ብሔራዊ ስጋት እየሆነ ያለው ሌብነት ሀገር ከማፍረሱ በፊት ለመቆጣጠር እየተካሄደ ያለው ትግል ተጠናክሮ ቀጥሏል። ሌቦችን በማጋለጥ ሙስናን ከሥር መሠረቱ ለመንቀል የሚደረገው የትግል ቀስትም ወደሚመለከታቸው አካላት አነጣጥሯል። ባለፉት ጊዜያት ሌቦችን ከተደበቁበት የሌብነት ጎሬ ፈልፍሎ በመመንጠር ለሕግ ለማቅረብ በተደረገው ጥረት ‹‹አባይን በጭልፋ››ይሉት አይነት ቢሆንም በጣም ጥቂቶቹን በሌብነት የተጠረጠሩ አካላትን በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ የማድረጉ ጅምር አበረታች ነው።
ሌቦችን ለመታገል የተጀመረው ዘመቻ ተጠናክሮ ቢቀጥልም በሚፈለገው መጠን እየተካሄደ ነው ብሎ አፍን ሞልቶ ለመናገር በሚያስችል ደረጃ ላይ ነው ብሎ ለመናገር የሚያስደፍር አይደለም። እነዚህን አካላት ወደ ሕግ ለማምጣት ሆነ ለማጋለጥ የሚደረገውን ጥረት በአጭር ጊዜ ለማሳካት ብዙ ፈተናዎች፣ ጋሬጣዎችንና እንቅፋቶች ማጋጠማቸው የማይቀር ነው። ከዘመቻው ማግስት ጀምሮ እያጋጠመ ያለውም ይሄው ነው።
ለዚህም ምክንያቱ ደግሞ ሌብነትን ለመታገል የተያዘው የሞት ሽረት ትግል መሆኑ የገባቸው ሌቦች ሳይቀድሙን እንቅደማቸው አይነት እሽቅድምድሞሽ የተያያዙበት መሆናቸው ነው። የቁርጡ ቀን አፍጥጦ መምጣቱ ደግሞ እነ አያ ሌቦ እስከዛሬ ሲፈነጩበት የከረሙትን ሜዳ ሊያሳጣቸው እንደሚችል ስለገባቸው ዙሪያቸው እያንዣበበ ያለው የተጠያቂነት ጉዳይ እረፍት ነስቷቸዋል።
ሌቦቹ ምንም እንኳን መስረቃቸው እንዳይታወቅ ለማድረግ የሚሄዱበት መንገድ የተጠናና ስውር ቢሆንም ጊዜው የደረሰ ዕለት /አንድ ቀን መጋለጣቸው እንደማይቀር ግን ያውቁታል። እስከዛሬም ቢሆን የሕግ ስርአቱ ሆነ ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት በተጠያቂነት ወደ ፍትህ ሊያመጧቸው ባለመቻላቸው የልብ ልብ ማግኘታቸው እንጂ ተጠያቂነታቸው ጠፍቷቸው አይደለም።
ከዚህም ባለፈ አካሄዳቸውም ከብዙ አካላት ጋር የሚገናኝ የአንዱ ጫፍ ሲመዘዝ ሌላውን በመጎተት ብዙዎችን በአንድ አጣምሮ የያዘ መሆኑ እና የጥፋት መንገዳቸው የተቆላለፈ መሆኑ የማይደረስባቸው ፤ቢደረስባቸውም በቀላሉ ወደ ፍርድ እንቀርባለን የሚል ስጋት እንዳይኖራቸው አድርጓቸዋል።
ይህ እንደሸረሪት ድር የሚተሳሰር ሰንሰለት ከላይኛው
የመንግሥት ባለስልጣናት ጀምሮ እስከታችኛው ሠራተኛ ድረስ የተሳሰረ በመሆኑ የድሩን ውል ለማግኘት በቀላሉ የማይታሰብና ጊዜ የሚጠይቅ ጉዳይ ቢሆንም የጊዜ ጉዳይ ይሆናል እንጂ ውሉ መገኘቱ የማይቀር ነው።
”የሌባ ልብ ደንዳና ነው” እንደሚባለው እነዚህ ሀይሎች ይህ ትግል ከተጀመረ ጊዜ ወዲህ እንኳን ባለው ሁኔታ በሕግ እጠየቃለሁ የሚል ፍራቻን አድሮባቸው ከቀደመው ተግባራቸው እየተቆጠቡ አይደለም ። እንዲያው በአንዳንድ ሁኔታዎች ስራቸው እየተባባሰና እና ይፋ እያወጣ ያለ ስለመሆኑ ማሳያዎች አሉ።
የጸረ-ሙስና ትግሉ ቀጥሎ ሕግ የብዙ ሌቦችን በር ማንኳኳት ሲጀምር የተጀመረውን ትግል አቅጣጫ ለማስለወጥ የሚቻላቸውን ሁሉ እያደረጉ ነው። በየቦታው የተለያዩ አጀንዳዎች በመፍጠር የህዝቡን አይንና ጆሮ ለመያዝ ጥረት እያደረጉ ነው።
የሕዝብ እንባጠባቂ ተቋም ባለፈው ወር ይፋ ያደረገው ጥናት እንዳመለከተው፤እጃቸው ረጅም የሆኑት አንዳንድ የመንግሥት ኃላፊዎች በሙስና /ሌብነት ውስጥ ተደፍቀዋል።ይህም ትግሉን ውስብስብና እልህ አስጨራሽ እንደሚያደርገው ይታመናል ።
ተቋሙ በጥናት አረጋገጥኩት ባለው መረጃ መሠረት የነዳጅ ድጎማው ከታለመለት አላማ ውጭ ለሌብነት መጋለጡ ፣ ኮንትሮባንድና ብክነትም በስፋት እየተስተዋለ መሆኑ በዚህ ጉዳይም አንዳንድ የክልል የመንግሥት ባለስልጣን እጅ እንዳለበት አስታውቋል።
በጥናቱ እንደተመላከተ፤ የነዳጅ ዱጎማ ውሳኔ የነዳጅ ድጎማ አሠራር ባፈነገጠ መልኩ ባለሥልጣናቱ በነዳጅ ኮንትሮባንድ ውስጥ ቤተሰቦቻቸውን በማሳተፍና ትስስር በመፍጠር፣ አሠራሩ ያላግባብ የግል መጠቀሚያ እየሆነ እንደሆነ ተመላክቷል።
‹‹አይን ሲመታ አፍንጫ ያለቅሳል›› ማለት ይሄኔ አይደለም ትላለችሁ። ስልጣንን መከታ አድርጎ የሚፈጸመው ሌብነት ደግሞ ከላይ ያለው አካል እንዳይጋለጥ በስልጣኑ መጠቀም እራሱን ለመከላከል ይሞክራል። ሁሉም ሰው ከሕግ በታች ነው የሚለው ሕግ በጽሁፍ ብቻ ያለ እንጂ ለእሱ የሚያገለግል አይመስለውም።
እነዚህ አይነቶቹ በስልጣናቸው የሚባልጉ ባለስልጣናት በሕግ አግባብ መቀጣት አለባቸው። የህዝብ እንባ ጠባቂ ተቋም ባደረገው ጥናት ያገኘውን መረጃ ይፋ ሲያደርግ የሚመለከታቸው አካላት ደግሞ ሌቦችን ለሕግ አሳልፈው መስጠት ይጠበቅባቸዋል።
ይሄ ካልሆነ ግን ባለስልጣናቱ በስልጣናቸው፤ ባለሀብቶች ደግሞ በገንዘባቸው እየተመኩ እንደአሻቸው የሚያሽከረክሩት ሀገር እንድትሆን መፍቀድ እንደማለት ነው። ለዚህም ሲባል የጸረ-ሙስና ትግሉ ያለ ርህራሄ በተጀመረበት ግለት ሊቀጥል ይገባል።
ሌብነትን አስመልክቶ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የተናገሩት ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው። እሳቸው እንደሚሉት የሌብነት ትግሉ ሲጀመር በርካታ ነውጥ ማስነሳቱን ጠቅሰው፤ አሁን በሀገሪቱ የሚታየው ነውጥ በሙሉ የሌብነት ዘመቻ ይቅር ለማለት እንደሆነ ማሳያ መሆኑን አመላክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ የሌብነት ዘመቻውን አጠናክራ ካልቀጠለች አሁን የሚገጥማት ፈተና በሌብነትም ምክንያት ስለሚገጥማት ሌብነትን መታገል አጠናክረን እንቀጥላለን ማለታቸው የሚታወስ ነው።
ሀገሪቷ ወደለየለት ስርቆትና ሌብነት እንድትገባ የሚፈልጉ አካላት መቼም ቢሆን የተደላደለ የምቾት አካባቢያቸው እንዲነካ አይፈልጉምና ተኝተው እንደማያድሩ የታወቀ ነው። የነዚህን አካላት ህልም ሽባ ማድረግ የሚቻለው ደግሞ ሌብነትን ከሥር መሠረቱ በመንቀል ሀገር የማትረፍ ዘመቻው ተጠናክሮ ሲቀጥል ነው ።
የጸረ-ሙስና ትግሉ ብዙ መስዋዕትነት፤ የበርካታ ብርቱ ክንዶች ርብርብ እና አንድነት እንዲሁም ቁርጠኝነት የሚጠይቅ ተግባር በመሆኑ መንግሥትና ህብረተሰቡ ተባብረው በህብረት መሥራት ይጠበቅባቸዋል። የፍትህ አካላትም ሕግን የማስከበር ኃላፊነታቸውን በአግባቡ መወጣት ይኖርባቸዋል። ማንም ይሁን ማንም ሁሉም ከሕግ በታች መሆኑን በተጨባጭ ማሳየት ይኖርባቸዋል።
መንግሥትም በበኩሉ ለሌብነት ክፍት የሆኑ አሠራሮችን በማጥናት ተጠያቂነት ያለው አሠራርን በመዘርጋት በትኩረት መሥራት ይጠበቃል። ህብረተሰቡም አገልግሎት ፈልጎ ወደ መንግሥት ተቋማት በሚሄድበት ጊዜ ሕጋዊ አካሄድ በመከተል ለሌብነት የሚዳረጉ አሠራሮች ሲያጋጥሙ በመቃወም እነዚህን አካላት በመጠቆም መተባበር ይገባዋል።
ሌቦች ከህብረተሰቡ እይታ ውጪ አይደሉምና የሀገር ነቀርሳ የሆነው ሌብነት ሀገር ከማፍረሱ በፊት ከወዲሁ ለማስቆም የሚደረገው ዘመቻ የሁሉንም የአካላት ተሳትፎ የሚጠይቅ ነው። በመሆኑም ከሊቅ እስከደቂቅ ያለው የህብረተሰብ ክፍል ስርቆት ባለመፈጸም፤ ሲሰርቅ የተገኘን ሌባ ደግሞ በመጠቆም የበኩሉን ኃላፊነት መወጣት አለበት ባይ ነኝ ። ቸር እንሰንበት ።
ትንሳኤ አበራ
አዲስ ዘመን ታህሳስ 26 ቀን 2015 ዓ.ም