የስንዴ ልማቱን፣ የበርካታ ግዙፍ ዳቦ ቤቶች ግንባታን ዜናን ስሰማ የዘመነ ደርግ የመጀመሪያዎቹ ዓመታት አንድ ዜማ ታወሰኝ። ዜማው ያኔ ይውጣ እንጂ ከዚያም በኋላ ተዜሟል። ዜማው ‹‹ሀ..ሁ ኢትዮጵያ ትቅደም…›› የሚል ነው። በዚህ ዜማ ውስጥ የሚገኙት ‹‹…ተብላ እንዳልነበር የዳቦ ቅርጫት፣ እንዴት እናታችን ትባል ራባት…›› የሚሉት ስንኞች የቁጭት መልእክት የሚያስተላልፉ ናቸው። ወቅቱ የ66ቱ ድርቅ ያስከተለው ረሀብ በርካታ ኢትዮጵያውያንን ፈጅቶ፣ ከቀዬቸው አፈናቅሎ፣ ለተረጂነት ዳርጎ ስለነበር የዳቦ ቅርጫት በመባል ትታወቅ የነበረችውን አገር ገጽታም በእጅጉ አበላሽቷል።
ድርቁ የ1966ቱን የንጉሱን አገዛዝ አሻፈረኝ ያሉ ወገኖች አመጽ ይበልጥ አንዲቀጣጠል ምክንያት ሆኗልም ይባላል፤ የአገሪቱን ገጽታም በእጅጉ አበላሽቶታል። የዳቦ ቅርጫቷን አገር የእንግሊዝኛው መዝገበ ቃላት የረሀብ ማሳያ ያደረጋትም ከዚያ ዘመን የሚጀመር ይመስለኛል። መዝገበ ቃሉ ድርቁን ‹‹ፋሚን›› ካለው በሁዋላ ስለፋሚን ማብራሪያ ሲሰጥ ምሳሌ የጠቀሰው ኢትዮጵያን ነው። ከዚያ ወዲህም እንደ 77ቱ ያሉ የድርቅ ወቅቶች በአገሪቱ ተከስተዋል። ሁሉም የአገሪቱን ገጽታ በእጅጉ እንዲጎድፍ አርገዋል።
በዚህች አገር ያን ገጽታ ለመቀየር ከ1966 ዓ.ም ወዲህ የመጡ መንግስታት ሁሉ ብዙ ጥረቶች አድርገዋል፤ ደርግ በ1977 ዓ.ም በአገሪቱ የተከሰተውን አስከፊ ድርቅ ተከትሎ እርዳታ ከማቅረብ በተጨማሪ ዘላቂ መፍትሄ ያለውን እርምጃ ወስዷል። አንዳንድ ወገኖች ሰፈራውን ሌላ ፖለቲካዊ መልክ ሊያላብሱት ቢሞክሩም፣ ለምነታቸው በተሟጠጡና ለድርቅ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎችን ወደ ለም አካባቢዎች አስፍሯል። በዚህም የበርካታ ዜጎችን የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ተችሏል፤ አንዳንዶችም ወደ ሀብት ማማ ወጥተውበታል።
በዚያ ዘመን በተካሄደው ሰፈራ ውጤት መታየቱንና ይህም የወቅቱ መንግስት ስኬት ተደርጎ መወሰዱን የሚያመለክት የሙዚቃ ድርሰት ጭንር በወቅቱ ወጥቶ ነበር። ይህ ሙዚቃ ታዋቂ አርቲስቶች ጭምር የተካተቱበት ነበር። ከእነዚህ መካከል አንዱ ድርሰት ‹‹የብሩህ ተስፋ እሸት›› ይሰኛል።
የብሩህ ተስፋ እሸት ካሴት በጊዜው በነበረው የኢትዮጵያ ሙዚቀኞች ማህበር አስተባባሪነት ገቢው በድርቅ የተጎዱ ወገኖችን ለመርዳት ተብሎ መዘጋጀቱን መረጃዎች ያመለክታሉ። ዝነኞቹ የሮሃና ዋልያስ ባንዶች እና በ12 ድምጻውያን የተዘጋጀ ነበር። ከድምጻውያኑ ስድስቱ ከአንጋፋ (ኦልዲስ) ስድስቱ ደግሞ በወቅቱ ያቆጠቆጡ፣ የጎመሩ ወጣት ድምፃውያን ነበሩ። የብሩህ ተስፋ አሸት ሕብረ- ዝማሬ ግሩም እንደነበረም ነው የሚገለጸው። በዚህ ዜማ፡-
የብሩህ ተስፋ እሸት አፈራ ጎመራ፤
በመላ ኢትዮጵያ ብሩህ ተስፋ ዘራ፤ …
የሚሉት ስንኞች የሚያመለክቱትም በወቅቱ በተወሰደው ርምጃ በግብርናው ዘርፍ ለውጥ መምጣቱን የሚያመለክቱ ናቸው። በዚሁ ዘመን የ‹‹አረንጓዴ ዘመቻ››ም ተካሂዶ እንደነበር ይታወሳል። ለምሳሌ፣ ኢህአዴግ አገሪቱን ማስተዳደር ከጀመረ በኋላ እንዳልነበር የሆነው የፓዊ የበለስ የመስኖ ልማት ያኔ በግብርናው ዘርፍ በተለይም ድርቅ እያስከተለ ከነበረው ችግር ለመውጣት ሲከናወን ለነበረው ተግባር ጥሩ ማሳያ ነው። በወቅቱ በቴሌቪዥን ይተላለፉ የነበሩ የፓዊ የመስኖ እርሻን የተመለከቱ ዘገባዎች አሁንም ድረስ ይታወሱኛል። በኛ አገር እየተፈጸመ ያለ አይመስልም ነበር። ኢህአዴግ እሱን ሰብሮ ጣለው።
በተመሳሳይ የጋምቤላው አልዌሮ ግድብ ተቀደመ እንጂ ደርግ ሌላው ታምር ሊሰራበት የታቀደ እንደነበርም ይገለጻል። እንዲህ እንደ ዛሬው ብዙ የተባለላቸው በርካታ ዳቦ ቤቶች በአዲስ አበባ ተገንብተውም ነበር። ምንም እንኳን በኢህአዴግ እድሜ እንዲኖራቸው ባይደረግም ሁሉም ጥረቶች ያን የዳቦ ቅርጫትነት ዘመን ለመመለስ የተሞካከሩ ስራዎች ይመስሉኛል።
በኢህአዴግ ዘመንም ቢሆን ግብርናው ላይ ለመስራት ጥረት ተደርጓል። ግብርና መር የኢኮኖሚ ፖሊሲ ተግባራዊ በማድረግ ለውጦች ማሳየት ተችሏል። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅዶቹም ግብርናው ላይ መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣትና በኢኮኖሚው ያለውን ድርሻ ወደ ኢንዱስትሪው ለማዞር ተሞክሯል። ይሁንና ካለው የግብርና ምርት ፍላጎት አኳያ ሲታይ ግብርናው ገና ብዙ ይቀረው ነበር። ታዩ የሚባሉ ለውጦችም ግብርናው ይፈለግ ከነበረው መዋቅራዊ ለውጥ አንጻር የሚጠበቀውን ውጤት ያመጡ አልነበሩም።
ከ2010ሩ አገራዊ ለውጡ በኋላ በግብርናው ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው። ግብርናው ዘርፍ ላይ ምርትና ምርታማነት እየታየ መሆኑ ታምኖበት፣ አድናቆት ተችሮትም ነበር፤ ይሁንና እንደ አገር ካለው የግብርና ምርት ፍላጎት እየጨመረ መምጣት አንጻር ሲታይ እድገቱ እዚህ ግባ የሚባል ሊሆን አልቻለም። እናም ዘርፉ ካለው እምቅ አቅም አኳያ እንዲሁም ከአቅርቦት ፍላጎት ክፍተቱ አኳያ ሲታይ በእርግጥም ዘርፉ ትልቅ ሪፎርም የሚያስፈልገው ሆኖ ተገኝቷል።
በመሆኑም መንግስት በግብርና ላይ ትኩረት አድርጎ የመስራት አስፈላጊነትን በማመን ወደ ስራ ገብቷል። ባለፉት አራት ዓመታት በግብርናው ዘርፍ በተለይ በስንዴ ልማት ላይ እየታየ ያለው ለውጥም ይህን ተከትሎ የመጣ ነው። በአጠቃላይ በግብርናው ምርትና ምርታማነት ላይ ለውጥ ለማምጣት እየተሰራ ሲሆን፣ በስንዴ፣ በሩዝና በአንዳንድ የእህል አይነቶች ምርትና ምርታማነት ላይ ለውጦች እየታዩ ናቸው።
በተለይ በስንዴ ልማቱ ላይ የታየው እምርታ ዓለምን ጭምር አስደምሟል፤ ያለፈው ዓመት የብሉንበርግ፣ የኬንያው ኔሽን ጋዜጣ ዘገባዎች፣ የአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት አድናቆት፣ ወዘተ የሚያመለክቱትም ይህንኑ ነው። በአገሪቱ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ስንዴ በመስኖ እየለማ ነው። በዚህም ባለፈው ዓመት 26 ሚሊየን ኩንታል ስንዴ ተገኝቷል፤ ዘንድሮ ደግሞ 52 ሚሊየን ለማግኘት እየተሰራ ነው። በቆላማ አካባቢዎች የተጀመረው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት አሁንም በሁሉም አየር ንብረቶች ላይ እየተካሄደ ይገኛል።
በስንዴ ልማቱ በመስኖ ላይ ብቻ አይደለም የተተኮረው፤ በመኸር ስንዴ ልማትም ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ነው። በመኸር ወቅት በስንዴ ዘር የሚሸፈነው ማሳ እየጨመረ ይገኛል። በቅርቡ የወጣ የግብርና ትራንስፎርሜሽን መረጃ እንደሚያመለክተው፤ አገሪቱ በሁለቱም መንገዶች ከ107 ሚሊየን ኩንታል በላይ ስንዴ ለማምረት እየሰራች ትገኛለ ች።
በዚህም በስንዴ ልማቱ የአገር ውስጥ ፍላጎትን ሙሉ ለሙሉ ከመመለስ በተጨማሪ፤ ሌሎች ታሳቢ የተደረጉ ስራዎችም አሉ። ስንዴ ለጎረቤት አገሮች ገበያ ማቅረብ እና የውጭ ምንዛሬ ማግኘት የሚሉት፤ እነዚህን ለማሳካትም ነው እየተሰራ ያለው።
ይህን ተከትሎም የጎረቤት አገሮች ፍላጎት እያሳዩ ይገኛሉ። የአገር ውስጥ የስንዴ ፍላጎት 90 ሚሊየን ኩንታል እንደሆነ መረጃዎች ያመለክታሉ። ይገኛል ተብሎ ከሚታሰበው በላይ የሚሆነውን የስንዴ ምርት ነው ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የታቀደው። የስንዴ ልማቱ ፖለቲካዊ ፋይዳም አለው። በስንዴ እርዳታ ሊሸነግሉን ለሚፈልጉ አካላት ግልጽ መልእክት የተላለፈበት ዋና ተግባርም ነው። ይህ ትልቅ እምርታ ነው።
በእርግጥም የአገር ውስጥ የስንዴ ፍላጎትን ሸፍኖ ለውጭ ገበያ መድረስ ትልቅ እምርታ ነው። የስንዴ እርዳታ ይደረግላት እና ስንዴ ከውጭ ስትገዛ የነበረች አገር ከውጭ ስንዴ ማስገባቷን ማስቀረቷ፣ የራሷን ፍላጎት አሟልታ ለውጭ ገበያ ማቅረቧና የውጭ ምንዛሬ ማግኘት ማቀዷ ልማቱ ምን ያህል እምርታ እንደታየበት መረዳት አያዳግትም።
አገሪቱ ስንዴ በማምረት ብቻ አልተገታችም። በዳቦ ፋብሪካዎች ግንባታም ተጠምዳለች። የሸገር ዳቦ ፋብሪካ በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎችና በከተማዋ ዙሪያ በሚገኙት የኦሮሚያ ከተሞች ዳቦ ለማቅረብ አንደሚሰራ ይገልጽ ነበር፤ በከተማዋ አቅራቢያ በሚገኙት ከተሞች ስላለው ሁኔታ ባላውቅም፣ ለአዲስ አበባ ዳቦ እያቀረበ ነው፤ በእዚሁ በአዲስ አበባ በቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ፕሮጀክት ሌላ የዳቦ ፋብሪካ ተገንብቶ ተመርቋል። የቀዳማዊ እመቤቷ ፕሮጀክቶች ዳቦ ቤቶችን በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እያስገነባ ይገኛል። በቅርቡም በወላይታ ሶዶና እና ሀዋሳ ከተሞች እያንዳንዳቸው በቀን 300 ሺ ዳቦዎችን የሚያመርቱ ፋብሪካዎች በቀዳማዊት እመቤቷ ፕሮጀክት ተገንብተው በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ተመርቀዋል።
የሸገር ዳቦ ፋብሪካ፣ በዚህ ላይ በእያንዳንዱ ክፍለ ከተማ በ90 ቀናት እቅድ ሁለት ሁለት ዳቦ ቤቶች እንደተገነቡ ስለመሆኑም እየተነገረ ነው፤ ዳቦ መጋገሪያ ህንጻዎቹ ቀጣይ ስራቸው ዳቦ መጋገሪያ ማሽኖች ተገጥሞላቸው ዳቦ መጋገርና በተመጣጣኝ ዋጋ ማከፋፈል ይሆናል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወላይታ ሶዶ የተገነባውን በቀን 300 ሺ ዳቦዎችን የሚጋገርበትን የዳቦ ፋብሪካ በመረቁበት ወቅት እንዳሉት፤ የዛሬ አራት ዓመት አዲስ አበባ ውስጥ 300 ሺ ዳቦ አይጋገርም ነበር፤ ዳቦ መጋገሪያዎቹ ሁሉ ተደምረው ይህን ያህል ዳቦ አያመርቱም ነበር። ዛሬ አዲስ አበባ ውስጥ በሚሊየን የሚቆጠር ዳቦ በቀን እየተመረተ ነው። በአዲስ አበባ ብቻ ሳይሆን በዋና ዋና ከተሞችም ሰፋ ያለ ዳቦ የሚያምርቱ ፋብሪካዎች ኢትዮጵያ ይኑራት ተብሎ በተለያዩ ከተሞች ዳቦ ፋብሪካዎች ተገንብተው ይመረቃሉ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቀጣይም በሀዋሳ፣ በጎንደር፣ በሐረር፣ በቦንጋ እና በሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የዳቦ ፋብሪካዎች ይመረቃሉ ሲሉ ጠቅሰው፣ ይህም ኢትዮጵያን የዳቦ ቅርጫት የማድረግ የመጀመሪያው ጡብ የተቀመጠበት ተደርጎ ሊወስድ ይችላል ብለው ነበር።
ይሄ ትልቅ ራእይ ነው። አገራችን የዳቦ ቅርጫት እንደነበረች የደርግ መንግስት ወደ ስልጣን በመጣበት ወቅት ይገልጽ ነበር። ‹‹ሀ..ሁ ኢትዮጵያ ትቅደም…›› በሚለው የወቅቱ ዜማ ውስጥ ከሚገኙት ‹‹ ተብላ እንዳልነበር የዳቦ ቅርጫት፤ እንዴት እናታችን ትባል ራባት›› ከሚሉት ስንኞች መረዳት የሚቻለውም ይህንን ነው። ይሁንና ከዚህ ይልቅ አገራችን የምትታወቀው አስከፊ በሚባሉ የድርቅ ክስተቶቿ ነው።
አሁን ግን ከስንዴ ልማቱ ውጤታማነት በተጓዳኝ፣ በአገሪቱ የተለያዩ ከተሞች ግዙፍ ዳቦ ቤቶች ለመገንባት መንግስት እና የቀዳማዊ እመቤት ፕሮጀክት እያደረጉ ካሉት ጥረት አኳያ ሲታይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉትም የዳቦ ቅርጫትነቷን እውን ማድረግ ይቻላል። ምክንያቱም እንደሚታወቀው የዳቦ ቤቶች መሰረታዊ ችግር ሆኖ የቆየው የስንዴ ችግር እየተፈታ ይገኛል። የዳቦ ጉዳይ ከዳቦ ቤቶች ወደ ዳቦ ፋብሪካዎች እየተሸጋገረ ነው። አሁን የሚጠበቀው ዳቦው ነው፤ ይህ ሲሆን አገሪቱ ወደ ዳቦ ቅርጫትነቷ እውን መሆን ምልክቶች ይበልጥ መታየት ይጀምራሉ።
አሁን ባለው ሁኔታ ሸገር ዳቦ ፋብሪካ እንደተባለለት ባይሆንም የዳቦ አቅርቦቱን ቀጥሎበታል። ሸገር ግዙፍ የዳቦ ፋብሪካ ነው፤ ከሚታይበት የአቅርቦት ወጣ ገባነት፣ ካለው የህብረተሰቡ ፍላጎት አኳያ ሲታይ ግን በሙሉ አቅሙ እያመረተ ነው ማለት ግን ያስቸግራል። በቀዳማዊ እመቤት ፕሮጀክት የተገነባው የዳቦ ፋብሪካ ትኩረት ተሰጥቶ ሊሰራበት የሚገባ ስለመሆኑ ጠቋሚ ጉዳዮች አሉ። በ90 ቀናት እቅዱ የተገነቡት የዳቦ ቤቶች ህንጻዎች አስፈላጊዎቹ መጋገሪያዎች ተተክሎላቸው፣ የኤሌክትሪክ ኃይል ተዘርግቶላቸው ዳቦ ጋግሮ ወደ ማቅረብ መሸጋገር እንዲችሉ ተገቢውን ትኩረት እና እገዛ ሊደረግ ያስፈልጋል።
ከዚህ ጋር ተያይዞ መታየት ያለበት የግል ባለሃብቱን ወደዚህ ስራ እንዲገባ መደገፍና ማበረታታቱ ሲሆን፤ በዚህ ረገድ በቀደሙት የግል ዳቦ መጋገሪያዎች የሚስተዋሉ የዳቦ ግራም ጉዳይም መፈታት ይኖርበታል። በግራም በኩል ሸገር ጥሩ ነው። ሌሎቹም ዳቦ አይደለም እየሸጡ ያሉት፤ የዳቦ ቅርፊት ነው እየሸጡ ያሉት። ዋጋው ሰማይ እንደ ወጣ ነው፤ በግራሙ የተሻለ ዳቦ የሚያቀርቡት ዋጋም ተመላልሶ የሚያስገዛ አይደለም።
ዳቦ በሁሉም የማህበረሰብ ክፍል የሚፈለግ እንደመሆኑ ሸገርን ጨሞሮ ሁሉም አዳዲስ ዳቦ ቤቶች ሁሉንም ማህበረሰብ ያማከለ የዳቦ አቅርቦት ላይ አተኩረው መስራት ይኖርባቸዋል። አዳዲስ ግዙፍ ዳቦ ቤቶች እየተገነቡ እንደመሆናቸው በአመጋገብ ላይም የባህል ለውጥ ይመጣል የሚል እምነት አለኝ፤ የእንጀራ አዘውታሪ የሆነው ህብረተሰብ የዳቦ አቅርቦቱ እየሰፋ ሲመጣ ዳቦ ተመጋቢ እንደሚሆን ይጠበቃል። ለሁሉም ግን ዳቦ ቤቶቹ ዳቦ ጋግረው ወደ ማቅረብ መሸጋገር፤ ከማሳ እስከ ጉርሻ ያለው ፍሰት ተሳልጦም የተጀመረውን ውጤት በማስቀጠል የዳቦ ቅርጫትነቱን ግስጋሴ እውን ማድረግ የሁሉንም ባለድርሻ ኃላፊነትን መወጣት ይጠይቃል። ሰላም !
ዘካርያስ ዶቢ
አዲስ ዘመን ጥር 2 ቀን 2015 ዓ.ም