለማምጣት ፍቃደኛ ስንሆን ለመፍትሔው አንድ እርምጃ ወደ ፊት እንደሄድን መገንዘብ እንችላለን።
ሁለተኛውና ዋንኛው ጉዳይ ደግሞ “የተጎዱ ሰዎችን መልሶ ማቋቋም ነው” በኢትዮጵያ ውስጥ ከጫፍ እስከጫፍ ባሉ በሮች በተለያዩ ጊዜያት በሚከሰቱ ግጭቶች ምክንያት ዜጎች ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል። ሃብታቸው ወድሟል። የሞራል ውድቀት ደርሶባቸዋል። ለስነ ልቦና ችግር ተዳርገዋል። ይህንን መገንዘብ ያስፈልጋል። ከሁሉም በላይ እከሌ ከእከሌ ሳንል ተጎጂዎችን መካስ ይኖርብናል። ይህንን ስናደርግ በእርግጥም የሽግግር ፍትሕ ተግባራዊ እንደሆነ ማረጋገጥ እንችላለን።
ሦስተኛውና መሠረታዊ ጉዳይ “የወንጀል ተጠያቂነት” ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ የደረሱ ከፍተኛ ጥፋቶች፤ለደረሰው ንፁሕ የሰው ሕይወት መጥፋት፣ ለንብረት ውድመት ባለቤት እንዳለው ማመን ይገባናል። ግጭት ጠማቂ የነበሩ አካላት ኃላፊነት ወስደው ተጠያቂ ሊሆኑ ፍትሕ መድረሻዋን እንድታገኝ ማድረግ ከቀዳሚ ሥራዎች ውስጥ መግባት ይኖርበታል። አጥፊው ሲጠየቅ በቀጣይ መሰል ተግባሮች ላይ ለመሳተፍ እጁን የሚሰድ ትምህርት የሚወስድበት መልካም አጋጣሚ ይፈጠራል።
የገፈቱ ቀማሽ የሆኑ ዜጎችም “ፍትሕ” እንዳለ እንዲያምኑና በሚመሠረተው ሥርዓት ላይ መተማመንን እንዲያሳድሩ በር ይከፍታል። በጋራ ዳግም ያዘመመውን ምሰሶ መልሶ ለማቆም ይህ እርምጃ በእጅጉ አስፈላጊ ነው። ይህም ሲሆን ሌላኛዎቹ የሽግግር ፍትሕ መሠረታውያን ተሟሉ ማለት ያስችለናል።
አራተኛውና መሠረታዊው የሽግግር ፍትሕ ዓላማ “ሕግ፣ ፖሊሲ” ጨምሮ መሰል ለሀገር ግንባታና ዘላቂ ሰላም እንቅፋት የሆኑ የአሠራር ሥርዓቶችን ለማሻሻል ቁርጠኝነት ማሳየት ነው። ዜጎች በጋራ በአንድ አገር ጥላ ስር እንዲኖሩ ሁሉም የተስማሙበት የሕግ ማዕቀፎች ሊኖራቸው ይገባል።
አንዱን የእናት ልጅ ሌላውን የእንጀራ ልጅ የሚያደርግ ሥርዓት፣ ሕግ፣ ሕገመንግሥትም ሆነ ማንኛውን ማዕቀፍ መሻሻል የጋራ መግባባት ላይ መምጣት ይኖርበታል። ለዚህ ደግሞ ውይይት ቀዳሚውን ድርሻ ይወስዳል። ኢትዮጵያንና ዜጎቿን ወደፊት አላራምድ ያለና ቀፍድዶ የያዘ ሕግ ካለ በሰከነ ውይይት ሊታይና ዳር ሊይዝ የግድ ነው። ይህን ማድረግ ስንችል መንግሥትም ሆነ ምሑራን እየደከሙለት የሚገኘው የሽግግር ፍትሕ ፈር እንዲይዝ ትልቁን መደላድሉን እንፈጥራለን።
ምሑራን ሁለት ዓይነት የሽግግር ወቅት ፍትሕ እንዳለ ይናገራሉ። የመጀመሪያው የሽግግር ሂደቱ የወንጀል ክስ ላይ ብቻ አተኩሮ እንዲሄድ የሚያደርግ ነው። ይህንን በእኛ ሀገር ነባራዊ ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ የሚፈትኑ አያሌ ጉዳዮች መኖራቸው እሙን ነው። ምክንያቱ ደግሞ በብሔርና በጎጥ ለዘመናት ለመከፋፈልና በዚያ ጥላ ውስጥም ተሸሽጎ ከተጠያቂነት ለማምለጥ የሚደረጉ ሙከራዎች አሉ።
ይህ ተግባራዊነቱንና ውጤታማነቱን አደጋ ውስጥ የሚጥል ነው። አንድ የፖለቲካ ቡድን ወይም ግለሰብ ላይ ክስ መሥርቶ ተጠያቂ ለማድረግ ጥረት ቢደረግ በቀጥታ አንዱን ብሔር አሊያም ጎጥ ለማጥቃት እንደተሠራ ደባና ሴራ የማይወሰድበት ምክንያት ስለማይኖር በከፍተኛ ጥንቃቄ ሊታይ ይገባዋል።
ሌላው የሽግግር ሂደት ውስጥ የሚካተተውና ሁለተኛው የፍትሕ አይነት ምንም አይነት “ክስ እንዳይመሠረት፤ አጥፊዎቹ እንዲለዩና ጥፋታቸውን አምነው ይቅርታ እንዲጠይቁ” የሚያደርግ አካሄድና የሽግግር ፍትሕ አይነት ነው። ይህም አካሄድ የራሱ የሆኑ ክፍተቶች ያሉበት ቢመስልም በመጠኑም ቢሆን ጉዳት የደረሰባቸው አካላት ሕመማቸውና የደረሰባቸው የውስጥ ቁስለት እውቅና እንዲያገኝ የሚያደርግ በመሆኑ በብዙዎች ዘንድ ተቀባይነት ያለው ነው።
ሆኖም ግን የማይታለፍ ግፍ የሠሩ፣ የሕዝብን ሃብት ዘርፈው ለግል ዓላማቸው ያዋሉ፣ በከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ውስጥ እጃቸው ያለበት ግለሰቦችም ይሁን ቡድኖችን የማምለጫ ቀዳዳ የሚሰጥ ክፍተት ስላለው ሙሉ ለሙሉ ውጤታማ ነው ማለት ያዳግታል። ይሁን እንጂ ይህ ተግባራዊ ባለመሆኑ ከሚደርስ ቀጣይ ጥፋት ይልቅ ለሀገር መረጋጋትና ሰላም መስፈን በሚኖረው መፍትሔ ብንመርጠው የሚበጅ ነው።
ማጠቃለያ
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የተለያዩ ሀገራት የሽግግር ወቅት ፍትሕን ተግባራዊ አድርገዋል። ከእነዚህ ውስጥ ሩዋንዳ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ዩጎዝላቪያ እና ቺሊ ይገኙበታል። የሩዋንዳው የዘር ፍጅት በሽግግር ወቅት ፍትሕ መቋጨቱን ሁላችንም የምናስታውሰው ነው። በዚህ ሂደት ውስጥ ተበዳዮች በደላቸው እንዲታወቅ ተደርጓል።
አጥፊዎችም ለፍርድ ቀርበዋል። ጉዳዩም ለማስተማሪያነት በሙዚየም ጭምር ተቀምጧል። በፊልም በታሪክ መጽሐፍት ጭምር ለሰው ልጆች መማሪያ ነው። ሁላችንም አስከፊ ስለሆኑ የሰብዓዊ ጥሰቶች ምሳሌ እያደረግን ይህን መሰል ጉዳት እንዳይደገም መቀጣጫ እያደረግነው ነው።
የሽግግር ፍትሕ ሂደትን ስናነሳ ደቡብ አፍሪካም ተመሳሳይ እርምጃ ወስዳ እንደነበር ያስታውሰናል። በአፓርታይድ ሥርዓት ብዙ ቁስል ያስተናገደችው ይህቺ ሀገር እንደ ሀገር ምልክት በምታያቸው ኔልሰን ማንዴላ (ማዲባ) መሪነት ዘመናት ያቆሰላትን ችግር መፍትሔ አበጅታለታለች።
ብዙ ጥያቄዎች እና ቅሬታዎች ቢነሱበትም የአፓርታይድ ሥርዓት የተቋጨው በእውነት አፈላላጊ እና የእርቅ ኮሚሽን ነው። በዩጎዝላቪያም አጥፊዎች በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት የቀረቡበትን ሁኔታ ስናስታውስ፣ ይህ አካሄድ ወደ ሀገራችን ነባራዊ ሁኔታ መምጣቱን እንድናበረታታ ይገፋፋናል፤ “የሽግግር ፍትሕ እውን ሲሆን የደፈረሰው ይጠራ ይሆን?” ብለን እንድንጠይቅም ያስገድደናል።
ዳግም ከበደ
አዲስ ዘመን መጋቢት 5 ቀን 2015 ዓ.ም