መንግስት ከስንዴ ኤክስፖርቱ ጎን ለጎንም አጉራ ዘለል የሆነው፤ በዘላቂነት መዋቅራዊና ተቋማዊ ችግር የሚስተዋልበትን የግብይት ስርዓት በማያዳግም ሁኔታ መፍታት ይጠበቅበታል በስንዴ ምርት ላይ የመጣው እጅን በአፍ የሚያስጭን እምርታም በልኩ እውቅና ሊሰጠው ፤ አንድምታውንም ሰፋ አድርጎ መመልከት ይገባል።
ሉዓላዊነቷንና ነጻነቷን ጠብቃ ሳታስደፍር የኖረች ጥንታዊት ኢትዮጵያ። ቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ አፍሪካዊት ሀገር። እስካፍንጫው የታጠቀን ቅኝ ገዢን ከአንድም ሁለት ጊዜ ድል ያደረገች። በጸረ ቅኝ ግዛት ትግሉ ቀንዲል የሆነች። የፓን አፍሪካኒዝምና የብላክ ኮንሽየስ ዋልታና ማገር ፤ የራሷ ፊደልና የዘመን አቆጣጠር ያላት ፤ የሚሉ እውነቶች ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት በተነሱ ቁጥር አብረው የሚወሱ ቢሆንም ድህነቷ ፣ ኋላ ቀርነቷና በምግብ እህል ራሷን አለመቻሏና ተመጽዋችነቷ ጋርዶባት ፤ ጥላውንና አዚሙን ጥሎባት፤ አንጸባራቂ ገጽታዋን አጠልሽቶባት ይገኛል።
ድርቅና ርሀብ በተነሳ ቁጥር ስሟ አብሮ ይነሳል። በመዝገበ ቃላት ላይም ሆነ በሌላ መጽሐፍ ላይ የርሀብ ምሳሌ ሆና ስትጠቅስ ማንበብ ምን ያህል ቅስም ሰባሪና አንገት አስደፊ እንደሆነ ለኢትዮጵያውያን መንገር ለቀባሪ እንደማርዳት ነው። ተረጅነትና ተመጽዋችነት ሀገር ፊት ላይ ያለ አሸማቃቂ ለምጽ ነው። አይደብቁት አይሸግጉት ነገር ፊት ላይ ያለ የሀገር ለምጽ ነው።
የቦረናን ድርቅና ርሀብ ልብ ይሏል። ቢያንስ ላለፉት 50 አመታት ይህ ማንነቷ ኢትዮጵያንም ሆነ ዜጎቿን በሄዱበት እንደ ጥላ ሲከተል ኖሯል። ለለውጡ መንግስት ምስጋና ይግባውና በዓለም አደባባይ በኩራት ደረታችንን ነፍተን ፣ አንገታችንን ቀና አድርገን እንዳንራመድ ቀይዶ ይዞን የነበረው የተመጽዋችነት ሰንሰለት ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመበጣጠስ ከጫፍ ደርሰናል።
ባለፉት ጥቂት አመታት የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ፣ የኩታ ገጠም ግብርና ፣ የበጋ ስንዴ ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ፤ የሜካናይዜሽን ግብርና ፤ የህዳሴው 3ኛ የውሃ ሙሊትና 2ኛው ተርባይን ኃይል ማመንጨት መጀመር ፣ ወዘተረፈ. የሀገራችንን ተስፋ ከወዲሁ እያለመለመ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የዱግዳና ቦራ ወረዳዎችን የመኸር የስንዴ ኩታ ገጠም እርሻን በጎበኙበት ወቅት ፤ በያዝነው አዲሱ ዓመት ስንዴን ለውጭ ሀገር ገበያ ለማቅረብ የተያዘው ግብ እጅግ ተስፋ የሚሰጥ ደረጃ ላይ ይገኛል ማለት ትልቅ ሀገራዊ ብስራት ነበር። እንዳሉት 38 ሚሊየን ኩንታል ወደ ውጭ የሚያስችል አቅም ተፈጥሯል። በመጀመሪያ ዙር ከሚላከው 3 ሚሊየን የተወሰነው መላክ ተጀምሯል። እንደ አለመታደል ሚዲያዎቻችን በነጠላ ዜና አለፉት እንጂ በሰበር ሊዘገብ ፤ ሆኖም ዛሬም አልረፈደምና ተገቢውን የሚዲያ ሽፋን ሊያገኝና እንደ ሀገር ሊከበር/ሴሌብሬት/ሊደረግ ይገባል።
ወደ ጠቅላይ ሚንስትሩ ንግግር ስመለስ ፤ ኢትዮጵያውያን በዚህ ልክ መስራታችን ብሔራዊ ክብራችን እና የሀገር ሉዓላዊነታችንን ከማስከበር ጋር በቀጥታ የተገናኘ መሆኑን ፤ የመንግስትም ዋነኛ ትኩረት ከዚህ በፊት የነበረውን ርሀብ የተፈጥሮ ሀብታችንና ያለንን ጉልበት በአግባቡ በመጠቀም ስንዴን ከሀገር ቤት ፍጆታ አልፈን ወደ ውጭ ወደ መላክ መቀየር እንደሆነ ፤ መሰደድን በሀገር ወደ መስራት መቀየር ፤ የመሬት መራቆትን ወደማልበስ ለማሸጋገር የመንግስት የትኩረት አቅጣጫ ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን የምስራች ብለዋል። ባለፈው ዓመት በበጋ መስኖ 600ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት 26 ሚሊዮን ኩንታል መመረቱን ፤ በአጠቃላይ የበልግን ሳይጨምር በመኸር 110 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ተመርቷል።
ይህ ታሪካዊ እመርታ የሀገራችንን ገጽታ ፣ ግብርናዊ ስሪትና የስነ ልቡና ውቅር የሚቀይር ወሳኝ መታጠፊያ/ክሪቲካል ጃንክቸር/ ነው። ለሌሎችም ሁለንተናዊ ኢኮኖሚያዊ ብልጽግና መስፈንጠሪያ ሆኖ ስለሚያገለግል በቀላሉ የሚታይ ስኬት አይደለም። በአጠቃላይ ሀገራችን ግብርናና አረንጓዴ ኢኮኖሚ የሰጠችው ትኩረት ፤ በአለማችን ላይ ከተከሰተው የአየር ጠባይ ለውጥ ፤ የዓለም ሕዝብ ቁጥር በእጅጉ እያሻቀበ በመምጣቱ የግብርና ምርት ውጤቶች በእጅጉ እየተፈለጉ ባለበት ወቅት ጋር መገጣጠሙ አለማቀፍ አንድምታ እንዲኖረው አድርጓል።
ያለንበት ዘመንም ሆነ መጪው ጊዜ ለግብርና ምቹ ነው። ለዚህ የሚበጅ የግብርና መሠረተ ልማት ግንባታ ላይ ትኩረት እንደተሰጠው ሁሉ ፤ ይሄን የሚመጥን የግብይት ስርዓት ፣ ተጠያቂነትና የሕግ የበላይነት በንግዱ ዘርፍ ተግባራዊ ካልተደረገ ምርትና ምርታማነት የቱንም ያህል ቢጨምር ገበያውን ማረጋጋትና ሸማቹንም አምራቹንም ተጠቃሚ ማድረግ አይቻልም። በዚያ ሰሞን በሲሚንቶ ሰሞኑን ደግሞ በስንዴ ግብይቱ የምናየው ችግር ለዚህ ጥሩ አብነት ነው። ስለዚህ አበክሮ ጎን ለጎን ሊሰራ ይገባል።
በተደጋጋሚ እንደምለው መጪው ዘመን ለግብርና ኢኮኖሚው ብሩህ እንደሆን እየተለፈፈ ይገኛል። አፍሪካም ሆነች ሀገራችን የሰፋፊ የእርሻ መሬቶች ፣ የተፈጥሮ ሀብት፣ የሰፊ ገበያ፣ በመልማት ያለ የሰው ኃይል፣ …፤ እምቅ አቅም potential ያላቸው መሆናቸው አይን ማረፊያ አድርጓቸዋል። እ.አ.አ በ2050 የዓለም ሕዝብ ቁጥር 10 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ ተተንብዮል።
የቻይናና የሕንድ ኢኮኖሚ እድገትን ተከትሎ የመሸመት አቅም መጎልበት ጋር ተያይዞ የሚያሻቅበው የምግብ ሸቀጦችን ፍላጎትን ለማርካት፤ በአመት ከ100 ትሪሊዮን ዶላር በላይ የሚያገላብጠው ግብርና የዓለም ኢኮኖሚ መሪነትን በቅርብ ከኢንፎርሜሽን ኮሙዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ይረከባል ተብሎ ስለሚጠበቅ፤ ትኩረቱ ባልታረሰው የአፍሪካ ድንግል መሬት ላይ መሆኑ ዘመኑን ይዋጃል። አገራችን ለግብርናውና ለአረንጓዴ አሻራ የሰጠችው ትኩረት ትክክለኛና ስትራቴጂካዊ ውሳኔ ነው።
የዓለም ሕዝብ ቁጥር እድገት አሁን ከሚገኝበት ሰባት ነጥብ አምስት ቢሊዮን፤ በክፍለ ዘመኑ መጨረሻ 11 ቢሊዮን ይደርሳል ተብሎ መተንበዩ፤ በዓለም በተለይ በቻይና፣ በሕንድና በሌሎች ታዳጊ አገራት እየተመዘገበ ካለው ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ጋር የምግብ ፍላጎት እጅግ ጨምሯል። እድገቱን ተከትሎ የመግዛት አቅም ከፍ በማለቱ እና የመጣው የአመጋገብ ለውጥ ፍላጎቱን አንሮታል። ባለፉት 20 እና 30 አመታት በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ቻይናውያን፣ ሕንዳውያን፣ ብራዚላውያን ፣ ኢንዶኔዣውያን፣ ማሌዣውያን፣ ወዘተረፈ ከድህነት ወደ መካከለኛ ገቢ ማደጋቸው በግብርና ውጤቶች ፍላጎት ላይ መሠረታዊ ለውጥ አምጥቷል።
በተቃራኒው የሚታረስ መሬትና የውሃ እጥረት እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥ በአናቱ ተጨምሮ ከአመት አመት ፍላጎቱን ማሟላት አዳጋች እያደረገው መጥቷል። የዓለም ሙቀት መጨመርና የደኖች መጨፍጨፍ፤ የአፈር መሸርሸርንና የመሬት መራቆት፣ በርሃማነት፣ ድርቅ፣ ሰደድ እሳት፣ ጎርፍ የግብርናውን ክፍለ ኢኮኖሚውን እያሽመደመደው ነው። በዚህ የተነሳ ፍላጎቱንና አቅርቦቱን ማጣጣም ከጊዜ ወደ ጊዜ አዳጋች እየሆነ መጥቷል። እንደ ኮቪድ 19 ያለ የተፈጥሮ አደጋ ሲከሰት ደግሞ ችግሩ ክፉኛ ይባባሳል።
የዓለም የምግብና የእርሻ ድርጅት ቀደም ባለ ጊዜ ይፋ እንዳደረገው ከወረርሽኙ ጋር በተያያዘ 265 ሚሊዮን ሕዝብ ለከፋ የምግብ እህል እጥረት ተዳርጓል። ከባድ ውሽንፍር፣ የጎርፍ መጥለቅለቅ፣ ድርቅ፣ የመሬት መንቀጥቀጥ ዓይነት የተፈጥሮ አደጋዎች በተከሰቱ ቁጥር የምግብ እህል እጥረት ከፍ ሲልም ርሀብ ይከሰታል። በመላው ዓለም አንድ ቢሊዮን ሕዝብ በምግብ እጥረት ሳቢያ ለተለያዩ የጤና እክሎች ተዳርጓል።
ወደ አገራችን ስንመጣ 47 በመቶ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን የከፋ የምግብ እጥረት እንዳለበት መረጃዎች ያትታሉ። ከወረርሽኙና ከድርቅ ጋር ተያይዞ ባለፈው ወደ 30 ሚሊዮን የሚጠጋ ወገናችን ለምግብ እህል እጥረት መጋለጡን መንግሥት ይፋ አድርጓል። ግብርና ለአገሪቱ ጥቅል ብሔራዊ ምርት ድርሻው 47 በመቶ ቢሆንም እድገቱ የሚጠበቀውን ያህል አይደለም።
አገራችን የወጣት ፣ 85 በመቶ የሚሆነው ሕዝቧ በገጠር የሚኖር፣ አመቱን ሙሉ የሚፈስሱ ወንዞች፣ የሁለት ጊዜ የዝናብ ወቅት፣ የሚታረስ ሰፊ መሬት፣ ታታሪ ሕዝብ ያላት እና ቀደምት ከስድስት ሺህ አመታት የሚሻገር የእርሻና የግብርና ታሪክ ያላት ምድር ብትሆንም ራሷን እንኳ በቅጡ መመገብ አልቻለችም።
በስንዴውና በዘይቱ ሲገርመን ሽንኩርትና ምስር ከውጭ እያስገባን ነው። በእኛው አባይ የለማ የግብጽ ብርቱካን በአለፍ ገደም ብቅ እያለ ነው። ካለፉት ሦስት አመታት ወዲህ ግን ከዚህ አዙሪት ለመውጣት በመንግሥት በኩል ፍላጎትና ቁርጠኝነትን እየተመለከትን ነው። ዛሬም ተረጂ ፣ ዛሬም ስንዴና ዘይት ከውጭ አስመጪ መሆናችን ቁጭት የፈጠረ ለለውጥ ያነሳሳ ይመስላል።
ቀድሞውኑም በኢኮኖሚያዊ አዋጭነትና በጥናት ባልተመሠረተ አግባብ ግብርናው የሚገባውን ያህል ድጋፍ ሳያገኝ ከፈረሱ ጋሪው እንዲሉ በግዕብታዊና በፖለቲካዊ ውሳኔ የዩኒቨርሲቲና የኢንዱስትሪ ፓርክ መዓት አግተልትለን ለምሩቃኑ ሥራ ለፋብሪካው ጥሬ ዕቃ ማቅረብ አልቻልንም። ለዚች አገር ነፍስ መዝሪያዋም መሞቻዋም ግብርና ነው።
ግብርና ላይ ከተሳካልን ሌሎችን ዘርፎች ይዞ መነሳትና መውጣት ይቻላል። ለቀደሙት 27 አመታት ከፕሮፓጋንዳ ባለፍ የአገራችንን ስነ ምህዳር ታሳቢ ያላደረገ የዘመቻ ሥራ መሠራቱ ዛሬ ላይ ጥሎናል። ቆም ብለን ትንፋሽ ስበን የመጣንበትን መንገድ ገምግመን በግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ የሚስተዋለውን መዋቅራዊና ተቋማዊ ችግር ቀርፈን ትኩረታችን ግብርናው ላይ ሊሆን ይገባል።
ይህ እስኪሆን የለውጥ ኃይሉ እጁን አጣጥፎ አለመቀመጡና የህልውናችን መሠረት የሆነውን አየር ንብረታችን እንዲያገግም በአምስት አመታት ውስጥ ወደ 25 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ግብ ጥሎ ካለፉት አራት አመታት ጀምሮ ወደ ተግባር መገባቱ የኑሮአችንና የኢኮኖሚያችን የጀርባ አጥንት ለሆነው ግብርና መልካም ዜና ነው። በሚቀጥሉት አምስትና አስር አመታትም የአገራችንን አየር ንብረትና ሥነ ምህዳር / ኢኮሎጂ / ፍጹም ይቀይረዋል።
ይህ በግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ላይ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት መስፈንጠሪያ ነው። ይህ በሂደት እውን እስኪሆን የለውጥ ኃይሉ ስንዴን ከውጭ ማስገባትን ለማስቀረት፣ ግብርናውን ሜካናይዝድ ለማድረግ፣ መሬት ጦም እንዳያድር፣ የኩታ ገጠም አሠራርን ለማስፋፋት የሚያደርገው ጥረት ይበል የሚያሰኝ ሆኖ ወጥ በሆነና ስፋት ባለው አግባብ እንደየ ሥነ ምህዳሩ በመላ አገሪቱ ተግባራዊ ማድረግ ላይ ግን ይበልጥ ሊሠራ ይገባል።
እንደ አገር ያለን ሀብት የሚታረስ መሬት፣ ውሃና የሰው ኃይል ነውና ለግብርናው ቅድሚያ ሰጥተን ልንረባረብ ይገባል። ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረግ ሽግግር ያለ ግብርናው ጽኑ መሠረት እውን ሊሆን አይችልምና። ስለሆነም ያለንን ሀብት ሁሉ አቀናጅተን ግብርናው ላይ ልንረባረብ ይገባል። የአረንጓዴ አብዮት በማቀጣጠል አንገታችንን ሲያስደፋን ሲያሸማቅቀን ከኖረው ርሀብ፣ ቸነፈርና ድህነት ይህን ተከትሎ ከማይለየን ተረጂነት መላቀቅ አለብን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
አዲስ ዘመን የካቲት 19 ቀን 2015 ዓ.ም