በመዲናችን አዲስ አበባ የመንገድ ላይ ልመናን በብዛት መመልከት የተለመደ ከሆነ ሰነባብቷል፡፡ አካል ጉዳተኝነት፣ ድህነት፣ ከአየር ንብረት መዛባትና ከሚታረስ መሬት እጥረት ጋር በተያያዘ ከገጠር ወደ ከተሞች የሚደረግ የነዋሪዎች ፍልሰት በጎዳና ላይ ለሚታየው የተረጂ ቁጥር መበራከት ዋነኞቹ ምክንያቶች ናቸው።
በኢትዮጵያ አስራ አንድ ከተሞች ከሰማንያ ስምንት ሺህ ዘጠኝ መቶ በላይ የጎዳና ታዳዳሪዎች እንዳሉ በጥናት ተረጋግጧል ፡፡ ከነዚህ ውስጥ ሃምሳ ሺ በላይ ያህሉ የሚኖረው በአዲስ አባበ ጎዳናዎች ላይ ነው፡፡ የተሻለ ኑሮን ፍለጋ ወደ መዲናይቱ የሚጎርፉት በብዛት ወጣቶች ናቸው።
እነዚህም ዜጎች ኑሮ እንዳሰቡት ሳይሆን ቀርቶ ውሎና አዳራቸው በጎዳና ይሆናል፡፡ ከማደሪያ ጀምሮ የዕለት ጉርሳቸውን እንኳ ለማግኘት ይቸገራሉ። ከዚህ የሚከፋው ደግሞ አብዛኛዎቹ ወጣቶች ረሃቡን እና እንግልቱን መቋቋም አቅቷቸው በተለያዩ ሱሶች ይጠመዳሉ፡፡
እውነታውን የበለጠ አሳሳቢ የሚያደርገው ደግሞ የነዚህ የጎዳና ተዳዳሪ ዜጎች ቁጥር በየአመቱ በእጅጉ እየጨመረ መምጣቱ ነው። ይህ ደግሞ ችግሩን ከስር መሰረቱ ለመቅረፍ የሚደረገውን አገር አቀፍ ጥረት ፈታኝ እንዲሆን እያደረገው ነው፡፡
እዚህ ላይ በጎዳና ላይ ስለሚስተዋሉት አካል ጉደተኞች ሲነሳ ሁሉም አካል ጉዳተኛ በልመና ላይ ይሰማራል ማለት አይደለም፤ ብዙ አካል ጉዳተኞች ከአካል መጉደል ውጪ ጤነኛ በመሆናቸው፤ ሰርተው ራሳቸውን አሳድገው ከቤተሰብ አልፎ ለማህበረሰብ እና ለአገር ተርፈው አይተናል፡፡
ልመና እና የአካል ጉዳተኝነት ሲታሰብ ግን ችግሩ ተደራራቢ ሲሆን ከሚያስከትለው ጫና አንጻር ነው ፤ በተለይም ከአካል ጉዳት ባሻገር ተጨማሪ የጤና እክል ያለባቸው ፤ በዚህና በሌሎች ተደራራቢ ችግሮች ወደ ጎዳና የወጡትን ለመጥቀስ ያህል ነው።
እነዚህ የማህበረሰብ ክፍሎች የእለት ኑሯቸውን ለመግፋት በልመና ላይ ይሰማራሉ፤ ልመናን መተዳደ ሪያቸው ያደርጋሉ፡፡ እነዚህን የማህበረሰብ ክፍሎች የመርዳት የሁላችንም ሃላፊነት እንደሆነ ይታመናል። ለዚህም ሁላችንም ትልቅ የሞራል ሃላፊነት አለብን።
በሌላ በኩል ዕድሜያቸው የገፉ አረጋውያን ጧሪ ያጡ አዛውንቶችም በስፋት በአዲስ አበባ ጎዳና ላይ መመልከት እየተለመደ መጥቷል ፡፡ እነዚህ ዜጎች በአንድ ወቅት ለሌሎች የሚተርፉ የነበሩ ቢሆንም ፤ ኑሮ ውድነቱ በፈጠረው ጫና ወደ ጎዳና ለመውጣት እየተገደዱ ስለመሆናቸው ተጋሪ የሚፈልግ አይደለም ።
ለእነዚህ ወገኖች ክብር መስጠት፣ ክብካቤ ማድረግ እና መብቶቻቸውን መጠበቅ ግዴታ ቢሆንም፤ እነዚህ አገር ያገለገሉ የአገር ባለውለታ አረጋውያን የሚደግፋቸው አጥተው ልመና ላይ ተሰማርተው ማየቱ የተለመደ ነው፡፡
የመስራት አቅም ያላቸው ከክልል ተሰደው ወደ አዲስ አበባ የሚገቡ ወጣቶች እና ህፃናት ሌሎች የአዲስ አበባ ጎዳና ተዳዳሪዎች ናቸው፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች በመሬት ማነስ እና አንዳንዴም በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ በቂ ምርት ባለማግኘታቸው ምክንያት ተገድደው ወደ ከተማ የሚገቡ ዜጎች ቁጥር በቀላሉ የሚታይ አይደለም። እነዚህ ዜጎች ከተማ ከገቡ በኋላ የሚያግዛቸው በማጣት ለከፋ የጎዳና ሕይወት ይጋለጣሉ ። ይህንንም ተከትሎ ለልመና እጃቸውን ይዘረጋሉ፡፡
የሰው ልጅ በሕይወት አጋጣሚ በተፈጠረ ችግር ወይም ሲወለድ አብሮት በሚመጣ የአካል ጉዳት ምክንያት በዕርጅና አቅሙ ደክሞ አልያም ሰርቶ መብላት ሲሰነው ወደ ልመና ሊገባ ይችላል። ምንም እንኳ ተርፎት ለሌላው የሚያካፍለው ያለው የአገሪቱ ዜጋ ቁጥር ጥቂት ቢሆንም፣ ከሌለው ላይም ቢሆን ቆንጥሮ ከኪሱ የዕለት ጉርሱን ላጣ ምሲኪን መስጠት የኢትዮጵያውያን መለያ ነው።
ይህ በአገራችን በየትኛውም የአገሪቱ ክፍል የሚታይ የመረዳዳት ባህል ጎልቶ የሚታይ ቢሆንም ልመናን በማበረታታት በኩል እየፈጠረ ያለው አሉታዊ ተጽእኖ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ቆም ተብሎ ሊታይ የሚገባ ፤ ትኩረት የሚሻ ጉዳይ ከሆነም ውሎ አድሯል።
ከዚህ የተነሳም አቅሙ እያለ ሰርቶ መብላት የሚችለው ሳይቀር ልመናን አዋጭ ስራ አድርጎ ተቀብሎ መንቀሳቀስ ተለምዷል። የዚህ የተበላሸ አስተሳሰብ ሰለባ የሆኑ ዜጎችን በጎዳናዎች ማየት የተለመደ ክስተት ከሆነ ሰንብቷል ፡፡ የሌለባቸውን የአካል ጉዳት ያለ አስመስለው ወይም ሌሎች የተለያዩ የማጭበርበርያ መንገዶችን በመጠቀም አቅምና ጉልበት ያለቸው ሰርተው መብላት የሚችሉ ዜጎች በልመና ተሰማርተው ማየት የፋሽን ያህል ሆኗል፡፡
አንዳንዶች እንደሚሉት በልመና የሚገኝ ገንዘብ ከአብዛኛው የመንግሥት ሰራተኛ የወር ገቢ በእጅጉ የሚበልጥ ነው ፡፡ ሳይሰሩ መብላትን እንደልማድ የወሰዱ ለማኞችም ከተሞችን እያስጨነቁ ሲሆን ፤ ሁኔታዎች በዚሁ ከቀጠሉ የመጪው ጊዜ አገራዊ ስጋት/ችግር ሆነው መገኘታቸው የማይቀር ነው፡፡
ችግሩን ለዘለቄታው ለመፍታት ትክክለኛ እርዳታ ፈላጊዎችን በመለየት ተገቢውን ድጋፍ የሚያገኙበትን አሰራር መፍጠር ያስፈልጋል። ለተረጂዎች ያለ ልዩነት የሚሰጠውን ምጽዋት በተደራጀ መንገድ ለትክክለኛ የሚደርስበትን መንገድና የአሰራር ሥርዓት መፍጠር ያስፈልጋል፡፡
ሌላው ቀድሞ መከላከል ሲሆን፤ በተለይ ወደ ከተማ በሚኖር ፍልሰት ምክንያት ለጎዳና ኑሮ ተጋልጠው ሕይወታቸው አደጋ ላይ የሚወድቁ እና ወደ ልመና የሚገቡ ዜጎችን ቁጥር ለመቀነስ በዛው የመኖሪያ አካባቢያቸው ኑሯቸው የሚሻሻልበት ሁኔታ ላይ መሥራት ያስፈልጋል፡፡
ከሶስት ዓመት በፊት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የጎዳና ላይ ኑሮና ልመናን በሕግ እስከመከልከል የሚደርስ እርምጃ እንደሚወስድ አሳውቆ ነበር፡፡ የቀድሞ የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ በወቅቱ ሲናገሩ በአዲስ አበባ ከየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል መጥቶ ሰርቶ መኖር ይቻላል። ጎዳና ላይ ግን መኖርም ሆነ መለመን የማይቻልበት ሁኔታ እንዲፈጠር ለመስራት እንገደዳለን ብለው ነበር፡፡
ምንም እንኳ በሕግ ደረጃ ይህን ማድረግ እና ማስፈፀም ቢያዳግትም፤ ሰርተው ራሳቸውን መቻል ብቻ ሳይሆን መለወጥ የሚችሉ ዜጎች ልመና ላይ ሆነው አካላቸውን እና ሥነልቦናቸውን እንዳያደቁ የሚታገዙበትን ሥርዓት ማበጀት ያስፈልጋል፡፡
ልመናን ማስቆም ባይቻል እንኳን ለመቀነስ ከመንግሥት ባሻገር የሁላችንም ትብብር ያስፈልጋል፤ በተና ጥል ከመስጠት ይልቅ በመንግሥት አሰራር በመዘርጋት ጎደና ላይ የወጡ ወገኖችን በዘላቂነት መርዳት /ሕይወታቸውን መቀየር ይገባል፡፡
ከዚሁ ችግር ጋር በተያያዘ በከተማዋ ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥሩ እየጨመረ የመጣውን የጎዳና ልመና ለመቀነስ በቅርቡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አበቤ የሴቶች የተሃድሶና መልሶ ማቋቋሚያ ማዕከል ግንባታ አስጀምረዋል፡፡
ኑሯቸውን በጎዳና ላይ ያደረጉና በወሲብ ንግድ ስራ የሚተዳደሩ ሴቶችን በማሰባሰብ በማዕከሉ የተለያዩ የማገገሚያ መረሃ ግብሮች እንዲያርፉ በማድረግ ሕይወታ ቸውን የሚለውጡበትና ክህሎት የሚቀስሙበት ማዕከል ቢሆንም ሕይወታቸውን በአስከፊ ሁኔታ ጎዳና ላይ ላደረጉ ሴቶች ፋይዳው የጎላና ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡
ችግሩን ለዘለቄታ ለመፍታት ግን ከሁሉም በላይ መንግሥት የአገር ውስጥ ፍልሰት በብዛት በሚታይባቸው የአገሪቱ አካባቢዎች ሰፊ የሰው ሃይል ቀጥረው ማሰራት የሚችሉ የኢንዱስትር ፓርኮችና መሰል ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ ችግሩን ለመከላከል መስራት ይጠበቅበታል። ይህን ስር የሰደደ ማህበራዊ ቀውስ ለመፍታት ነገ ዛሬ ሳይባል መረባረብና ከቃላት ያለፈ ተግባራዊ እርምጃ መውሰድ የሁሉንም ባላድርሻ አካላት ርብርብ ይጠይቃል። ሰላም!
ክብረአብ በላቸው
አዲስ ዘመን ጥር 14 ቀን 2015 ዓ.ም