ኢ ይቀመጣል እንደ አደራ
ሰው ክፉም ደግም ሰራ
ሁሉም የእጁን ያገኘዋል..
ቢቆይ እንጂ መች ይቀራል..
ለዛሬው በእነዚህ የሙዚቃ ግጥም ስንኞች የጽሁፌን ሃሳብ ጀምሬአለው። በዚህ መጀመሬም ያለ ምክንያት አይደለም፤ ይልቁንም በአገራችን ላይ የምንሆነው ነገር ሁሉ እንደ አደራ የሚቀመጥ ስለሆነ ያንኑ ለመጠየቅ እንጂ። በጎ ከሰራን የበጎ ስራችንን ውጤት ልጆቻችንና የልጅ ልጆቻችን ይበሉታል። ክፉ ከሰራን ደግሞ እንዲሁ የክፋታችንን ውጤት ማንም አይወስድብንም። ለምሳሌ፣ ዛሬ ላይ ተነጋግረን ያልተግባባንባቸው ወደ ጦርነትና ወደአላስፈላጊ ነገር እየወሰዱን ያሉ ችግሮች ትላንትና በቀና ልብ ያላደረግናቸው ነገሮች ናቸው። ዛሬ ላይ እየበላን ያለነው የትላንት የእጅ ስራ ፍሬአችንን እንደሆነ ከልቤ ለመናገር እወዳለሁ።
በመሆኑም ፍሬአችን ሞት የሌለበት የህይወት፣ የተድላ፣ የሰላም ፍሬ እንዲሆን ዛሬ ላይ መልካም ዘርን መዝራት ይኖርብናል። መልካም ዘር መልካም ፍሬን ነው የሚያፈራው። መልካም ፍሬ ደግሞ የሰላምና የደስታ አብራክ ነው። የእድገትና የብልጽግና፣ የአንድነትና የመቻቻል ስፍራ ነው። ሰላምና ደስታ፣ እድገትና ብልጽግና፣ አንድነትና መቻቻል ደግሞ ለየትኛውም አገር፣ ለየትኛውም ህዝብ፣ ለየትኛውም አስተሳሰብ የመጨረሻው ግብ ነው።
ምክንያቱም አገር አስተሳሰብ ናት፤ አገር የቀና ልብ፣ የቀና አእምሮ ጽንስ ውጤት ናት። አገር በዜጎች በጎ ማህጸን ተምጣ የምትወለድ ከትውልድ ትውልድ የምትተላለፍ የጋራ ስማችን ናት። አገራችንን ለመውለድ አገር የሚያረግዝ፣ ትውልድ የሚጸንስ ብቁና ምቹ ልብና አእምሮ ያስፈልገናል። ብቁና ምቹ የሆነ ልብና አእምሮ በመነጋገር የተገነባ፣ በመቻቻል የተሰራ ነው። የሀሳብ የበላይነትን የሚያራምድ፣ አገርና ህዝብን መሰረት ያደረገ ነው። ብቁና ምቹ ልብና አእምሮ ጦርነትን ለምንም ነገር መፍትሄ ያላደረገ፣ በእውቀትና በምክክር አገር እንደሚገነባ የተረዳ ነው። ብቁና ምቹ ባልሆነ ልብና አእምሮ የምትጸንስ አገር ለዜጎቿ የስቃይ ምንጭ ናት። ለምንም ነገር ጦርነትን መፍትሄ አድርጋ የምትኖር ናት። በወንድማማች ሞት ማትረፍን የምትመርጥ ናት። ተነጋግሮ መግባባት፣ ተግባባቶ አብሮ መቆም አይቻላትም። ብቁና ምቹ ባልሆነ ልብና አእምሮ የሚፈጠር ማህበረሰብ ችግር ፈቺ ከመሆን ይልቅ ችግር ፈጣሪ የመሆን እድሉ የሰፋ ነው። እናም አገራችንን ሀሳብ ባለው፣ እውቀት ባለው፣ ጥበብ ባለው፣ አንድነት ባለው፣ ተግባቦት ባለው፣ ይቅርታ ባለው አእምሮና ልብ ጸንሰን ልንወልዳት ይገባል።
አገር በዜጎቿ ተተክላ በዜጎቿ የምትጸድቅ ናት። በዜጎቿ ተተክላ በዜጎቿ ያልጸደቀች አገር በታሪክ የለችም። ሁሉም አገራት በዜጎቻቸው የተሰሩ ናቸው። አገር ለመስራት የመጀመሪያው ግብዐት አንድነት ነው። ከዛ መቻቻልና ወንድማማችነት ይመጣሉ። የሀሳብ የበላይነትና ተነጋግሮ መግባባት ይከተላሉ። በመጨረሻም የአንድነት አገር፣ የመቻቻልና የምክክር አገር እንፈጥራለን። በዚህ ውስጥ ያለፈች አገር ለዜጎቿ ሁሉንም ናት። ይቺን አገር መፍጠር ነው ያቃተን።
ሆኖም ይቺን አገር መፍጠር ነው ህልማችን። ይቺ ኢትዮጵያ የእኛ እንድትሆን ነው ምኞታችን። ግን በሚፈለገው መጠን እየሮጥን አይደለም። የምንፈልጋትን ኢትዮጵያ ለመፍጠር የሚያስችል የሀሳብ የበላይነትና ተነጋግሮ የመግባባት ጥበብ ይጎለናል። እናም ራሳችንን እናድስ፤ ለምንፈልጋት ኢትዮጵያ የሚሆን አስፈላጊ እውቀትና ተግባቦት ያስፈልገናል። ለምንፈልገው ሰላም፣ ለምንፈልገው ስልጣኔ የሚሆን ጊዜውን የዋጀ አስተሳሰብ ያሻናል። ራሳችንን ለአዲሷ ኢትዮጵያ ምቹ እናድርግ።
በድሮ በሬ ያረሰ የለም፤ ድሮነት አሁን ላይ ዋጋ አጥቷል። ዛሬ የሰላም ስፍራው መቻቻል ብቻ ነው። ዛሬ የስልጣኔ ስፍራው መነጋገር ብቻ ነው። እኛ ደግሞ በሀሳብ በልጽጋ ትውልድ የሚጠለልባት፣ ትውልድ የሚኮራባት ዋርካ የሆነች አገር ታስፈልገናለች። በጋራ ሀሳብ፣ በጋራ እውነት የጸናች አገር ታስፈልገናለች። ታሪክ የሚጻፈው፣ ማንነት የሚገነባው፣ ስልጣኔና ብልጽግና የሚመጣው በጸደቀች አገር ላይ እንጂ በጠወለገች አገር ላይ አይደለም። አገራችን እንዳትጠወልግ የሚያስፈልጋትን ልንሰጣት፣ እንደምትፈልገው ልንሆንላት ይገባል። አገራችን እንዳትጠወልግ የሰላም ባለቤቶች ልንሆን ይገባል።
ምክንያቱም አገር የምትጠወልገው በጦርነት ነው። አገር የምትጠወልገው ነውጥ ባነገበ ኢ-ምክንያታዊ ሀሳብ ነው። እኛም በሰሜኑ ጦርነት ብዙ ቦታ ላይ ጠውልገናል። በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካ፣ በጤናው፣ በትምህርቱ ዘርፍ ጠውልገናል። እንደ አገር፣ እንደ ዜጋ ጠውልገናል። ጦርነት ያጠወልጋል..አለመነጋገር፣ ተነጋግሮ አለመግባባት ያጠወልጋል። የይቅርታ ልብ ማጣት፣ የሰላም ሀሳብ ማጣት ያጠወልጋል። መግደል መሞት ያጠወልጋል..ስንሞትና ስንገል እኛ ብቻ አይደለንም የምንሞተውና የምንገለው..በእኛ መሞት ውስጥ፣ በእኛ መግደል ውስጥ የሚሞቱና የሚከስሩ ብዙ ነገሮች አሉን። ትንሳኤአችን ሰላም ነው..ሞትን የምንገልበት ጥበባችን ደግሞ ሰላም ነው። ስለዚህ በቀና ልብ ለሰላም እንልፋ። ለሰላም የሚለፉ ነፍሶች ደግሞ እዳ የለባቸውም።
የአገር ፍቅር ከሚገለጽባቸው መንገዶች ውስጥ ቀዳሚው ለሰላማዊ አገር ሰላማዊ ሀሳብ ማዋጣት ነው። ለአገራችን ምርጡን እናዋጣ። ሰላም ያለበት ሀሳብ፣ ሰላም ያለበት ምክክር፣ ሰላም ያለበት ጉርብትና፣ ሰላም ያለበት ፖለቲካ ሁሉ ምርጥ ስጦታ ነው። እንደ ዜጋም ሆነ እንደመንግስት ለአገራችን ልናደርገው የሚገባው ነገር ይሄ ነው። አገር በቀና አስተሳሰብ ስትመራ ቀና ትውልድ ነው የሚፈጠረው። የቀና ትውልድ እድሉ ደግሞ ከመልካም ነገር ያልጎደለ ነው። ስልጣን የምንፈልገው፣ አለቅነትን የምንመኘው እንደ ሙሴ የድህነትን ባህር ከፍሎ፣ የኋላ ቀርነትን ቀንበር ሰብሮ ህዝብን ለማሻገር ካልሆነ ተጠያቂዎች ነን። ፖለቲከኛ የሆንው ዋሽተንና አስመስለን አገራችንን ለማዋረድ ከሆነ ተጠያቂዎች ነን። ዛሬ በምንሰራው መጥፎ ስራ የሆነ ቦታ ላይ ትውልድ ይጠይቀናል። የሆነ ቦታ ላይ ትውልድ ጣቱን ይቀስርብናል። የሆነ ጊዜ ላይ ታሪክ በመጥፎ ያወሳናል።
በእኛ ዘመን ለመጪው ትውልድ በጎ ነገር መስራት ግዴታችን ነው። በጊዜአችን ላይ ኢትዮጵያ የምትፈልገው ሰው መሆን አለብን። አገር ቅብብሎሽ ናት። ከአባቶቻችን የተቀበልነው ብዙ ነገር አለ። ለልጆቻችን የምንሰጠውም ብዙ ነገር አለ። በዚህ የቅብብሎሽ ሂደት ውስጥ ነው አገር የምትፈጠረው። ለልጆቻችን ምን እየሰጠን ነው? ለትውልዱ ምን እየሰራን ነው? እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል በሚል አስተሳሰብ አገር አትፈጠርም። እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል የሚል እሳቤ አገር የሚያጠወልግ፣ ትውልድ የሚያወድም እጅግ አደገኛ እሳቤ ነው።
አገር የምትለመልመው እኔ ለሚመጣው ትውልድ፣ የሚመጣውም ትውልድ ቀጥሎ ለሚመጣው ስናስብ ነው። እውነት ለመናገር ይሄን አመክንዮ በተመለከተ የሚያስቀኑኝ የውጪ አገራት አሉ። ለምሳሌ፣ አሜሪካውያን እና ቻይናውያን ያስቀኑኛል። ዛሬ ላይ ሆነው ከመቶ አመት በኋላ ለሚፈጠረው ለማይታወቀውና ለአዲሱ ትውልድ የሚሆን ብዙ ነገር አዘጋጅተዋል። እጅግ ለራቀው ከብዙ መቶ አመት በኋላ ለሚፈጠረው ትውልድ የሚሆን የክብርና የኩራት ስራዎችን አስቀምጠዋል። እኛስ ለሚመጣው ትውልድ ምን አይነት አገርን ለማስረከብ ነው እየሰራን ያለነው? ይሄ ጥያቄ የሁላችንም ጥያቄ ነው።
ለልጆቻችን በምንሰጠው ነገር ላይ ነው መጪው ተስፋችን ያለው። ለልጆቻችን በምናደርገው ነገር ላይ ነው ተስፋዎቻችን የተቋጠሩት። አሁን ላይ እየሆንን ባለነው ነገር ነው ኢትዮጵያ የምትፈጠረው። ማንም አይመጣልንም፤ የአገራችን ፈጣሪዎች እኛ ነን። የሰላማችን ባለቤቶች እኛ ነን። ለሌሎች በሚተርፍ በጎ ስራ እንጂ ለሌሎች በሚተርፍ መጥፎ ስራ አገር አትቆምም። ያለፈው አልፏል አሁን ላለችው ኢትዮጵያና ትውልድ ግን ኃላፊነት አለብን። አገር ዛሬ ብቻ አይደለችም። ትውልድ አሁን ብቻ አይደለም። ከእኛ የራቀ፣ ከእኛ ቀጥሎ የሚመጣ አዲስ ትውልድ እንዳለ በማሰብ የምናደርጋቸውን ነገሮች በኃላፊነት ማድረግ ለኢትዮጵያ ውለታ መዋል ነው። በሀሳብ የተገነባ በእውቀት የታጀበ የተሰራ ትውልድ ያስፈልገናል። የተሰራ ትውልድ አገር አይጎዳም፣ ታሪክ አያበላሽም። የተሰራ ትውልድ ለሰላም ሁሉንም ይከፍላል። የተሰራ ትውልድ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል አይልም። ለመጪው ትውልድ የሚሆን መልካም ስራን ያዘጋጃል እንጂ።
የትውልዱ ሰሪዎች እኛ ነን። ትውልድ በጥሩ ስነ ምግባር፣ በፈርሀ እግዚአብሄር የሚሰራ ነው። ትውልድ ስልጣንን በአግባቡ በመጠቀም፣ ለሰላም ዋጋ በመክፈል የሚሰራ ነው። ትውልድ በሀሳብ የበላይነት የሚሰራ ነው። በፍቅርና በይቅርታ፣ በመነጋገርና በመቻቻል የሚሰራ ነው። ትውልድ በእውቀት የሚበጅ ነው። ዛሬ ላይ በምንሆነው መሆን ውስጥ መጪውን ትውልድ እየፈጠርነው ነው። ልጆቻችን ጉያችን ውስጥ ሆነው ከእኛ ብዙ እየተማሩ ናቸው። የነገዋ ኢትዮጵያ ተረካቢዎች ዛሬ ላይ ጉያችን ውስጥ ያሉት እንቦቃቅላዎች ናቸው። ጥሩ ነገር ልንሰጣቸው፣ ጥሩ ነገር ልናስተምራቸው፣ ጥሩ ነገር ልናሳያቸው ይገባል። በጥሩ ስራ ለመጪው ትውልድ ዋስትና መሆን የዚህ ትውልድ ግዴታው ነው። ስንኖር አገራችንን እያሰብን መሆን አለበት። ስንሰራ፣ ስንማር ድሀ ህዝባችንን እያሰብን መሆን አለበት። ስልጣን ስንይዝ፣ ቦታ ስናገኝ፣ ወንበር ሲሰጠን ትውልዱን እያሰብን መሆን አለበት። በዚህ እውነት ውስጥ ስንቆም ነው ለራሳችንም ለአገራችንም ሰላም ማምጣት የምንችለው። በዚህ እውነት ውስጥ ስንኖር ነው እንደ አገር ያጣነውን የምንመልሰው።
አንዳንዶች በጥበብ ቤት ይሰራሉ፣ አንዳንዶች በጥበት ቤት ያፈርሳሉ። በአሁኑ ሰዐት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ጽንፍ የረገጡ ብዙ አይነት አመለካከቶች አሉ። እኚህ ለአገር የማይበጁ አመለካከቶች ታዲያ በጠረጰዛ ዙሪያ ነው የሚስተካከሉት። እናም ለመነጋገር መቀመጥ፣ ለመግባባት መወያየት አለብን። አገራችንን የምንሰራት ጽንፍ በረገጠ ሀሳብ ሳይሆን አንድነትን በተላበሰ ሀሳብ ነው። ቤት ጸንቶ እንዲቆም ዋልታና ማገር አለው። ቤት ያለዋልታና ማገር ምንም ነው። አገርም ጸንታ እንድትቆም ሰው ያስፈልጋታል። ሰው ስላችሁ ግን ዝም ብሎ ሰው አይደለም፤ አገር ማለት ምን ማለት እንደሆነች የተረዳ ሰው ነው። ምክንያቱም ሰው አገር ማለት ምን ማለት እንደሆነች ቢገባው አገሩ ላይ ጥፋት አያደርስም። አገር የህልሞቻችን መፈጠሪያ፣ የህልሞቻችን ማረፊያ ናት። አገር የነገ የልጆቻችን ቤት ናት። ካለሰላም አገር፣ ካለሀገር ሰላም ምንም ነው። በአገር ውስጥ ሰላም፣ በሰላም ውስጥ አገር የሁሉም ነፍሶች ምኞት ነው። ምኞታችን እውን እንዲሆን ለትውልዱ የሚቀመጥ መልካም ስራን እንስራ። ሳንጣላ፣ ሳንገዳደል መታረቅን ባህል እናድርግ።
የአገራቸውን መልካም ነገር የሚናፍቁ ሁሉ ለአገራችን ዋልታና ማገር መሆን ይጠበቅባቸዋል። ቤት ለመስራት ዋልታና ማገር እንዳስፈለገ ሁሉ፤ አገር ለመስራትም ሀሳብና ተግባቦት ግድ ይላሉ። የአንድነት ሀሳብ፣ የፍቅር ሀሳብ በሌለበት አገር ውስጥ ቤት አይሰራም። የእርቅና የተግባቦት፣ የሰላምና የመቻቻል ባህል በሌለበት ማህበረሰብ ውስጥ አገር አትረባም። የሚረባ አገር፣ የሚረባ ትውልድ እንዲኖረን የሚረባ ሀሳብ ያስፈልገናል። የሚረባ እድገት፣ የሚረባ ብልጽግና እንዲኖረን የሚረባ ሰላም ግድ ይለናል።
እየካብናቸው የተናዱብን፣ እያቆምናቸው የፈረሱብን ነገሮቻችን ሀሳብ በሌለው ምኞት የገነባናቸው ስለሆኑ ነው። ያሰብናቸው ያልተሳኩት፣ የተመኘናቸው ያልሆኑት ሰላም የሚፈጥር ተግባቦት ስለሌለን ነው። አገራችንን በጠረጴዛ ዙሪያ እንፍጠራት፤ ሃሳብ ሰጥቶ ሀሳብ በመቀበል እናቁማት። ለአገራችን ዋልታ እንሁናት፤ ለትውልዱም ምሰሶ እንሁን። ከታሪኮቻችን ተምረን ሰላም የዋጀው አዲስ ታሪክ እንስራ። ከትላንት ተምረን አዲስ ዛሬን እንፍጠር። በሰላም ከፍ የምንልባትን አገር፣ በመነጋገር ከፍ የሚልበትን ፖለቲካ እንፍጠር። በእርቅ የምትቀድም፣ በወንድማማችነት የበረታች ኢትዮጵያን እናጽና። ለዛሬው አበቃሁ፤ ሰላም!
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ጥር 5 ቀን 2015 ዓ.ም