ድሮ ልጆች እያለን ለኔ ማንኛውም ነገር ከተግዛ ታናሽ እህቴ በለቅሶ ብዛት ቤቱን በጥብጣ የኔን ንብረት አንቺ ትልቅ ነሽ ተብዬ እነጠቃለሁ ምንም እንኳን ንብረቱ ገዥ ቤተሰቦቼ ቢሆኑም የተገዛው ግን ለኔ ነው ከተገዛ ሰአት ጀምሮ ባለቤቱ እኔ ሆኜ ሳለ በጉልበት ነጥቀውኝ ይሰጧታል።
አሁን አድጌ ስራ ከጀመርኩ በኀላም እንደ እህቴ ያሉ በሰው ገንዘብ (መብት) ድርቅ ብለው የሚያለቅሱ ብዙ አገልግሎት ሰጪዎች ያጋጥሙኛል በርግጥ እህቴ በወቅቱ በጉልበት ልትቀበለኝ ስልማትችል ነው አልቅሳ ለነጣቂ የምታስነጥቀኝ አሁን ያልኳቹ አገልግሎት ሰጪዎች ግን በጉልበታቸው ተማምነው ነው የሚነጥቋችሁ።
ያለፈው ሳምንት አከባቢ ነው እና ምን ሆነ መሰላቹ አያቴ ልጄ ቀን አይጨልምብሽ ፤ አይምሽብሽ ብላ ምትመርቀኝ ነገር እውነት ሰው ሲመሽበት በተላይ እንደኔ ያለው እግረኛ ከመሸበት ….. እኔ አልናገርም አምሽታችሁ እዩት ይሄው ነገር እድሜ በጠገበ አእምሮዋ የተገለጠላት የመገለጦች ሁሉ አውራ መገለጥ ነው።
ታክሲ ውስጥ ገብቼ ዝርዝር ስለነበረኝ ያለኝን 5 ብር ሰጠሁት” እ እ እናት የት ነሽ? ሰአትሽን አይተሸዋል ምሽቷል እኮ 10 ብር ነው ጨምሪ “ አለኝ እኔም ትንሽ መብቴን የማስከበር ወኔ መቶብኝ ታሪፉ ስንት ነው? አንተስ ሰአትክን አይተከዋል ገና በ 12፡30 የሶስት ብር ከሃምሳ መንገድን 10 ብር ምታደርግው ? ” መሸ ለመባል ሰአት አይታይም ጸሃይ ወደ ማደሪያዋ መግባቷ ብቻ በቂ ነው”አለኝ ።
እንደዛ ሲል ደግሞ ደሜ ፈላ ”ያለውል ከተበላች ቆሎዬ በውል የሄደች በቅሎዬ” ያሉት አባቶቻችን ያለምክንያት አይደለም አልኩና ፤ እንዳጋጣሚ ደግሞ ቀና ስል ታሪፍ ተለጥፎ አየሁ እስከ 3 ኪ.ሜ ድረስ ታሪፉ ሚፈቅደው 3፡ 50 ነው ይለይለት ብዬ እንደውም መልስ አለኝ አምጣ አልኩት የታክሲ ረዳቱ ጨርቁን ሊጥል ምንም አልቀረውም
ከሱ መናደድ በላይ ያስገረመኝ” ከሌለሽ የለኝም በይ”፤” ምንድነው ለሰፈሩ አዲስ ነሽ ሁሌ እንደዚነው እየተከራከርሽ አታስመሺብን” ፤ ”ወንድም እኔ እጨምርላታለሁ ሹፌር እንሂድ” ፤ አለ አንድ ወጣት ልጅ ደሜ ፈላ ማን ስለሆንክ ነው የምትጨምርልኝ ታክሲ ውስጥ የገባሁት እርዳታ ለመጠየቅ ሳይሆን ተሳፍሮ ለመሄድ ነው፣ ያ ደግሞ መብቴ ነው አልኩ በብስጭት።
ወደ ጎን ዞር ስል የምትገርም መፈክር አየሁ እንዲህ ትላለች ”ጀበና ሲገነፍል ራሱን ነው የሚያቆሽሸው” ሾርኒ እንደሆነች አሰብኩ ሰው መብቴ ተነጠቀ ብሎ ለገዛ መብቱ ሲናደድ ” እንደፈለክ ተናደድ እኔ እንደሆንኩ መንጠቄን አልተውም፤ ስትበሳጭ ያንተው ጨጓራ ነው የሚላጠው” የሚል ቅኔ እንዳላት መጠርጠር ሳይሆን እርግጠኛ ሆንኩ ።
ቁም ነገሬ ይሄንን ማውራት አይደለም ሰዎች በሃገራችን መብታቸውን መጠየቅን እንደ ተጨቃጫቂነት ነው ሚያስቆጥራቸው ለምሳሌ እኔ መብቴን ነው የጠየኩት ግን ሰዎች እኔን ደግፈው ከመቆም ይልቅ መብቴ እንዲጣስ ብቻ ሳይሆን መብቴን መጠየቄም እንደ አላዋቂ እና እርዳታ ፈላጊ እንዲቆጥሩኝ አስችሎአቸዋል።
መንግስት የነዳጅ ድጎማ የሚያደርገው ከህብረተሰቡ ላይ የኢኮኖሚ ጫናውን ለመቀነስ ነው ነገር ግን መብቱን ሳይጠይቅ ሚያከብርለት የለም ፤ ሲጠይቅ ደግሞ የራሳቸውን መብት መጠየቅ ባለቻሉ ወይም ባልፈለጉ ሰዎች መብታቸውን አስጥሰው መብትህን ማስጣስ ያሻቸዋል።
አንተ መብትክን ማስከበር ካልቻልክ ሚያከብርልክ ለማክበር የስነ ልቦና ዝግጅት የለውም ምክንያቱም እንደ ሁላችንም ታናናሽ ወንድምና እህቶች ነው ያደገው ፤የሰው ንብረት መጠየቅ አስፈቅዶ መውሰድ አልተማረም ፤ከቻለ ይነጥቅሀል ካልሆነለት ያስነጥቅሀል።
ሰዎች ብዙ ጊዜ መብታቸውን አይጠይቁም አንድ ጊዜ አንዲት ሴት መሬት መግዛት ፈልጋ ቦታው ለልማት ይፈለጋል ወይም አይፈለግም ሚለውን ለማወቅ አንድ የመንግስት ተቋም ሄዳ በጣም ያጉሏላታል ይህንን ጉዳይ መጠየቅ መብቷ ነው እዛ ጋር የተቀመጡት ሰዎች ደግሞ ግዴታቸው እና የእንጀራ ገመዳቸው ነው።
እረ እንደው ምን ይሻለኛል ብላ ሰው ስታማክር ”ምነው አንቺ በግርሽ ብቻ ትሄጃለሽ በጅሽ ሂጂ እንጂ ” ብለው መብት ገዳይ መፍትሄ ሰጧትእንዲህ አይነቱ ነገር ሲገጥመን ተሟግተን መብታችንን ማስከበር ሳይሆን ለመብታችን ከፍለን ነው ጉዳዩን የምንዘጋው።
ብዙ ያገልግሎት ሰጪ ተቋማት የነሱ እዛጋ የመቀመጣቸው ትርጉም ያንን የነሱን ግልጋሎት የሚፈልግ ሰው በመኖሩ ነው ለምሳሌ ለአንድ ዶክተር ታካሚው የሱ እንጀራ ገመድ ነው ያ ታካሚ ባይደኖር የሱ አስፈላጊነት ዜሮ እንደሚገባ ማስተዋል አለበት አንድ ቀበሌ ላይ የሚሰራ ሰው የቀበሌው ኗሪዎች የሱ እዛጋ የመኖር ዋስትናዎች መሆናቸውን ማስተዋል አለበት በሱ የምያጋለግል ሙሉ መብት እንዳላቸው ማወቅና መገንዘብ አለበትለመብታቸው እንዲከፍሉት መጠበቅ የለበትም ።
ለመብታችን መክፈል የለብንም ይህ ጉዳይ ምናልባት ዋጋ ሊያስከፍለን ይችላል ቢሆንም ግን በጋራ ተዋግተን ልናስቆመው ይገባልእንደውም እኔ ምን እላለሁ ሙስና በሁለት ይከፈላል አንዳንዴ ሰዎች በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ለመብታቸው ይከፍላሉ፤ ሌላኛው ደግሞ የማይገባቸውን ለመንጠቅ ሙስና ይሰጣሉ።
ሙስና ያለሰጪው ምንጩ የደረቀ ወንዝ ነው የሆነ ድረስ ሊቆይ ይችላል ግን ወንዙ ያለምንጩ ሀሩሩን መቋቋም ስለማይችል ያለማንም አጋዥ ይደርቃል ነገር ግን ሰጪው እያለ መንግስት ብቻዬን ልዋጋ ገድቤ ላቁመው ካለ አንድ እጅ ብቻውን እንደማጨብጨብ ይሆንና ወንዙ አቅጣጫውን ቀይሮ መፍሰስ ይጀምራል ።
የማይገባቸውን ለማግኘት ሲሉ የሚከፍሉትን ማስቆም ባንችልም ቢያንስ ሰዎች የትኛው መብታቸው መሆኑን አውቀው ለመብታቸው መክፈል ቢያቆሙ የሙስናን ችግር በግማሽ መቀነስ ያስችለን ይሆናል ህገ ወጦች መብቱን ሊጥሱ ሲከጅላቸው መብቱት ሚያስመልሰው ከፍሎ ሳይሆን ተዋግቶ ነው ለዚህ ደግሞ እንደ ወታደር የውጊያ ስልት ፤ ዝግጅት ፤ ትጥቅ ፤ እውቀት የመሳሰሉት ያስፈልጉታል።
ለመብቴ አልከፍልም ስንል በመጀመሪያ መብቴ ነው ወይ የሚል የእውቀት ዝግጅት፤ ይህንን መብቴ ስለተጣሰ በማን በኩል ጠይቄ ነው ማስመልሰው የሚል የስልት ቅየሳ ፤ማስረጃ አለኝ ወይ የሚል የትጥቅ ዝግጅት ያስፈልገናል በመጨረሻም መዋጋት።
ይህንን ጹፍ ለመጻፍ ካሰብኩ ጀምሮ ብዙ ጊዜ አስተውያለሁ ፤ የታክሲ ረዳቶች መልስ ከመስጠታቸው በፊት በአይናቸው ገርመም ያደርጉና እድሜያቸው ለ ገፉ ሰዎች መልስ ይመልሳሉ ለምን ብዙ ጊዜ ትልልቅ ሰዎች መልሳቸውን ይጠይቃሉ ወጣቱስ ? ወጣቱ መብቱን ቢያውቅም መብቱን አይጠይቅም መብቱን መጠየቅ እንደ መጨቃጨቅ ይቆጥረዋል መብቱን ስለማይጠይቅ መብቱ እንደ ግዴታው ተቆጥሮ ለ መብቱ መገበር ይጀምራል።
አገልግሎት ሰጪ ሚኒባሶች ሚኒባሱ የ ባለቤቱ ቢሆንም አገልግሎት የሚሰጡት ግን ለኛ ነው፤ ስለዚህ በግራም አለ በቀኝ የኛ ነው ለዚህ ማሳያ የሚሆነው መንግስት ሚኒባሶቹ ህዝቡን እንዲያገለግሉ በማሰብ የነዳጅ ድጎማ እና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞችን ከሌሎች ለህዝብ አገልግሎት ከማይሰጡ ተሽከርካሪዎች በተሻለ ማቅረቡ ነው።
እነሱ ግን በማናለብኝነት የአገልግሎት ታሪፍ ይጨምራሉ፤ የስምሪት መስመር ይቀይራሉ ፤ሲያሻቸውም ግማሽ መስመር ድረስ ይጭናሉ በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን መብቴ ነው ለምን ይህን ታደርጋለክ ብሎ የሚጠይቅ መጠየቅ ብቻ ሳይሆን አጥፊውን የሚያስቀጣ የለም።
ማህበረሰቡ መጀምሪያ ሲያሳድግ አጠፋ ”ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል ” እያለ ልጁን አሳደገ የልጁ ስብና እንዲበላሽ ትልቁን ሚና ተጫወተ አሁን ላይ በዚህ አስተሳሰብ ውስጥ ያደገ ልጅ ሲሾም ቶሎ ብሎ ሳይሻር መብላት እንዳለበት ያስባል እውነቱ ግን ከዚህ በተለየ ነው የተሾመው ፣ስልጣን የተሰጠው ህዝብን ለማገልገል ነው። ስልጣን የህዝብን መብት መሸጫ አለመሆኑን ለማሳየት ሲያጠፋ ዝም ብሎ ከማየትና የጥፋቱ ተባባሪ ከመሆን መቆጠብ ያስፈልጋል።
ከሁሉም በላይ እንደ ሀገር የጀመርነውን አዲስ ለውጥ ለማስቀጠል ከሁሉም በላይ ለመብቴ አልከፍልም ብለው እራሳቸውን ነጻ የሚያወጡ፤ ያላግባብ ገብርልኝ ሲባሉ ወኔያቸው የሚቆጣ፤መብት እንጂ ሸቀጥ አይደለም አልሸጥም የሚሉ ብዙ ጀግኖችን ማፍራት አለብን ለዚህ ደግሞሁላችንም ራሳችን ልናዘጋጅ ይገባል።
በመክሊት ወንድወሰን
አዲስ ዘመን ታህሳስ 28 ቀን 2015 ዓ.ም