ኢትዮጵያ ሀገራችን በአለም ላይ በባህላዊ እሴቶቻቸው ሀብታምና ኩሩ ከሚባሉ ሀገራት መካከል አንዷ ናት። በዚህ የህዝቦች የጋራ ትውፊት በሆነ ባህላዊ እሴት ተመርተን ብዙ ዘመናትን በፍቅርና በወንድማማችነት ተጉዘናል። አሁን ላይ እንደ ድሮው በዝተውና ጠርተው አይኑሩ እንጂ ኢትዮጵያዊነትን ጠብቀውና አክብረው የሚኖሩ እሴቶቻችን ቀላል የሚባሉ አይደሉም።
በአንድ ሀገር ማህበራዊ እሴቶች ሁሉንም ነገር ናቸው። በደስታና በሀዘን፣ በየትኛውም ባህበራዊ ህይወታችን ውስጥ ከፊት ቀድመው የምናገኛቸው እነሱን ነው። ለአፍታ ዞር ብንል ዘመናዊነትን ያስናቁ ኢትዮጵያዊ ቀለሞችን እናገኛለን። አብረን የበላንባቸው፣ በሀዘንና በደስታ የተደጋገፍንባቸው እነዛ ዘመኖች መልካም እሴቶቻችን ናቸው።
ዛፍ ጥላ ስር ተሰብስበን ስለችግሮቻችን ያወጋን ባቸው፣ አንተ ትብስ አንተ ተባብለን የተጎራረስንባቸው፣ በደቦ ተሰባስበን ያረስንባቸው፣ ቤት የሰራንባቸው እነዛ ጊዜዎች የኢትዮጵያ ወርቃማ ዘመኖች ናቸው። በታላላቆቻችን ፊት የምናጎነብስበት፣ የአባቶቻችንን እግር የምንስምበት፣ ነዋር ስንባል በእግዜር የምንባባልባቸው እነዛ ዘመኖች ኢትዮጵያዊነትን ከፍ ያደረጉ እሴቶቻችን ናቸው።
ባህላዊ የእርቅ ስርዓቶቻችን የኢትዮጵያ ጌጦች ናቸው። ሀገር ያቆዩልን፣ ታሪክ ያበጁልን እነሱ ናቸው። እስኪ ለአፍታ ኢትዮጵያን ያባህልና ስርዓት እናስባት..ምንም ናት አይደል? ሀገራችን ብቻ አይደለችም እኛም ያለባህሎቻችን ምንም ነን። አንዳንድ እሴቶች ከምንምነት መውጫ ቀዳዳዎች ናቸው።
ዛሬ ላይ ከምንምነት መውጣት ያቃተን ለእነዛ መልካም እሴቶቻችን ዋጋ ያለመስጠት ነው እላለው። ሀገራችን በዚያ ዘመን ከምንምነት የወጣችው ባህላዊ ስርዓቷን ይዛ ነው። ዛሬም ከተደቀኑብን ጊዜ ወለድ እድፎች ለመጽዳት ወደ ባህሎቻችን ማየት ይኖርብናል። ወደ እርቅ እሴቶቻችን፣ ወደ አንድነት እሳቤአችን መመለስ ይኖርብናል።
እስኪ ራሳችንን እንበርብር..እስኪ ወደ ኋላ ራቅ ብለን እንመልከት። ኢትዮጵያን እኮ ትተናት መጥተናል። አሁን የቆምንበት ቦታ ላይ እኛ እንጂ ኢትዮጵያ የለችም። ኢትዮጵያ ያለችው ከኋላችን ነው..በድንቅ ባህልና ስርዓት ተከባ። እኛ ባህልና ስርዓታችንን ትተን ዘመን ባሳየን በማይጠቅመን አለም ውስጥ ነን። ትተናት ወደመጣንው ኢትዮጵያ እንመለስ..ክብራችን፣ ከፍታችን፣ ስልጣኔአችን፣ አንድነታችን፣ ታሪካችን፣ ያለው እዛ ነውና።
ኢትዮጵያ በአለም አደባባይ ስሟ ከፍ ያለው አባቶቻችንን ይዛ ነው። በባህልና ወጓ ውስጥ በቆሙ አባቶቻችን። በእኛ ጊዜ ኢትዮጵያ ስሟ ጎደፈ እንጂ አልተወደሰም። ዛሬም ድረስ የምንጠራው በአባቶቻችን ስም ነው። ለራሳችንም ለትውልዱም የሚሆን አንዳች ነገር የለንም። ይሄ ለምን ሆነ ብለን ስንጠይቅ አንድ መልስ እናገኛለን እርሱም ከኢትዮጵያዊነት ስለራቅን ነው የሚል ነው።
አባቶቻችን በአለም ላይ ገነውና ኮርተው የኖሩት በባህላዊው ስርዓት ውስጥ ስለቆሙ ነው። ሲጣሉ አስታራቂ ሳያሻቸው እየታረቁ። አብረው እየበሉና አብረው እየጠጡ፣ በአንዱ ህመም አንዱ እዬዬ እያለ በዚህ ነው። እኛ አይደለም ለትውልዱ ለራሳችን ያልበቃነው መነሻውን በማናውቀው የአውሮፓ ስልጣኔ ስለወደቅን ነው።
ራስን መተው ምን ያክል ዋጋ እንደሚያስከፍ አይንን ከፍቶ ማየት ያስፈልጋል ። አባቶቻችን ተፈጥረው እስኪያልፉ ድረስ ማንንም አልነበሩም..ማንንም አልመሰሉም። ራሳቸውን ሆነው ነበር የኖሩት። እኛ ግን ሌላ ነን..መልካችንን ቀይረን፣ ባህላችንን ሽረን ሌሎችን ሆነናል።
ወደ እሴቶቻችን እንመለስ፤ ከወደቅንበት የሚያነሳን አባቶቻችንን መሆንና እነሱን መምሰል፣ በነሱ እውነት ውስጥ መጓዝ ነው ። አሁን ላይ ዋጋ እያስከፈሉን ያሉ ነገሮች ሁሉ አባቶቻችን አይጠቅመንም ብለው የተዋቸው ናቸው ።
አለም በስልጣኔ ስም የምትሰጠንን በሙሉ አግበስብሶ ከመቀበል መቆጠብ ይኖርብናል። ሁሉም የሚጠቅሙን አይደሉምና በማስተዋል መርጠን ልንቀበል ይገባል። የእኛ የሆነውንና የሚጠቅመንን ብዙውን ጥለን የነሱን እያጋበስን ነው። እኛ በማያተርፈን የስልጣኔ ውድ ባህላችንን እየጣልን ነው።
በችግሮቻችን ውስጥ አስታራቂና መፍትሄ ሰጪ መስለው የሚገቡት ውድ የእርቅ እሴቶቻችንን አደብዝዘውብን ነው። እንደዛ ባይሆንማ ከራሳችን አልፎ ለሌሎች የሚተርፍ የእርቅና የሽምግልና ባህል ነበረን። እስኪ በእኛ ጉዳይ አለም እጇን አርዝማ ያልገባችበት ጊዜ የቱ ነው? ።
ለመግባት እንዲቻላት አላስገባ ብለው የከለከ ሏቸውን ማህበራዊ እሴቶቻችንን ዘመናዊ በሚመስሉ ከንቱ ነገሮች እየጨፈለቀጭብን ነው ። በዚች ሁለት አመት ውስጥ እንኳን ከህወሓት ጋር በተፈጠረ ጦርነት ያጋጠሙንን ተጨባጭ እውነታዎች ማስታወስ በቂ ነው ።
ለባህላዊ እሴቶቻችንን ዋጋ ከሰጠናቸው ችግሮቻችንን ለመመከት በቂና ከበቂ በላይ ናቸው። ወደሌሎች ሳናይ፣ የሌሎች ጣልቃ ገብነት ሳይታከልበት በችግሮቻችን ላይ የበላይ የምንሆንበት ብዙ እድል አለን ። እነዛን እድሎች ተጨባጭ ማድረግ የምንችለው ደግሞ ለባህላዊ እሴቶቻችን ተገቢውን ዋጋ ስንሰጥ ብቻ ነው።
ወደራሳችን እንያ..እኛ የሌለን አለም ያለት ምንድነው ብለን እንጠይቅ። ኢትዮጵያን እንበርብራት..የአባቶቻችንን ልቦች እንፈትሻቸው። ምን ነበሩ..ምን ይመስሉ ነበር? ከአብራካቸው በቅለን እኛ እነሱን ያልመሰልነው ለምንድነው? የአባቶቻችን ልጆች መሆን ያቃተን በምን ይሆን? እያልን እንጠይቅ።
መጠየቅ፣ ማንነትን ከማወቅ በሚመነጭ ስብእና አሁንን ለማሸነፍ እድል ይሰጣል ። ኢትዮጵያ ሙሉ ናት.. እኛ ወደ ራሳችን ከተመለስን ገናብዙ ነገር ለአለም ማበርከት እንችላለን። ብዙ መደነቆችን ልንፈጥር እንችላለን ።አለከዛበፊት ግን ወደ ራሳችን ተመልሰን ባለን ነገር እንደነቅ ። በባህሏና በስርአቶቿ እንደነቅ።
በወግና ልማዷ፣ በእምነትና ቀለሟ እንኩራ። ሀገር በሰሩ ባህላዊ እሴቶቿ እንመካ። በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ ቅርሶቿ እንደነቅ። ያኔ ልክ መሆን እንጀምራለን። ያኔ ለችግሮቻችን የሌሎችን ጣልቃ ገብነት መጠበቅ እናቆማለን። ያኔ ኢትዮጵያዊነት አለም ተመኝቶ ያጣው ማንነት እንደሆነ እንደርስበታለን።
የኢትዮጵያ ማህጸን ባለ ብዙ ፍሬ ነው። ብዙ አይነት ጉራማይሌ መልኮችን ጸንሳ የወለደች ሀገር ናት። በየጓዳውና ጎድጓዳው አለምን ያስደነቁ የብሩክ እጆች ዋጋ አሉ። በየሀገሩ፣ በየመንደሩ ኢትዮጵያዊነትን ያጀገኑ እሴቶች አሉ። እዚህም እዚያም ዘመናዊነት የሸፈናቸው፣ ስልጣኔ የደበቃቸው ብዙ መልካም ባህሎች አሉን።
ኢትዮጵያዊነትን ቀን ያወጡ ፣ ሀበሻነትን የገለጡ ነገር ደግሞ በዘመን የተደበቁ ብዙ የአንድነት እሴቶች አሉን። ዛሬ ላይ የሚያስፈልገን እነዛን ባህላዊ እሴቶች መግለጥ ነው። ዛሬ ላይ የሚያስፈልገን በስልጣኔ ስም የተሸፈኑ መልካም እሴቶች ነጻ ማውጣት ነው። አባቶቻችን ከዚህ ዘመን በራቀና በመጠቀ መልኩ አስተዋይ ነበሩ ። የነሱ አስተዋይነት ሀገር በማቆየት ውስጥ፣ ኢትዮጵያዊነትን የሙጥኝ ብሎ ችግሮችን በሽምግልና በመፍታት ውስጥ፣ እግዚአብሄርን በመፍራት ውስጥ ተጀምሮ ያበቃ ነበር።
በዛፍ ስር መታረቅ፣ በዛፍ ስር ተቀምጦ ሰላም ማውረድ፣ በዛፍ ስር ተሰብስቦ ደም የተቀባቡ ነፍሶችን ማስተቃቀፍ ከዚህ በላይ ምን ዘመናዊነት አለ? ከዚህ የተሻለ አስተዋይነት አለ !? ። ወደዚህ አባቶቻችን ማስተዋል እንመለስ ። በአባቶች ምክር ቂምን መርሳት፣ በደልን መተው..በአዛውንቶች እውነት ተመርቶ በይቅር ለእግዜር ወንድማማችነትን መመለስ፣ ጉርብትናን ማስቀጠል ዋጋው በምን ይለካል? ።
በአባቶች ‹አንተም ተው አንተም ተው› በምትል ላመል ቃል ፍቅርን መመለስ፣ ጥላቻን መሻር ዋጋው የት ድረስ ነው? ይሄን ነው የሚበጀን። ትተናት የመጣንው ኢትዮጵያ ይቺ ናት። ዛሬም መቼም ታስፈልገናለችና..ወደ እኛ ሳይሆን ወደ እሷ ተራምደን እንቆራኛት። የአባቶቻችን የእርቅና የሽምግልና ስርኣቶች ለዛሬ መከራዎቻችን ደም አድራቂዎች ናቸው። ተመርኩዘናቸው ይሄን ክፉ ጊዜ ብናልፍባቸው ብዙ እናተርፋለን ። በየትኛውም ዘመን የኖረችውን ኢትዮጵያን ብናያት በዚህ ባህላዊ እሴት የቆነጅች ሆና ነው የምናገኛት።
በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ ቅርሶች በአለም አቀፍ ደረጃ ቀዳሚ ነን። እኚህ ሁሉ የጋራችን ናቸው። እኚህ ሁሉ የሚያግባቡን ነበሩ። ተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ ቅርሶቻችን የአንድ ብሄር ንብረት ሳይሆኑ የአጠቃላዩ ኢትዮጵያዊ መጠሪያ ናቸው። ባህላዊ እሴቶቻችን የአንድ ወገን ንብረት ብቻ ሳይሆኑ የሁላችንም መድመቂያዎች ናቸው።
ሌላው አለም እኛ ያለን ያህል ተሪክና ከዚህ የሚቀዳ ቅርስ ባለቤት አይደለም ። የራሳችንን አሳንሰን የምንጓዝበት መንገድ ዋጋ ከማስከፈል ባለፈ አያሻግረንም ። አንዘናጋ የሚሻለን ከማንነታችን/ ከኢትዮጵያዊነት ጋር መታረቅ ነው ።
ለእሴቶቻችን ዋጋ በመስጠት መከራዎቻችንን በቀላሉ ማለፍ እንችላለን። አሁን ላይ ከገጠሙን ሀገራዊ ችግሮች ለመውጣት ቀላሉና አስተማማኙ ዘዴ ለባህላዊ የእርቅ ስርኣቶቻችን እውቅና መስጠት ነው።
እነዚህ እሴቶችቻችን ለሰላማችን አልፋና ኦሜጋ ናቸው ።
አለም የአሁኑን ስልጣኔዋን ከማግኘቷ በፊት እንደ ሀገርና እንደ አህጉር ስትንቀሳቀስ የነበረችው በህዝቦች የጋራ እሴቶች ተመርታ ነው። ወደ ሀገራችን መጥተን በእያንዳንዱ ብሄረሰብ ጓዳ ውስጥ ያሉትን ባህላዊ እሴቶች ብንመረምር ደግሞ ሀገራችን ምን ያክል በባህላዊ እሴቶቿ ባልፅጋ እንደሆነች እንደርስበታለን። ባህላዊ እሴቶች የዘመናዊ ስልጣኔ መነሻዎች ናቸው።
አንድ ሀገር ባህላዊ እሴቶቹን ሳይጠብቅና ሳይንከባከብ ዘመናዊነትን መቀበል አይችልም። አለም ላይ በተፈጥሮ ከታደሉ ሀገራት መካከል አንዷ ኢትዮጵያ ናት። በዚህ መታደል ላይ ዋጋ ያላቸው ባህላዊ እሴቶች ሲጨመርበት መዳረሻችን ምን ሊሆን እንደሚችል ለማሰብ አይከብድም ። በባህላዊ የእርቅ ስርዐታችን መታረቅ እየቻልን የሌሎችን ጣልቃ ገብነት ከፈለግን የመጨረሻ አለመታደል ነው።
በዘመናዊነት ካባ አንቱታን ያሰጡንን የእናት የአባት ስማችንን እያጣን ነው። ጥንት አባቶቻችን ከዘመን ቀድመው፣ ከስልጣኔ ልቀው ለችግሮቻቸው የሚሆን ብዙ መላ ነበራቸው። ፍርድ ቤት ሳይሄዱ፣ ሽመል ሳይማዘዙ ተክለው ባጸደቋቸው ኢትዮጵያዊ ወግና ባህል ይቅር ለእግዜር የሚባባሉበት አለም ያላየችው ስልጣኔ ነበራቸው።
ኢትዮጵያ በአለም ላይ ገናና ሆና የኖረችበት ያ ዘመን የአባቶቻችን መልካም እሴት የፈጠረው ተጽዕኖ ነው ። አሁንም ባህላዊ እሴቶቻችንን ከፊት አስቀድመን እስካልተራመድን ድረስ ችግሮቻችንን በዘመናዊ መንገድ ብቻ እንፈታለን ማለት ዘበት ነው። ባህላዊ የእርቅ እሴቶቻችን ከዘመናዊው በላይ የላቀና የሚከበር ዋጋ አላቸው።
እኔና እናንተ በዘመናዊ አለም ውስጥ ዘመናዊ ከመሆናችን በፊት ባላገሮች ነበርን። ዛሬ ላይ ያለንውና እየኖርን ያለንው ያ ባላገርነት በሰጠን ኢትዮጵያዊነት ውስጥ ነው። የጥንቱን ሀያልነታችንን ለመመለስ ዘመናዊነት ከፈጠረው መታወር ወጥተን ባላገር መሆን አለብን። ባላገር መሆን ማለት ከስልጣኔና ከዘመናዊነት ርቆ መኖር ማለት አይደለም።ኢትዮጵያዊ ለሆኑ እሴቶችና ቀለሞች ዋጋ መስጠት ማለት ነው።
አለም አንድ ወቅት ላይ ባላገር ነበረች። ኢትዮጵያ ለብዙ ዘመን ባላገር ነበረች። አሁንም ወደተውንውና ወደረሳንው ባላገርነታችን መመለስ አለብን። ዛሬ ላይ አባቶቻችን በቀላል መንገድ በእርቅ የሚፈቷቸውን ችግሮቻ በዘመናዊ መንገድ መፍታት ያቃተን እኮ እሴቶቻችንን ስለሻርን ነው። ዛሬ ላይ በተልካሻና ውሀ በማያነሳ ሰበብ በብሄርና በጎሳ የምንባላው ጠብቆ ካቆየን ባላገርነት ስለራቅን ነው።
ዛሬ ላይ በመነጋገር መስማማት አቅቶን ችግሮቻችን አለም አቀፍ የሆኑት እኮ ከባህላዊ ይልቅ ለዘመናዊ አስተሳሰብ /እስከ መርዙ እጅ በመስጠታችን ነው። ዛሬ ላይ የእኛ ባልሆነና በማንታወቅበት እኔነትና ራስ ወዳድነት ሰልጥነን ሀገርና ትውልድ የምንመርዘው አብረን ከበላንበት ኢትዮጵያዊነት ስለራቅን ነው።
ባላገርነት ይሻለናል..ባላገሯንና ለወንድማማችነት ቅድሚያ የምትሰጠውን ኢትዮጵያ አምጠን እንውለዳት። ያለባላገርነት ዘመናዊነት ምንም ነው። ባላገርነት የዘመናዊነት ስር ነው። ዘመናዊነት ዋጋ ያለው ለባህላቸውና ለስርዐታቸው ለሚገዙ ሀገርና ህዝቦች ነን።
ከትላንት ሸሽተን የትም አያደርስም። ዛሬን የሰጠን ትላንት ነውና ወደ ትላንት ተመልሰን ለዛሬ ያበቁንን ወርቆቻችንን ከጣልንባቸው ቦታዎች እናንሳቸው ። ለብቻ በመቆም ውስጥ ዘመናዊነት የለም። በመለያየትእና በመኮራረፍ ውስጥ የፀናች ሀገር መፍጠር የሚታሰብ ማስጌጥ፣ ማሳደግና ማድመቅ ነው።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ጥር 14 ቀን 2015 ዓ.ም