ኢትዮጵያ የሰላም ርግቧን ለቃለች..እንደ ቁራ ሄዶ የቀረ ሳይሆን ተስፋን የሰነቀች የሰላም ርግቧን ሰላም በራበው ጥቁር ሰማይ ላይ ለቃለች። አሁን አንደበታችን ስለሰላም፣ ጆሮቻችን ደግሞ ስለወንድማማችነት የሚሰሙበት ጊዜ ላይ ነን። የሰላም ስምምነቱ ፍሬ እያፈራ እንደሆነና የኢትዮጵያ የአንድነት ጊዜ እየመጣ እንደሆነ ብዙ አመላካች ምልክቶችን መጥቀስ ይቻላል።
የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት መሠረት አድርጎ በሕወሓትና በፌደራል መንግሥት መካከል የተደረገው የሰላም ስምምነት በአግባቡ እየሄደ ነው። ሰሞኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ የሚመራ የፌደራል መንግሥት የልዑካን ቡድን ወደ መቀሌ አቅንቷል። ይሄ ብዙዎቻችን የምንመኘው የኢትዮጵያን መጻኢ እድል በበጎ እንድናይ የሚያደርግ አዲስ የተስፋ መንገድ ነው።
የልዑካን ቡድኑ ወደ መቀሌ ማቅናት በሰላም ስምምነቱ መሠረት እየተከናወነ ያለውን የትግበራ ሂደት ለመቃኘትና ሂደቱን ለመከታተል ነው። በዚህም መሠረት አመርቂና አስተማማኝ ሊባል የሚችል የሰላም መደላድል መፍጠር ተችሏል። ከዚህ ባለፈ ልዑካን ቡድኑ ከሁለት ዓመት በኋላ ወደመቀሌ የተጓዘ የመጀመሪያው የፌደራል መንግሥት ልዑክ ነው። ይሄ የሚያሳየው ስምምነቱ በመልካም ሁኔታ ላይ እንዳለና መጪው ጊዜ በሰላምና በፍቅር የሚኖርበት እንደሆነ ነው።
መንግሥት በገባው ቃል መሠረት ቅድሚያ የሚሰጠውን ማንኛውንም ነገር እያደረገ ነው። ከሰብዓዊነት አንጻር ብዙ ሥራዎች እየተሠሩ ነው። ጤና ጣቢያዎች፣ ሆስፒታሎች አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል። የስልክና የባንክ፣ የመብራትና የኢንተርኔት አገልግሎቶች በማስጀመር የክልሉን ሕዝብ ወደነበረበት የሰላምና የመሠረተ ልማት ምቹነት እየመለሰው ነው። ከአዲስ አበባ ወደ መቀሌ የአየር በረራ ተጀምሯል። አየር መንገዱ ትግራይ ክልል ወዳሉ ሌሎች የበረራ መዳረሻዎች በረራ ለማስጀመር እየሠራ ነው።
በቀጣይም የሰላም ስምምነቱን ወደላቀ ታማኝነት የሚያሸጋግሩ ሌሎች ሥራዎች እንደሚሠሩ ይታመናል። ካለፈው የጦርነትና የጉስቁልና ሕይወት ተምረን ችግሮቻችንን በጦርነት ሳይሆን በሰላም እየፈታን አንድ ሀገርና አንድ ሕዝብ እንፈጥራለን። ሰላም በሚናገሩ፣ ሰላም በሚሰሙ ድምጾች ወደቀደመ ወንድማማችነት ተመልሰን ሀገራችንን በጋራ እንደምናበለጽግ እናምናለን።
የሁለቱ ወገን መጨባበጥ እኛጋ የሚፈጥረው ስሜት አለ። ከመጀመሪያዋ ቀን ከፕሪቶሪያ ስብሰባ ጀምሮ ሕዝቡ አብሮ የመኖርን፣ አብሮ የመብላትን ተስፋ ሲሰንቅ ነበር። ይሄ ተስፋ አድጎና መንድጎ መቀሌ ላይ በሌላ መጨባበጥ ታየ። ይሄን ነው የኢትዮጵያ ሳቅ። ይሄን ነው የትውልዱ እልልታ። ሀገር ነፍስ የምትዘራው እንዲህ ነው። በሰላማችንና በመጨባበጣችን የሳቀችውን ያክል በመገፋፋታችን የምታዝንበት ጊዜ አለ። የሀገር ሳቅ የትውልድ ሳቅ ነው። የሀገር ሳቅ የሕዝብ ሳቅ ነው..መከራዋም በመለያየታችን የሚመጣ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በመቀሌ የነበረውን የልዑካን ቡድን ምልከታ አስመልክተው በትግራይ ክልል የተጀመረው አገልግሎት የማቅረብ ሥራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል መመሪያ አስቀምጠዋል። በየደረጃው ያሉ የመንግሥት ኃላፊዎች የትግራይ ክልል ወደቀደመው ሁኔታው እንዲመለስ እንደሚሠሩ ቃላቸውን ሰጥተዋል። እየተረባበሩ ነው ። በቀጣይም በሰላም ስምምነቱ መሠረት ሌሎች ቀሪ ሥራዎችም ይተገበራሉ።
የተጀመረው የሰላም ስምምነት ፍሬ እንዲያፈራና ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ከፍሬው እንድንቋደስ የአንድነት ዜማዎችን፣ የሰላም ብሥራቶችን ማስተጋባት አለብን። መንግሥት ለሰላም እየተጋ እኛ ሰላም የሚያደፈርስ ድርጊት ላይ የምንሳተፍ ከሆነ ልክ አይደለም። ሰላም የጋራ ውጤት ነው። መንግሥት ብቻውን የሚያመጣው ሀገራዊ ሰላም የለም።
ለሀገራችን ሰላም ሁላችንም እኩል ዋጋ አለን። ከምንናገረው ጀምሮ፣ ከምንሰማው ጀምሮ፣ ከተግባራችን ጀምሮ ለሀገራችን ሰላም ኃላፊነት አለብን። ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የሰማነውን ማንኛውንም ያልተረጋገጠ ነገር እውነት ነው ብለን የምንቀበል ከሆነ፣ እውነት ነው ብለን የምናወራ ከሆነ፣ እውነት ነው ብለን ለሌሎች የምናጋራ ከሆነ የሰላም ሀላፊነታችንን እየተወጣን አይደለም።
የሰላም ተደራዳሪዎቹ በናይሮቢ ውይይታቸው መቀሌ ላይ ተገናኝተው ሊመክሩ ተነጋግረው ነበር። በቀጠሯቸው መሠረትም ትግራይ ላይ ተገናኙ። ሰላም ዋጋ የሚያወጣው ልክ እንደዚህ ከቃል ባለፈ በተግባር ሲውል ነው። ተግባር የታከለበት ቃል ፍሬ የሚያፈራ ነው። ቃላችን ፍሬ አፍርቶ እንድናይ በሰላም ስምምነቱ ሂደት ላይ በሁለቱም ወገን የተገቡ ቃሎች ተፈጻሚ መሆን አለባቸው።
የለቀቅናት የሰላም ርግብ የመከራችን ዘመን ማብቃቱን እንድትነግረን ደጅ ቆመን እየጠበቅናት ነው። ተስፋን የጣልንባት የሰላም ርግባችን መርዶ ይዛ እንድትመጣ አንፈልግም። ከመቶ ሚሊዮን በላይ ሰላም የተራቡ ልቦች ብሥራቷን እየጠበቁ ነው። ጦርነቱ ማብቃቱን፣ ወጀቡ ማለፉን የሚያበስር የዘንባባ ዝንጣፊ ይዛ እስክትመለስ ልባችን መምጫዋ ላይ ነው። የተጀመረው ሰላም በማይሰበርና በማይናወጥ የወንድማማኝነት ስሜት እንዲቋጭ እንፈልጋለን። መከራ ላጠላባት ሀገሬ ተስፋና ብርሃን እንዲሆን የሁላችንም ምኞት ነው።
መንግሥት ሰላም ወዳድ መሆኑን ፤ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት፣ ለሰላም ያለውን የጸና ፍላጎት በተለያየ ጊዜ አሳይቶናል። ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት ሰላም ይሻለናል ሲል ነበር። ከተጀመረም በኋላ ሰላም እንዲመጣና በመነጋገር ወደመፍትሔ እንዲመጣ ብዙ ዕድሎችን ሲፈጥር ቆይቷል። አሁንም ከሰላም ስምምነቱ በኋላ ቃሉን በማክበር ወደትግራይ ብዙ አይነት ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ድጋፎች እንዲገቡ በማድረግ ላይ ይገኛል።
የመንግሥት የሰላም ቁርጠኝነት ከቃል ባለፈ በተግባር የተደገፈ ስለመሆኑ በርካታ ማስረጃዎችን ማቅረብ እንችላለን። የልዑክ ቡድኑን ወደመቀሌ መላኩ ከቃልና ከተግባር በላይ ለሰላም ያለውን እውነተኛ ቁርጠኝነት ያሳየ ነው። ሰላም በመልካም ቃል ውስጥ ነው የሚያፈራው። መርዶ እየተናገርን ሰላምን ማምጣት አንችልም። እየሆነ ላለው በጎ ነገር እውቅና በመስጠት ለሌላ በጎ ነገር መዘጋጀት አለብን።
የፖለቲከኞቻችን መጨባበጥ ለእኛ የተስፋ ምልክት ነው። የፖለቲከኞቻችን መተቃቀፍ ለሀገራችን የማያባራ ሳቅ ነው። እንደ ዜጋም ሆነ እንደ ሀገር መጨባበጣቸውን እንፈልገዋለን። የሁለት ዓመት ጉስቁልናችን ካለመጨባበጥ የመጣ ነው። ሰላምን ከፊት አድርጎ ለአንድነት መቆምና መጨባበጥ በአሁኑ ሰዓት ግድ የሚለን ነገር ነው። ለሰላም እጅ መስጠት ማሸነፍ ነው።
ሀገር የሚያፈቅሩ ልቦች ሁሉ ለሰላም እጅ የሰጡ ናቸው። ኢትዮጵያን የምንወድ ከሆነ ለሰላሟ እጅ እየሰጠንና እየተጨባበጥን ፍቅራችንን መግለጽ ይኖርብናል። አሁን ላይ እየሆነ ያለው ይሄ ነው..ተጨባብጠናል፣ ለሰላም ቅድሚያ ሰጥተን ስለሀገራችን አውርተናል። ቀሪው ጊዜ በመጨባበጥና በመተቃቀፍ የኢትዮጵያ ይሆናል።
በመካከላችን ገብተው መጨባበጣችንንና መተቃቀፋችንን ሊያደበዝዙ ለሚችሉ ማናቸውም ነገሮች ዕድል መስጠት የለብንም። በመጨባበጣችን የምናተርፈው ብዙ ነው..ሳንጨባበጥ ተለያየተን የሰነበትንባቸው ሁለት የጦርነት ዓመታት ምን ያክል ዋጋ እንዳስከፈሉን የምናውቀው ነው። አዲሷን ኢትዮጵያ በመጨባበጥ መፍጠር አለብን። በመተቃቀፍና በወንድማማችነት መንፈስ መፍጠር አለብን።
ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ሰላም ያስፈልገናል። አሁን ላይ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ምን ትፈልጋለህ? ብለን የመጠየቅ እድል ቢገጥመን ከሰላም ውጪ ጥያቄ እንደሌለው እንደርስበታለን። የሰላም ጥያቄ የልማት ጥያቄ ነው። የሰላም ጥያቄ የዲሞክራሲ ጥያቄ ነው። የሰላም ጥያቄ የሕልውና ጥያቄ ነው። በእኛም ሆነ በመንግሥት እቅድ ውስጥ ያሉ ማናቸውም ነገሮች የሚሰምሩት ሰላም ሲኖር ነው።
የሀገራችን የኋላ ቀርነት ታሪክ ከሰላም ማጣት ውስጥ የሚመዘዝ ነው። ይሄ ነውር እንዲጸዳ በመነጋገር የቆነጀ ታሪክ ያስፈልገናል። ይሄ ጉድፍ እንዲጸዳ በውይይት የሚያምን አዕምሮና ልብ ያስፈልገናል። ጭንቅላቶቻችን ነውጥ እየፈጠሩ የሰላም ሀሳብ የሚጠፋቸው ከሆነ፣ ጦርነት እየጎሰሙ የሰላም ቃል የሚያጥራቸው ከሆነ አዲስ ሀገር መሥራት አንችልም። ከትላንት ለመውጣት እንደትላንት ከሚያደርጉን ልምዶች መላቀቅ አለብን። ሰላምን በሰላማዊ ሀሳብ እንጂ በጽንፈኛ ሀሳብ ማምጣት አንችልም። የለመድናቸውንና የተለማመድናቸውን አንድ አይነት የሕይወት ልምዶች ገሸሽ አድርገን አንድና ልዩ በሚያደርጉን እውነቶች ላይ መምከር ከትላንት ለማምለጥ አቋራጭ መንገድ ነው።
ጠያቂዎች መሆን አለብን..የማይጠይቅ ትውልድና እውነትን የማይናገር ታሪክ ሁለቱ አደገኛ ናቸው። ለሀገራችን ውለታ ለመዋል፣ ከማይጠቅማት ወጥታ ወደሚጠቅማት እንድትሄድ መጠየቅ አለብን። እውነትን መስማት አለብን። ዛሬ ላይ ችግር እየተፈጠረብን ያለው መጠየቅ በማይችሉና እንዴት ማስረዳት በማይችሉ ባለታሪኮች ነው። ለምን ሳንል በሰማንው ነገር ብቻ ለውሳኔ መሮጥ የኢትዮጵያ የብዙ ዘመን ታሪኳ ነው።
በዚህ ታሪክ ውስጥ ኖረን ስላለፍን ነው ሰላም ማምጣት የቸገረን። ለጦርነት የሚሆን፣ ለውሸት ወሬ የሚሆን፣ ለማስመሰልና ለፈጠራ የሚሆን ብዙ እውቀት አለን። ለተረት የሚሆን፣ ዋሽቶ ለማጣላት የሚሆን ብዙ እውቀት አለን። ለሰላም ሲሆን ግን ደካሞች ነን። ሰው ለሰላም ካልበረታ፣ ሰው በሰላም ካልጀገነ ለምንም ነገር አቅም አይኖረውም። በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው፣ በማኅበራዊ ሕይወታችን አቅም እያጣን የመጣንው ለሰላም የሚሆን ጉልበት ስለሌለን ነው። ለሰላም የሚከፈል ዋጋ ለምንም ከሚከፈል ዋጋ የሚበልጥ ነው። መንግሥት ለሰላም ዋጋ እየከፈለ ነው። ዋጋውም ፍሬ አፍርቶ ከጦርነት ወደሰላም መጥተናል። ይሄ ሰላማችን እንዲቀጥል ለሰላም የሚሆን ብዙ ኃይልን ማበጀት ይጠበቅብናል።
እንጠይቅ..ክፉዎች ወደጦርነት ሲወስዱን ለምን እንበል። ራስወዳዶች ወደሞት ሲነዱን ለምን እንበል። በለምን ያልተማገረች ሀገር፣ በለምን ያልቆመ ማኅበረሰብ ምንም ነው። ለምን ብሎ የማይጠይቅ ፖለቲከኛ፣ ለምን ብሎ የማይጠይቅ ትውልድ ለሀገር ስጋት ከመሆን ባለፈ ዋጋ አይኖረውም። የአሁኑ ሰላማችን በብዙ ጥያቄ የመጣ ነው። የአሁኑ መጨባበጣችን በብዙ ምኞት የመጣ ነው። ብዙ ለፍተን፣ ብዙ አልቅሰን፣ ብዙ ጸልየን፣ ብዙ ጠይቀን ፈጣሪ የመለሰልን መልስ ነው።
ከእጃችን እንዳይወጣ አጥብቀን ልንይዘው ይገባል። ለድርጊት ከመነሳሳታችን በፊት ለምን ብለን እንጠይቅ። በእኛ ሀገር ለምን ብለው ሳይጠይቁ ለመግደልና ለመሞት ሾተል የሚያነሱ ብዙ ናቸው። ሳንሞትና ሳንገል፣ ብዙ ጉስቁልና ሳይደርስብን የሰላምን ዋጋ ልናውቅ ይገባል። ጠያቂ ትውልድ አይኑን እንጂ ጆሮውን አያምንም..በአይኑ ቢያይ እንኳን እንዴትና ለምን ብሎ ጠይቆ ችግር ካለ በመነጋገር ወደሰላም ለመምጣት ዝግ ይላል እንጂ አይፈጥንም። እናም ለምን ብለን በመጠየቅ፣ ዝግ ብሎ በማሰብ፣ ስለሰላም በመጨባበጥ ለሀገራችን ውለታ እንዋል።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ታህሳስ 28 ቀን 2015 ዓ.ም