የኢትዮጵያ ሕዝብ ጥበበኛ ሕዝብ ነው፤ ጥበቡ ይገርመኛል። ማስተዋል እና ምሳሌው ያስደንቀኛል። ነገሮችን፣ አጋጣሚዎችን፣ ሁኔታዎችን በምሳሌያዊ ንግግር ሲገልጽ ሳይንስን የሚያስንቅ ጥበብ አለው። ከዚህ ምሳሌያዊ ንግግሩ መካከል ለሙሰኛ ባለሥልጣን የሚመጥን አንድ አባባል መዘዝኩ፤ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይበቀል የሚል” አህያዊ አባባል። ይሄ አባባል አህያን ከግብሯ ለማሳነስ የተነገረ አይደለም፤ ይልቁንም በአባባል ሂደቷ ላይ ተመሥርቶ የሚታይባትን ባሕሪ ያገናዘበ ገለጻ እንጂ፤ እኔም ይሄን የራስ ወዳዶች ስሜት ለሙሰኛ ባለሥልጣናትና ላልተገባ ተግባራቸው ስጠቀምበት ሀሳቤን በትክክል ይገልጽልኛል ብዬ በማሰብ ነው፡፡
ሙሰኞችን በአንድ ቃል ግለጽልኝ ብትሉኝ ከአህያ ጋር አዛምዳቸዋለሁ። አህያ ሰርዶ ስትግጥ ለነገ የሚል እሳቤ የላትም። ምክንያቱም ለነገ ማቆጥቆጥ እንዳይችል ጭምር አድርጋ ሥሩን ነቅላ ትበላለችና ነው። በዚህም ለሚመጣው ትውልድ ርህራሄን አጥታ ሰርዶ እንዳይበቅል፣ ግጦሽ እንዳይለማ የምታስብና አሁናዊ ራሷን ብቻ የምትሻ እንስሳ ሆና በአባባሉ ላይ ቀርባለች። አህያ ራስ ወዳድና ለእኔ ብቻ የምትል ሆና ተስላ በሥነ ቃሉ ላይ ቀርባለች። በአህያ ልብ ውስጥ ለነገ የሚል ማስተዋል የለም፤ በአህያ ልብ ውስጥ ርህራሄ የለም። ለሌሎች ማሰብና፣ ለሌሎች መኖር የለም። ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ የራሷ ብቻ ናት። ይሄን እውነት ወደ ሙሰኛ ባለሥልጣናትና ወደ ግብራበሮቻቸው ስናመጣው ከአህያ ግብር ጋር አንድ ሆኖ እናገኘዋለን።
ሙሰኞች ለመጪው ትውልድ የሚያስብ ከእኔነት የተረፈ አስተሳሰብ የላቸውም። ልክ እንደ አህያና እንደ አስተሳሰቧ ስለሚግጡት ሳር፣ ስለሚያግበሰብሱት ሃብት ብቻ ነው የሚያስቡት። በማንነታቸው ውስጥ ሰውኛ ባሕሪ የለም። ለሚመጣው ትውልድም ሆነ ላለው ትውልድ የሚሆን ቅንጣት ርህራሄ ያልፈጠረባቸው ከእኔነትና ከብቻ እሳቤ ያልተላቀቀ እንስሳዊ ተፈጥሮ ያላቸው ናቸው። ማን ወደ ሥልጣን እንዳመጣቸው፣ ለምን እንደመጡ፣ መጥተውስ ምን እንደሚሠሩ ያውቃሉ ቢባል እንኳን፤ እነሱ ግን በዛ እውነት ውስጥ አይደሉም። ሙሰኞች ወደ ሥልጣን ያመጣቸውን ድሀ ሕዝብ በመጠቀም ራሳቸውን በመጥቀም ሥራ ላይ የተጠመዱ ናቸው። ማኅበረሰብ ለማገልገል የሚሆን የሞራል ልዕልና የላቸውም። ለዚም ነው በመስረቅና በመዋሸት፣ በመስጠትና በመቀበል ሕገ ወጥ ድርጊት ውስጥ የሚሳተፉት፡፡
ሙሰኞች ከኢትዮጵያ አብራክ የበቀሉ ናቸው። ኢትዮጵያ ሀገራችን ይጦሩኛል ብላ በችግር ያሳደገቻቸው፣ አስተምራ ለቁም ነገር ያበቃቻቸው ናቸው። ከየትም አልመጡም፤ የበቀሉት ከማኅበረሰቡ ውስጥ ነው። እያሰቃዩ ያሉትም ማኅበረሰቡን ነው። እኩይ ድርጊታቸውን የተለማመዱበት መንገድ ይለያይ እንጂ ማኅበረሰቡ ወልዶ ያሳደጋቸው ናቸው። የሚገቱትም በማኅበረሰቡ ነው። በመሆኑም ማኅበረሰቡ እነዚህን የአገልጋይነት ዓላማ የሌላቸውን ሙሰኞች እያጋለጠ እንስሳዊ ድርጊታቸውን መግታት አለበት። ከድሀ እናት መቀነት በተከፈለ ገንዘብ ተምረውና ለቁም ነገር በቅተው በድህነት ያስተማረቻቸውን ሀገራቸውን መዝረፍ በየትኛውም መስፈርት ቢታይ ዛሬን ብቻ በልቶ የማደር ለነገ ያለማለት የአህያዋ አይነት እሳቤ ነው። ይሄ ድርጊት እንዲቆም ከራስ አልፎ ለትውልድ የሚበቃ፣ ከዛም የራቀ ዓለም አቀፍ አስተሳሰብን መውረስ ያስፈልጋል።
ሙሰኞች በድርጊታቸው ብቻ አይደለም በባሕሪያቸውም ነውረኞች ናቸው። ሀገራቸውን ሊውጡ የተሰናዱ ደራጎኖች ናቸው። በሕዝብ ላብ፣ በወገን እንባ ራሳቸውን ፈጥረው ያሳደጉ፣ በሀገር ሀብት፣ በሕዝብ ጥሪት የራሳቸውን ሆድ ብቻ የሚሞሉ ስግብግቦች ናቸው። አረመኔነት መልክ ቢኖረው፣ አህያነት ስም ቢኖረው እነሱን ይሆን ነበር። እውነት ለመናገር ሙሰኞች በተግባራቸው እጅግ የዘቀጡ በሀገርና ሕዝብ ላይ ያመጹ ናቸው። ግብራቸው ከየትኛውም መጥፎ ነገር ጋር የማይነጻጸር ነው። በብዙ ነገራቸው ሀገራቸውን ጎድተዋል። ሥልጣናቸውን ተጠቅመው በሀገር ላይ ያደረሱት በደል እንዲህ በቀላሉ የሚታይ አይደለም። እንዳውም በተግባራቸው የአህያን ያክል ግልጋሎት አልሰጡም። ከኦሪት እስከ አዲስ ከዛም አልፎ እስከ አለንበት ጊዜ ድረስ አህያ በታማኝነት ስታገለግለን ኖራለች። ሙሰኞች ግን ከመስረቅና ከመዝረፍ የዘለለ ታሪክ የላቸውም፡፡
ሙሰኞች ሁልጊዜም አንድ ዓይነት ናቸው። አጋጣሚ ባገኙ ቁጥር ከመስረቅ ወደኋላ አይሉም። ለኢትዮጵያ እድገትና ብልጽግና ከለፉት ይልቅ ያጠፉት ይበልጣል። ‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል’ አለች አህያ የሚለው ተረት ሙሰኞችን በደንብ ስለሚገልጻቸው ‹እኛ ከሞትን ሀገር
ትውደም’ አሉ ሙሰኞች በሚል ቢስተካከል ደስ ይለኛል። ምክንያቱም አሁን ላይ ለሀገራችን ጉስቁልናና ኋላቀርነት እየሠሩ ያሉት እነሱ ስለሆኑ። ራሳቸውን ለሀገር ሳይሆን ሀገርን ለራሳቸው አመቻችተው የተቀመጡ ናቸው። በትረ ሥልጣናቸውን ለሀገር ክብር አልተጠቀሙበትም። እየሰረቁና እያሰረቁ በሌብነት ሀሳብ ውስጥ ከድጡ ወደማጡ የሚዋዥቁ ናቸው። ለራሳቸው ባመቻቹዋት ሀገር ላይ፣ ለራሳቸው ባመቻቹት ማኅበረሰብ ላይ አዲስ ነገር መፍጠር አቅቷቸው እኩይ ድርጊታቸውን ለመሸፋፈንና በሌላው ላይ ለመላከክ የሚያደርጉት ድርጊታቸው ሌላ በመጥፎ የሚነሳ ግብራቸው ነው።
እነሱ ማለት የሀገርና የታሪክ የትውልድም ጠንቅ ናቸው። በሥልጣናቸው ተጠቅመውም በሙስና ተግባራቸው የሀገራችንን ተስፋ፣ የትውልዱን ደስታ እያበላሹ ነው። ዕውቀታቸው ተጀምሮ የሚያልቀው በመስረቅ ነው። ሌባ ለአመሉ ዳቦ ይልሳል እንዲሉ፤ ሁሌም በመስረቅ ተግባር ውስጥ ናቸው። እስኪበቃቸው ሰርቀው አልበቃቸውም። ወደፊት እንዴትና ምን እንደሚሰርቁ በማሰብ ከግብረአበሮቻቸው ጋር በመምከር ጊዜ የሚያጠፉ ናቸው። በዚህ በእነሱ ሀሳብ ውስጥ ኢትዮጵያ የለችም፤ በዚህ ሀሳባቸው ውስጥ ትውልድ አይገነባም። ይልቁንም ይሄ ሀሳብ የሀገርን ተስፋ የሚያደበዝዝ ጅምላ ጨራሽ መርዘኛ ሀሳብ ነው። ተባብረን ልናስቆመው ይገባል። የፀረ-ሙስና ኮሚሽንም ከወትሮው በተለየ መንገድ በዚህ ላይ መስራት አለበት። መንግሥትም የተለያ አመራር በመስጠት እንደነዚህ አይነቶቹን ሀገር ሻጪ ሌባና ባንዳዎች ሊቆጣጠር ይገባል።
ሙሰኞች ለሀገር በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ናቸው። ሀገራችን በብዙ ችግር ተከባ ባለችበት በዚህና በዚያ ዘመን እነሱ ነበሩ። አሁንም ለሀገራችን ተጨማሪ ችግር ሆነው አሉ። መፍትሔ ሊያገኙ ይገባል። በብዙ ሀገራዊ ችግሮች ላይ ጆሮ ደግፍን የሚያክል ችግር ተጨምሮብን ይቅርና ወትሮም ኢኮኖሚያችን በመንገዳገድ ላይ ያለ ነን። እንኳንስ ዘንቦብሽ የሚለውን ታሪክ እየተረክን ዝም ማለት ሳይሆን ለችግሮቻችን መፍትሔ በመስጠት ላይ ማተኮር ይኖርብናል፡፡
ሀገር በሙሰኞች ስትበዘበዝ ማር የሌለው ቀፎ ናት። ሕዝብ ደግሞ ማር ይጠብቃል፤ ማሩ ግን ለሆዳቸው ባደሩ ስግብግቦች ይበላል። ሙሰኞችን ከወዲሁ አደብ ማስያዝ ካልተቻለም የሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታ እንዲህ እየሆነ ነው። ማሩ ወደ ሕዝብ መድረስ አለበት። ባለሥልጣኖቻችን የማሩ ጠባቂ እንጂ ማሩን ቆርጠው የሚበሉና ወደቤታቸው ብቻ የሚወስዱ አይደሉም። የማሩ ባለቤት ሕዝብ ነው። ሕዝብ ባለሥልጣኖችን የሾመው የማሩ ቆራጭ ሆነው አብዝተውና አትረፍርፈው እንዲሰጡት እንጂ በውሸት ዜና ቀፏችን ማር አልያዘም ብለው እንዲያረዱት አይደለም፡፡
በታማኝ ባለሥልጣኖች ማር ያለበት ቀፎ ያስፈልገናል። ሀገራችን ማር ይዛ ሕዝቦች በጋራ እንዲበሉ የሚያስችል ኢኮኖሚያዊ ሥርዓት ያስፈልጋል። ማሯ በጥቂት ግለሰቦች የሚበላባት ሀገር ሊኖረን አይገባም። በታማኝነትና በቅንነት ሕዝብን ያስቀደመ አሠራር ያስፈልጋል። ሕዝብ አበባ እየተከለ፤ ለንቦች የሚመች ስፍራ እየፈጠረ ማሩ ግን በስግብግብ ሙሰኛ ባለስልጣን የሚቆረጥ መሆን የለበትም። ተቆርጦ ወደ ሕዝብ ቢደርስ ጥሩ ነው። እናም ሕዝብ ይቅደም፤ ሥልጣን ሕዝብ ማገልገያ ነውና፡፡
በሙሰኛ ባለስልጣኖች እንጀራ የሌለው ሌማት አንፈልግም። ባዶ ሌማት ምን ይሠራልናል? እንዲያበሉን እንጂ የሾምናቸው እንድናበላቸው አይደለም። ከድህነት እንዲያወጡን እንጂ በድህነታችን ላይ እንዲቆምሩ አይደለም። መስኮት አልባ ቤት ምን ያደርግልናል? እኛ የምንፈልገው በመተማመን ላይ የተመሠረተ ፖለቲካና ፖለቲከኛ ነው። አሠሪና ሠራተኛ ነው። ባለጉዳይና ባለሥልጣን ነው። ጥቂቶች ጠግበው ብዙኃኑ የተራበባት ሀገር ልትኖረን አይገባም። በእኔነት መንፈስ ተሰልበው ራሳቸውንና በዙሪያቸው ያሉን የሚጠቅሙ ሙሰኛ ጥቅመኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ተጠያቂ እንዲሆኑ የሚያደርግ አሠራር ያስፈልጋል። ሀገራችን ከዚህ ውጪ የሚበጃት የለም። በኢትዮጵያ ተስፋ ላይ ለሚመጡ የማያዳግም እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል። ለሌላው ማስተማሪያ የሚሆን ፍርድ ያስፈልጋል። በእኛ ይብቃ..እኛን ያየ ይቀጣ ብሎ የሚናገር ዘመን ተሻጋሪ የወንጀለኛ መቅጫ ሕግ ሊረቅ ይገባል።
በኢትዮጵያ ምድር የሙሰኞቻችን ግብር ከእንስሳ ግብር ያነሰ ነው። በዚህና በመሰለው ተግባራቸው ‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል’ አሉ ከማለት ውጪ ምን ሊባሉ ይችላሉ? በሥልጣን ስም እዛም እዚም የተሰገሰጉ እንሰሳዊ ባሕሪን የሚያራምዱ ነውረኞች መታረም አለባቸው። ከትላንት እስከዛሬ በሙሰኞች የግፍ በትር ያልተመታ ኢትዮጵያዊ የለም። ዛሬም እንደትላንቱ ሀገራችን በነዚህ ግለሰቦች እየተቦጠቦጠች ነው። ይበቃል የሚል ድምጽ ከመንግሥትም ከእኛም ሊሰማ ይገባል፡፡
ታማኝነት ኢትዮጵያን የማፍቀር ምልክት ነው። አንድን ሰው ከልባችን ስንወደው ነው እምነታችንን የምንሰጠው። እነኚህ ግለሰቦች ኢትዮጵያን ስለማይወዷት ሊታመኑላት አልቻሉም። ሕዝቡን ስለማያከብሩት በታማኝነት ሊያገለግሉት አልቻሉም። ሀገራችን መታመንን በማያውቁ፣ ፍቅርን በማያውቁ ሌባና ራስወዳድ ባለስልጣናት ልትመራ አይገባትም። ከምንም በፊት ታማኝነትን መማር አለባቸው፤ መቀበልን ሳይሆን መስጠትን መልመድ አለባቸው፡፡
ሙሰኞች ኢትዮጵያን ቢወዷት ኖሮ በዚህ ልክ ባልጎዷት ነበር። ሕዝባቸውን ቢያከብሩት በዚህ ልክ ባልዋሹት ነበር። ኢትዮጵያ ለስግብግብ ባለስልጣናት ምንድን ናት? እንዴትም ብናየው ምንም አይደለችም። ጥቅማቸውን የሚያስጠብቁባት ሀገር እንጂ የሚሞቱላት እንዳይደለች ከእኩይ ከተግባራቸው መረዳት እንችላለን። የአውሬአዊ ማንነታቸው መደበቂያ እንጂ መድመቂያቸው አላደረጓትም። አዕምሮ የሚደምቀው ሀገርን ሲያደምቅ ነው። ማኅበረሰብን ሲያገለግል ነው። እነሱ ግን በሀገር ለመድመቅ እንጂ ሀገር በነሱ እንድትደምቅ አላደረጉም። ክብራቸውና ደስታቸው ሰርቆ በመብላት የሚመነዘር ነው። እውነትና ፍርሃት በነፍሳቸው ውስጥ የለም። አነዚህን ወንበዴዎች መታገል አለብን። መታገል ብቻ አይደለም እስኪወድቁ ድረስ፣ ዳግም መነሳት እስኪያቅታቸው ድረስ ልንታገላቸው ይገባል። ከነአስተሳሰባቸው፣ ከነሌብነታቸው፣ ከነድርጊታቸው እንዲቀበሩ ማድረግ አለብን፡፡
እኔ እስከማውቀው ድረስ የሀገር ፍቅር በተግባር ነው የሚገለጸው። ሀገር መውደድ ውስጥ እኔነት የለም። ሀገር መውደድ ውስጥ በጎ ሀሳብ እንጂ እንደ አህያ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል የሚል ፈሊጥ አይነገርም። ለሀገር የሚለፉ እነሱ የተባረኩ ናቸው። ለሀገር የሚለፉ አንድ ቀን በትውልዱ እንደሚከብሩ ስነግራችሁ ከልቤ ነው። አባቶቻችን ለሀገርና ለነጻነት በከፈሉት ዋጋ እያመሰገናቸው ነው። በዓድዋና በአንባላጌ፣ በካራማራና፣ በኦጋዴን ለሀገርና ለታሪካቸው ሲሉ በከፈሉት የሕይወት መስዋዕት ትውልድ እየዘከራቸው ነው። እንደ ሙሰኞች ያሉ በሀገርና በታሪክ ላይ መጥፎ አሻራ የሚያስቀምጡ እነሱ እነሱ ከኢትዮጵያ ማህጸን የሚፋቁበት ጊዜ ሩቅ አይሆንም፡፡
ሀገር መልካም ነፍስ ትሻለች። ሀገር መልካም ልብ ግድ ይላታል። መልካም ነፍሶች ለሌላው የሚሆን ደስታ እንጂ ስቃይ የላቸውም። መልካም ልቦች ለሌሎች የሚሆን እውነት እንጂ ሐሰት አይኖራቸውም። አሁን ጊዜው በተባበረ ክንድ ኢትዮጵያን ወደ ፊት የምናሻግርበት ነው። ከእኔነት ወጥተን ወደ ሕዝባዊነት የምንሸጋገርበት የተሐድሶ ምዕራፍ ነው። አሁን ጊዜው እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል የምንልበት ሳይሆን በኔ መኖር ሌሎች እንዲኖሩ የምፈቅድበት ጊዜ ነው፡፡
አሁን ጊዜው በእኛ ፍቅር፣ በእኛ አንድነት፣ በእኛ ታማኝነት የልጆቻችንን ኢትዮጵያ የምንገነባበት እንጂ እንደ ሌባ ባለሥልጣን እየሰረቅንና እያሰረቅን በራስ ወዳድነት ሀገርና ታሪክ የምናወድምበት አይደለም። አሁን ጊዜው ለውጥ ከናፈቁ ሕዝቦች ጋር ወደ ፊት የምንልበት እንጂ ከሕዝብ የምንሰርቅበት አይደለም። ይሄ ጊዜ ከሌብነት አስተሳሰብ ተላቀን መልካም ሀገርና መልካም ትውልድ የምንገነባበት የመተማመን ጊዜ ነው። ይሄ ጊዜ ከመቼውም ጊዜ በላይ ኢትዮጵያን የምናገለግልበት፣ ሕዝባችንን የምንጠቅምበት የመነሳት ጊዜ እንጂ አጋጣሚዎች በተመቻቹልን ቁጥር የምንዋሽበት አይደለም፡፡
በሀገር ጉዳይ ላይ የድርሻችንን እንወጣ። በሀገር ጉዳይ ላይ ሁላችንም ያገባናል፤ መንግሥት ብቻ አይደለም፣ ሕዝብ ብቻ አይደለም፣ ጥቂት ለአገርና ሕዝብ የሚለፉት ባለስልጣናትም ጉዳይ ብቻ አይደለም። ሁላችንም ለሀገራችን ስፍራ አለን። በሀገር ጉዳይ ላይ የሚመለከተው የሚባል ነገር የለም። ሁላችንም ስለሀገራችን ይመለከተናል። ሁላችንም ስለሕዝባችን ያገባናል። ለሀገር ነቀርሳ የሆኑ ሙሰኞችንም የምንዋጋቸው በአንድነት ስሜት ነው፡፡
ማንም ይበለው ‹እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል..አደገኛ አባባል ነው። ሀገር የሚያወድም..ትውልድ የሚመርዝ። ቃላት ምን ያክል ገላጭና ተጽዕኖ እንዳላቸው ለማወቅ ይሄን አባባል ማየቱ በቂ ነው። እንደ ሀገርም ሆነ እንደ ግለሰብም ይሄን አባባል የሚሽር ሰብዕና ያስፈልገናል ባይ ነን። ምክንያቱም አሁን ላይ ሁላችንም ኢትዮጵያን በመፍጠር ሀሳብ ላይ ስለሆንን። አዲስ ሀገር በአዲስ አስተሳሰብ የምትፈጠር ናት። አዲስ ሀሳብ ከሌለን አዲስ ነገር አይኖረንም፣ የጥንቱን ስርዓት አራማጅ ነው የምንሆነው፡፡
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ጥር 9 ቀን 2015 ዓ.ም