(የመጨረሻ ክፍል)
ለሀገራችን ኢትዮጵያ ነጩን ቤተመንግስት ዴሞክራቶች ይሁኑ ሪፐብሊካኖች ቢቆጣጠሩት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲያቸው ብዙም ልዩነት ስለሌለው ይህ ነው የሚባል ተጠቃሚነት የሚፈጥር አይደለም። ቀደም ባሉት ጊዜያት ሪፐብሊካኖች የግብጽ ነገር እንዴት እንደሚያንዘረዝራቸው ከግብጽ ጋር በነበሩን ድርድሮች ታዝበናቸዋል። በታላቁ የሕዳሴ ግድብ የተነሳ አሜሪካ ሁለት ጊዜ ወደ ጸጥታው ምክር ቤት ሀገራችንን መጎተቷ ሳያንስ ትራምፕ የሕዳሴውን ግድብ ግብጽ ለምን በቦንብ አታፈርሰውም እስከ ማለት ደርሰው ነበር።
ወደ ዴሞክራቶች ስንመጣ ደግሞ ባለፉት ሁለት አመታት እንዴት የበረታ ጫና ያደርጉብን እንደነበር አይረሳም። ሀገራችን 15 ጊዜ በመንግስታቱ ድርጅት በተከሳሽ ሳጥን እንድትቆም የአንበሳውን ድርሻ ተጫውተዋል ፤ ሀገራችንን ለአፍሪካ አገራት ከሰጠችው ከቀረጥና ኮታ ነፃ የሆነ የገበያ እድል(African Growth and Opportunity Act /AGOA/) አግዋ አስወጥተዋል፤ ይህ አልበቃ ብሏቸው በሀገራችን ላይ ማዕቀብ ጥለዋል፤ ከዓለም ባንክና ከአለማቀፉ የገንዘብ ተቋም ልናገኘው የነበር የፋይናንስ ድጋፍ እንዲዘገይ አድርገዋል።
ይህም ሆኖ ግን ባለፉት ሁለት አመታት ፓርቲዎቹ በሀገራችን ላይ ያራመዱትን አቋም ከወጪ ቀሪ ስናሰላው ለሀገራችን ሪፐብሊካኖች ይሻላሉ። የቢቢሲው አንቶኒ ዙርከር ምርጫው ለሪፐብሊካኖች ጥሩ ሊባል የሚችል ቢሆንም የጠበቁትን ያህል ግን አይደለም። እንደ ፎከሩት ከዴሞክራቶች ጋር አንገት ለአንገት የተናነቁባቸውን ሁሉ እንደ ማዕበል ጠራርገው ማሸነፍ አልቻሉም። ሪፐብሊካኖች ባልተጠበቀ ሁኔታ ፒንሲላቫኒያ ላይ የሴኔት መቀመጫን ያጡ ሲሆን ይሄን ለማካካስና አብላጫ መቀመጫ ለማግኘት፤ ኔቫዳና አሪዞና ዴሞክራቶች ያሸነፉ ሲሆን የጆርጂያ የሴኔት መቀመጫም ዴሞክራቶች ሰፊ የማሸነፍ ዕድል እንዳላቸው ተገምቶ ነበር።
በርካታ የሕዝብ አስተያየት አጥኚዎችና ታዋቂ ሚዲያዎች ሪፐብሊካኖች የተወካዮች ምክር ቤት አብላጫ መቀመጫዎችን ያሸንፋሉ ብለው ቢተነብዩም አልሰመረም። በ2020 ምርጫ በርካታ የምክር ቤት መቀመጫዎችን ማሸነፋቸው በዚህ የዘመን አጋማሽ ምርጫ በቀላሉ ሊያሸንፉ ይችላሉ የሚል ትንበያ ነበር። ፍሎሪዳ ሪፐብሊካኑን ሮን ዲሳንቲስ ዳግም መረጠች።
ከ4 አመት በፊት የዴሞክራቱን አንድሪው ጂሉም ያሸነፉት በጠባብ ልዩነት ሲሆን፤ ዘንድሮ ግን በሰፊ ልዩነት በሁለት አኅዝ ማሸነፋቸው የ2024 ፕሬዝዳንታዊ እጩ ለመሆን ያግዛቸዋል እየተባለ ነው። የቀድሞው ፕሬዝዳንት ትራምፕ በዚህ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ ተፎካካሪ ባይሆንም ተጽዕኗቸው ግን ቀላል አልነበረም። በዚያው ሰሞን ማራላጎ በሚገኘው የመኖሪያ ቤታቸው በሰጡት መግለጫ የደገፏቸው እጩዎች በአብላጫ ማሸነፋቸውን ገልጸዋል።
መሬት ላይ ያለው ሀቅ ግን ለየቅል ነው ይለናል ቢቢሲ፤ ትራምፕ ድጋፋቸውን ገልጸውላቸው የነበሩት አብዛኛዎቹ እጩዎች አልቀናቸውም። ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከመደገፍ አልፈው እንዲመረጡ ይቀሰቅሱላቸው የነበሩት የፔንሲልቫኒያ ሴናተር ሜህሜት ኦዝ ሲረቱ፤ እንዲሁም ትራምፕ የደገፋቸው የጆርጂያው ሔርሼል ወከር 50 በመቶ ማሸነፍ ባለመቻላቸው 2ኛ ዙር ለመወዳደር ተገደው በመጨረሻ ተሸንፈዋል።
ትራምፕ ደግፈዋቸው የነበሩት ሌላው እጩ የአሪዞናው ብሌክ ማስተርስ ፤ በዴሞክራቱ ተቀናቃኛቸው እንዲሁ ተረተዋል። ሆኖም ሪፐብሊካኖች አሁንም ሴኔቱን የማሸነፍ ሰፊ እድል አላቸው ቢባልም መራጮች የተጠበቀውን ያህል ወጥተው ድምጽ ባለመስጠታቸው ጉድ ተሰርተዋል። ዲሞክራቷ የካንሳስ ገዢ ላውራ ኬሊ፤ የሪፐብሊካኑን እጩ ዴሪክ ሼሚት በመርታት ለ2ኛ ጊዜ ተመርጣለች።
አልጀዚራ አናገርኋቸው ያለው የቀድሞ ዴሞክራት ሴናተር፤ ጽንስ ማቋረጥን ተቃውመው መቆማቸው ሪፐብሊካኖችን ዋጋ አስከፍሏቸዋል ይላሉ። ሌላው ሪፐብሊካኖች እየተስተዋለ ያለውን የዋጋ ግሽበት ለምርጫ መቀስቀሻነት ሊጠቀሙበት ሲገባ ትኩረት አለመስጠታቸው ዋጋ አስከፍሏቸዋል ሲሉ ይደመጣሉ። በወግ አጥባቂ የሪፐብሊካን ተሿሚ ዳኞች ተጽዕኖ ስር የወደቀው የሀገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጽንስ ማቋረጥን ማገዱ በርካቶች ዴሞክራቶችን ለመምረጥ አነሳስቷቸዋል ይለናል ቢቢሲ። የፕሬዝዳንት ትራምፕን ድጋፍ ያገኙት አብዛኛዎቹ የሪፐብሊካን እጩዎች የድል በለስ ባይቀናቸውም የዊስኮንሰኑ ሴናተር ሮን ጆንሰን መቀመጫቸውን አስጠብቀዋል።
ብዙዎች ሚዲያዎችና የሕዝብ አስተያየት አሰባሳቢዎች እንደተነበዩት ሪፐብሊካኖች በምክር ቤቱ አብላጫ መቀመጫ ቢያገኙም፤ ልዩነቱ በጣት የሚቆጠር ነው የሚሆነው እንዳሉት የሀዋርድ ዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ሮቢንሰን ውድዋርድ ፤ በየአጋማሽ ዘመን ምርጫዎች ኋይትወስን የተቆጣጠረው ፓርቲ 31 መቀመጫዎችን ማጣት የተለመደ ነው ይላሉ ፕሮፌሰሩ፤ ቢል ክሊንተን 54፣ ባራክ ኦባማ 64፣ ዶናልድ ትራምፕ 38 መቀመጫዎችን በአጋማሽ ዘመን ምርጫ ቢያጡም ባይደን ግን በታሪክ አነስተኛ መቀመጫዎችን ነው የተነጠቁት።
የሮይተርሱ ጄሰን ላንጄ የአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ ውጤትን ለማወቅ ቀናትንና ሳምንታትን መጠበቅ ግድ ነው እንዳለው ከብዙ ጥበቃ በኋላ ዴሞክራቶች አሸንፈዋል። በዚህ ምርጫ ተፎካካሪዎች ለ435 የኮንግረስ መቀመጫዎች ፣ ለ35 የሴኔት መቀመጫዎችና ለ36 ግዛቶች ተፋጠው ነበር። ሪፐብሊካኖች በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ወይም በኮንግረሱ አብላጫ ድምጽ ለማግኘት አምስት ተጨማሪ መቀመጫዎችን ማግኘት የነበረባቸው ቢሆንም ከዚያ በላይ አሳክተዋል። ሴኔቱን ለመቆጣጠር ደግሞ ዴሞክራቶች አንድ መቀመጫ ማሸነፍ ይጠበቅባቸው የነበር ቢሆንም ከጆርጅያው ጋር ሁለት መቀመጫዎችን በመርታት ሴኔቱን በእጃቸው አስገብተዋል።
ስለ አሜሪካ ምርጫ የምንፈተፍተው ውጤቱ ምንም ይሁን ምን በአዎንታ ወይም በአሉታ በሀገራችን ላይ ተጽዕኖ ስላለው ነውና አንዳንድ ነጥቦችን እናንሳ። አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር የዲፕሎማሲ ግንኙነት ከጀመረች ወደ 120 አመታት እየተጠጋት ነው። በአሜሪካም ሆነ በኢትዮጵያ መንግስታት ቢቀያየሩ አንድ ጊዜ ሞቅ ሌላ ጊዜ ቀዝቀዝ አልፎ አልፎም ለብ እያለ ቀጥሏል።
የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት አሜሪካ ከሌሎች ሀገራት ጋር ታራምደው ከነበረ ግንኙነት የተለየ አልነበረም። ከብሔራዊ ጥቅሟ በተጻራሪ የሚቆም መንግስት በመጣ ጊዜ ለመቀየር የማትፈነቅለው ድንጋይ የለም። በ19ኛው መክዘ እኩሌታ ማብቂያ አካባቢ በላቲን አሜሪካ በደቡብ ምዕራብ ፓሲፊክ እንዲሁም በ20ኛው መክዘ መግቢያ ደግሞ፤ በፓናማ ፣ ሆንዱራንስ ፣ ኒካሯጓ ሜክሲኮ፣ ሄይቲና ዶሚኒካን ሪፐብሊክ መንግስታትን ለውጣለች።
በተለይ በቀዝቃዛው ጦርነት (1945-1991 እኤአ)ዓለም በሶሻሊስትና በካፒታሊዝም ርዕዮተ ዓለም ጎራ በተከፈለ ጊዜ የኢትዮጵያና የአሜሪካ ግንኙነት ሻክሮ ነበር። ደርግ ሶሻሊስት ስለነበርና አሰላለፉም በሶቭየት ሕብረት ረድፍ ስለነበር አሜሪካና አጋሮቿ ለተቃዋሚዎች በግልጽ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ድጋፍ በማድረግ፤ ደርግን በተራዘመ ትጥቅ ትግል ገርስሰው አስመራንና አዲስ አበባ እንዲገቡና የስልጣን መንበሩን እንዲቆጣጠሩ በማድረግ የማይተካ ሚና ተጫውተዋል። ታሪክ ራሱን ይደግማል እንዲሉ አሜሪካ ባለፉት ሁለት አመታት የኢትዮጵያን መንግስት የመቀየር ያልተሳካ ሙከራ አድርጋለች።
በተለይ አሜሪካ በኢትዮጵያ እንዳደረገችው በመላው ዓለም የ70 ሀገራትን መንግስት ለመለወጥ በህቡዕና በይፋ ተንቀሳቀሳለች። የቀዝቃዛው ጦርነት በበርሊን ግብ መፍረስ በሶቪየት ሕብረት መበታተን ከተቋጨ ከ30 አመታት በኋላ፤ ዛሬም የማትፈልገውን መሪ ለማስወገድ በምርጫ ጣልቃ ትገባለች በውክልና ወይም በቀጥታ መንግስት ትገለብጣለች።
ሀገሬን ያለ ብሔርተኛ/nationalist/ ተላላኪና አሻንጉሊት አልሆንም ያለና ለዜጋው ጥቅም የቆመ መንግስት፤ ከአሜሪካና ከምዕራባውያን ጥቅም በተጻጻሪ እንደቆመ እንደጠላት ተቆጥሮ እንዲወገድ ይደረጋል። ባላንጣየ ከምትላት ቻይና ጋር የጠበቀ ግንኙነት ያለውም በጠላትነት ተፈርጆ ጥርስ ይነከስበታል። የቡርኪናፋሶው ቶማስ ሳንካራ የጋናው ኩዋሚ ንኩሩማህ የኢራቁ ሳዳም ሁሴንና የሊቢያው ሞአመር ጋዳፊ ከሰለባዎቿ መካከል ይጠቀሳሉ።
በምርጫ ጣልቃ መግባትም ሆነ የመንግስት ለውጥ ማምጣት የአሜሪካንን ጥቅም ለማስከበር አዋጭ ነው ቢባልም፤ መጨረሻው ግን ሀገራትን ወደለየለት የእርስ በርስ ጦርነት እና ቀውስ ስለሚዘፍቅ ውጤታማ ባይሆንም ዛሬም በጀ ብላ ቀጥላበታለች። የቅርቦቹን እነ አፍጋኒስታን፣ ኢራቅ ፣ ሶሪያ ፣ የመን ፣ ቬኒዞላንና ሄይቲ ልብ ይሏል።
ዛሬም ጥቅሜን ያስከብርለኛል የምትለውን መንግስት ለማንገስ በኢራንና በሶሪያ በሌሎች በርካታ ሀገራት አሻንጉሊትና ተላላኪ መንግስት ለመተካት ሌት ተቀን እያሴረች ነው። አሜሪካ እኤአ 1946-2000 በ81 ሉዓላዊ ሀገራት ምርጫ በይፋ ወይም በስውር ጣልቃ ገብታለች። በጣሊያን፤ በፊሊፒንስ፣ በሊባኖስና በጃፓን ምርጫዎች ጣልቃ በመግባት እንዳሻት የምታሽከረክረው መንግስት እንዲመረጥ አድርጋለች።
የመንግስታቱ ድርጅት ቻርተር አንቀጽ 2 ቁጥር 4 ላይ በግልጽ የአንድን ሉዓላዊ ሀገር መንግስት፤ በኃይልም ሆነ በሴራ ለመለወጥ የሚደረግ እንቅስቃሴን የሚያወግዝ ድንጋጌ ከጸደቀ በኋላ እንኳ አሜሪካ ይህን አለማቀፍ ሕግ በመተላለፍ የ70 ሀገራትን መንግስታት ለውጣለች። ለዓለም ሰላም ለሕግ ልዕልና ለሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ቆሜያለሁ የምትለው አሜሪካ እንዲህ ናት።
ቆሜለታለሁ የምትለው እሴትና መርህ የውሸት ነው። ስለዚህ ከአሜሪካ ጋር የሚኖረንን ግንኙነት በጥንቃቄ ማየትና መከታተል ያሻል። ከሁሉም በላይ አሜሪካንን ለጣልቃ ገብነት የሚጋብዙ ቀዳዳዎችን እየተከታተሉ መድፈን ልዩ ትኩረት ይሻል። ውስጣዊ አንድነት ላይ ያልሰራናቸውን ተግባራትም በጊዜ መከወን ይጠይቃል።
ዘላቂው መፍትሔ ምዕራባውያን ድህነታችንና ኋላቀርነታችንን መያዣ አድርገው ዝቅ አድርገው እንዳያዩን ፤ ከፍ ሲልም በእርዳታና በብድር ሰበብ በነጻነታችንና በሉዓላዊነታችን ላይ እንድንደራደር እጃችን ለመጠምዘዝ የሚደረገውን ጥረትና ጫና ለመቋቋም የድህነትንና የኋላቀርነትን ቀንበር ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ መስበር አለብን። የግብርናውን፣ የኢንዱስትሪው፣ የአገልግሎት ዘርፉን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የድህነትንና የኋላቀርነትን ቀለበት ሰብረን የመውጣት ጉዳይ ለነገ የሚተው ጉዳይ አይደለም።
አስተማማኝ የስራ ዕድል መፍጠር ፤ የዋጋ ግሽበትንና የኑሮ ውድነትን ከመቀነስ ጎን ለጎን ደግሞ የዴሞክራሲ፣ የደህንነትና የጸጥታ ተቋማትን መገንባ ፤ የሕዝብን አንድነት የሚሸረሽሩ ፖለቲካዊ ሴራዎችንና ደባዎችን ተቆራርጦ መታገል ፤ ብልሹ አሰራሮችንና ሙስናን ፤ ጽንፍ የረገጠ ብሔርተኝነትን ፤ ወዘተረፈ ማስወገድ ፤ ውስጣዊ ለቀውስ ተጋላጭነትን ከመቀነስ ባሻገር እንዳለፉት ሶስትና አራት አመታት ያሉ ያላባሩ ጫናዎችን ለመመከት ጉልበት ይሆናሉ።
ከውጭው ጫና ይልቅ እነዚህን የቤት ስራዎቻችንን አበክረን ባለመከወናችንና ባለመስራታችን የሚመጣብን አደጋ የከፋ መሆኑ ግንዛቤ ተወስዶ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች ይበል የሚያሰኙ ናቸው። መንግስት ምንም እንኳ ወደ ስልጣን ከመጣበት የመጀመሪያ ቀን አንስቶ በየአቅጣጫው ዘርፈ ብዙ የጥቃት ግንባሮች ተከፍቶበት ፋታ ባያገኝም ተስፋ የሚጣልባቸውን ተግባራት አከናውኗል።
ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ ሰሞኑን በአፋር ክልል እየለማ ያለ የጥጥ እርሻን በጎበኙበት ወቅት ፤ “ አባቶቻችን ደማቸውን አፍስሰው ፣ አጥንታቸውን ከስክሰው ያጎናጸፉንን ሉዓላዊነትና ነጻነት በላባችን ማስከበር ካልቻልን ልናጣው እንችላለን። “ በማለት ድሀና ተመጽዋች ሀገር ነጻና ሉዓላዊ ሊሆን እንደማይችል አጽንኦት ሰጥተዋል።
አመቱን ሙሉ የሚገማሸሩ ወንዞችን ፣ ሊታረስ የሚችል ሰፊ ለም መሬትንና አምራች የሰው ኃይሉን አቀናጅተን በአመት ሁለትና ሶስት ጊዜ በማምረት በምግብ እህል ራሳችንን ችለን ለፋብሪካዎችና ኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚተርፍና ለውጭ ገበያ የሚቀርብ አምርተን ከድህነትና ከኋላቀርነት ካልተላቀቅን አያት ቅድመ አያቶቻችን መስዋዕት ሆነው ያቆዩን ነጻነትና ሉዓላዊነት ሙሉ ሊሆን አይችልም፡፡
ለዚህ ነው የለውጥ ኃይሉም ሆነ የጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ መንግስት ወደ ኃላፊነት እንደመጣ ድፍረት የተስተዋለባቸውን ማሻሻያዎችን ያደረገው በተለይ የሕዳሴው ግድብ ላይ ተደቅኖበት የነበረን አደጋ የመቀልበስ ፤ የአረንጓዴ አሻራ ፣ የኩታ ገጠም እርሻ፣ የበጋ ስንዴ ፣ የሜካናይዜሽን ግብርናን ፣ ወዘተረፈ በመተግበር የሚጨበጥ ለውጥ ያመጣው። ሕዳሴውን ከለየለት ክሽፈት ታድጎ ለዚህ ስኬት የበቃው።
ካለፈው አመት ጀምሮ ስንዴን ከውጭ ማስገባት አቁሞ ራሱን የቻለው ፤ በዚህ አመት ደግሞ ወደ ውጭ ለመላክ ያቀደው። ይህ ስኬት የውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችን አካልና መደላድል ነው። ውስጣዊ ድሎቻችን ለውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችን አቅም ናቸው። ከፍ ብዬ የጠቀስኋቸው ሶስቱ ኩነቶች ወደዚህ የሚያደርሱ ናቸው። አንድ ምስል ይከስታሉ ያልሁትም ይሄን ነው።
የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ጉምቱ አሜሪካዊ ሪቻርድ ሀስ ፤ “ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ከሀገር ቤት ይጀምራል ፤ “/ FOREIGN POLICY BEGINS AT HOME :…” በሚል መጽሐፉ ይሄን ይተነትናል። ጠቅላይ ሚንስትሩና መንግስታቸው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ከሀገር ውስጥ እንደሚጀምር አበክረው ተገንዝበው እየሰሩ ያሉት ለዚህ ነው።
የሀገራችንን ሰላም ፈጣሪ ያጽናልን !
ሻሎም !
አሜን ።
አዲስ ዘመን ጥር 21 ቀን 2015 ዓ.ም