በሰው ልጆች ታሪክ በእልቂታቸውም ሆነ በአውዳሚነታቸው የሚታወቁት የ1ኛውም ሆነ የ2ኛው የዓለም ጦርነቶች እንዲሁም ከዚያ በፊትና በኋላ የተካሄዱ ዘግናኝ ጦርነቶች የተቀሰቀሱት በቀላሉ መሆኑን የታሪክ ድርሳናት ያትታሉ። ሆኖም መውጫቸው ማለት ወደ ሰላም መምጣቱ እጅግ ፈታኝና ውስብስብ ነው። የጦርነቱ ተዋንያን በሰላም ስምምነቱ የገቡትን ቃል ለመፈጸም የሚያሳዩት ማመንታትና እግር ጉተታ ለሰላም ስምምነቱ ሳንካ ይፈጥራል። የሰላም ስምምነቱ ሀቀኛ ሳይሆን ሲቀርና ለጊዜ መግዣ ታስቦ ሲደረግ አይደለም ሰላም ማስፈን ጦርነቱን ማስቆም አይቻልም። በሰላም ስምምነቱ ትግበራ ሕዝብ በቀጥታና በባለቤትነት ካልተሳተፈም የመጽናቱ ጉዳይ አጠያያቂ ይሆናል።
የኮሎምቢያ አማጽያንና የኮሎምቢያ መንግስት ስምምነቶችን እና የእስራኤልና የፍልስጤም ተደጋጋሚ ስምምነቶችን በአብነት ማንሳት ይቻላል። በፕሪቶርያ በሕወሓትና በፌደራል መንግስት የተደረሰው የሰላም ስምምነት ግን ከተጠበቀውና ከተገመተው በላይ እየተፈጸመ ይገኛል። ከሰላም ስምምነቱ ወዲህ ኮማንዶዎች በሽሬ ተገናኝተው መምከራቸው በተለይ በያዝነው ሳምንት በአፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ የተመራ የሚንስትሮች ፣ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽነሮች ፣ የዋና ስራ አስፈጻሚዎች ልዑክ በመቀሌ ተገኝቶ በሰላም ስምምነቱ ሒደት ከሕወሓት አመራሮችና ከሕዝብ ጋር መምከሩ ፤ በቅርቡ በኢትዮጵያና በትግራይ የጦር አዛዦች በኬንያ በተደረሰው ስምምነት መሰረት የአፍሪካ ህብረት የክትትል፣ ማረጋገጥ እና ማሟላት ኮሚቴ ተቋቁሞ የመጀመሪያ ስራው በትግራይ ኣጉላዕ ተገኝቶ የትግራይ ሰራዊት የከባድ መሳሪያ ትጥቅ የተሰበሰበበት አካባቢ ጎበኝተዋል። እነ ኦሊሴጎን ኦባሳንጆም በመቀሌ ተገኝተው ሂደቱን መከታተላቸው በወሳኝ መታጠፊያነት ሊወሳ ይችላል።
ከሁሉም በላይ ግን የፕሪቶርያውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ የፌደራል መንግስት የዕለት ደራሽ እርዳታንና መድኃኒትን ያለገደብ ማቅረቡ ፤ መጀመሪያ የኢፌዴሪ የመከላከያ ኃይል በደረሰባቸው የትግራይ ከተሞች የመብራት ፣ የስልክ ፣ የባንክ አገልግሎት ለማስጀመር ሌት ተቀን መትጋቱ ፤ ወደ መቀሌ የኢትዮጵያ የአየር መንገድ በረራ መጀመሩ ከነገ ሰኞ ጀምሮ ደግሞ ወደ ሽሬ እንደሚያቀና መነገሩ፤ የጤና ተቋማትን ስራ ለማስጀመር እየተደረገ ያለው ርብርብ የሰላም ሂደቱን የቀደመ እምርታ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል። አንድምታው ግን ከዚህም የላቀ ነው። ላለፉት ሁለት አመታት በጦርነት ላይ የነበረው ሕዝብ የሰላም ስምምነቱን ፍሬ ወዲያው ወዲያው እንዲያጣጥም ያደረገ እርምጃ ስለሆነ የጦርነትንና የሰላም ልዩነትን በተግባር ከመግለጡ ባሻገር ሕዝቡን ከሰላም ስምምነቱ ጎን እንዲቆም ያደረገ እና የሰላም ስምምነቱ ሳይሸራረፍ በሙላት እንዲፈጸም የላቀ አስተዋጾም ይኖረዋል።
ከዚህ በተጨማሪ የፌደራል መንግስት በሁሉም ኮሪደሮች እርዳታ በስፋት እያቀረበ መሆኑ፣ የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል አገልግሎት፣ ኢትዮ ቴሌኮም ፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክና የኢትዮጵያ አየር መንገድ አገልግሎታቸውን ተደራሽ ማድረጋቸው ከሰላም ስምምነቱ ባሻገር የትግራዋይን ልብና ልቦና የመማረክ እምቅ አቅም አለው። የሰላም ስምምነቱ ዋስትና ኦባሳንጆ ፣ ኡሁሩ ወይም የአፍሪካ ሕብረት አልያም አሜሪካና የአውሮፓ ሕብረት ሳይሆኑ የሰላም ስምምነቱ ዋስትና የትግራይ ክልል ሕዝብና የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። ሆኖም የትግራዋይን ልብና ልቦና ለማሸነፍ ከሚደረገው ጥረት ባልተናነሰ የተቀረውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ልብ ለማሸነፍም ስለ ሰላም ስምምነቱና ስለ አፈጻጸም ሒደቱ ከስር ከስር ማስገንዘብ በተለይ የአማራና የአፋር ሕዝብ ደግሞ የጦርነቱ ግንባር ቀደም ገፈት ቀማሽ ስለሆኑ በሂደቱ ግንባር ቀደም ተሳታፊና የሰላም ስምምነቱ ባለቤት ሊሆን ይገባል።
ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ ወደ መሪነት ከመጡበት ሰዓት አንስቶ ይህ ጦርነት እንዳይቀሰቀስ ሕወሓትን ለማግባባት ያላደረጉት ጥረት የለም። ከባዕለ ሲመታቸው የፓርላማ የመጀመሪያ ንግግር እስከ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም የሰሜን ዕዝ ክህደትና ጥቃት ድረስ ልዩነቱ በሰላም ይፈታል የሚል ተስፋ ነበራቸው። በዚሁ ቀን ምሽት ሳይቀር ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በስልክ የክልሉን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት ስለተያዙ እቅዶች ከተወያዩ በኋላ አዲሱን የብር ኖት ለማድረስና አሮጌውን ብር ለማምጣት ሁለት የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላኖች ምሽት መቀሌ አርፈዋል።
ይህ በመንግስት በኩል የነበረን የሰላም ፍላጎት ያሳያል። ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ ለሰላም ካላቸው ቁርጠኝነትና ጦርነት ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ በውትድርና ሕይወታቸው ጠንቅቀው ስለሚያውቁት፤ ጓደኞቻቸውንና ወንድማቸውን ስለነጠቃቸው ፤ ጦርነት የሀገርን ኢኮኖሚ ምን ያህል እንደሚያወድም አበክረው ስለተገነዘቡና ፤ የትግራይ ሕዝብም ጦርነት ይበቃዋል በሚል እምነትና የጦርነት ነጋሪት የሚጎስሙ ኃይሎች የድሀን ልጅ የእሳት ራት ያደርጋሉ እንጂ እነሱ አይዋጉም በማለት ለትግራይም ሆነ ለሌሎች ሕዝቦች ደህንነት ሲሉ እስከ መጨረሻው ሰዓት ሆደ ሰፊነትንና ትዕግስትን መርጠዋል።
ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር አይደለም ጦርነትን ተራ ግጭት እንኳ ለመከላከል ሲሉ ለያዥ ለገናዥ አስቸገርው እያለ ከዛሬ ነገ ይለወጣሉ ፣ ይመከራሉ፣ ይዘከራሉ ሲሉ በሆደ ሰፊነትና አንዳንድ ጊዜም አይተው እንዳላዩ በማለፋቸው መንግስታቸው እንደደካማ በመታየቱ ሸላዩና አቅራሪታው ተበርክቶ ነበር። የታጠቁ ኃይሎች “ማን የማንን ትጥቅ ያስፈታል !? “ እስከሚል እብሪት ደረሰው ነበር። ሸኔ በምዕራብ ኦሮሚያ ፣ በቦረና ፣ በጉጂ ዞኖችና በሌሎች የክልሉ ከተሞች በኦሮሞና በአማራ ሕዝቦች ላይ ለማየት የሚዘገንን ለመስማት የሚሰቀጥጥ ጭካኔ የተሞላበት ግፍ ፈጽመዋል። መንግስት የለም የሚለውን ጀብደኝነት ጨምሮ ሕገ መንግስቱን በኃይል እስከመናድ በመንቀሳቀስ የመጨረሻውን ቀይ መስመር እስኪያልፉ ታግሰዋል።
ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ሀገሪቱን ከጠብመንጃ አዙሪት ለማውጣትና ከዚህ ቀደም የነበሩ ገዥዎች ያልሄዱበትን የሆደ ሰፊነትና ቁጭ ብሎ የመነጋገር መንገድ በመምረጣቸው በልኩ እውቅና ሊሰጣቸውና አብዛኛው ዜጋ ከጎናቸው ሊቆም ሲገባ መንግስታቸው በልፍስፍስነት ከመወቀሱ ባሻገር ፓርቲያቸውም ሆነ እሳቸው ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ ደጋፊያቸውና ተከታያቸው ብዥታና ድንጋሬ ላይ እንዲወድቁ አድርጓል። ይሁንና የጥቅምት 24ቱን ታላቅ ክህደት ተከትሎ የሕግ የበላይነትን ለማስከበር ግንባር ድረስ መዝመታቸው፤ የሀገር ህልውናን ለማስቀጠል ያሳዩት ቁርጠኝነት እና ሰራዊቱ ከተፈጸመበት ታሪክና ትውልድ ይቅር ከማይለው ክህደት በኋላ ሞራሉና ወኔው አንሰራርቶ በእልህና በቁጭት ተነሳስቶ የሀገሩን ህልውናና የግዛት አንድነት በማስከበሩ ሒደት በነበራቸው ሚና በሕዝቡ ዘንድ መልሰው ሞገስ ማግኘት ችለዋል።
የሀገራችንን ፖለቲካና ታሪክ እንደ አዲስ የሚበይን፤ የሀገሪቱን ህልውና በጽኑ መሰረት ላይ የሚያኖር እና መጻኢ እድሏን ወገግ የሚያደርገው ይህ አንጸባራቂ ድል የተመዘገበው በእሳቸው እና በየደረጃው ያለው ወታደራዊና ሲቪል አመራር የተንሰላሰለና የተቀናጀ ብልህ አመራር በመስጠቱ ነው። የዓለም ታሪክ እንደሚያስታውሰን ጦርነትና የቀውስ ጊዜ የሀገራት መሪዎች ተቀባይነት የሚወሰነው ጦርነቱ በመሩበት ስልትና ባስመዘገቡት ድልና ቀውሱን በፈቱበት አግባብ ነው።
ከዚህ አንጻር ክቡር ጠቅላይ ሚንስትሩ ሆኑ ሰራዊቱ በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ዘንድ አድናቆት አትርፈዋል። በአራቱም የሀገሪቱ ማዕዘናት ሕዝቡ ያለ ልዩነት ደጀንነቱን ማረጋገጡ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው። ከፍ ብዬ ለማንሳት እንደሞከርሁት እሳቸውም ሆኑ መንግስታቸው ለሰላም ፣ ለሆደ ሰፊነት ፣ ተቀራርቦ ለመነጋገርና ሀገሪቱም ሆነ የትግራይ ሕዝብ ጦርነት ይበቃቸዋል በማለታቸው ያጡትን ተቀባይነትና ተከታይ ብቻ ሳይሆን ዳር ቆመው ለውጡን በመጠራጠር ያዩ የነበሩትን ሳይቀር አቋማቸውን እንደገና እንዲመረምሩ አድርጓቸዋል። የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥና የህልውና ዘመቻው በአንጸባራቂ ድል ቢጠናቀቅም የትግራዋይን ልብና አእምሮ በፍቅር ለመማረክ የተደረገው ጥረት አጥጋቢ ስላልነበረ የተገኘውን ወታደራዊ ድል ማጽናት አልተቻለም። አሁንም ያለፈው ስህተት እንዳይደገምና የሰላም ስምምነቱን ወደ ተሟላ ምክክርና እርቅ ለማሸጋገር የትግራዋይን ልብ መማረክ ላይ ጠንክሮ መስራት ይጠይቃል።
ፈጣሪ ከብልቶቻችን ሁሉ ያስቀደመው ልባችንን ነው። እንደ ፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ሁሉ አንድ የሕግ አዋቂ ፈጣሪን ሊፈትነው ፤ “ መምህር ሆይ ፥ ከሕግ ማንኛይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት? ብሎ ጠየቀው። “ፈጣሪም በታላቁ ቅዱስ መጽሐፍ ማቴዎስ 22 ÷ 37 _ 38 ላይ እንዲህ ሲል ይመልስለታል ፤ “ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ ። ታላቂቱና ፊተኛይቱ ትእዛዝ ይህች ናት። “ በዚህ ታላቅና ቀዳሚ ትዕዛዝ እየሱስ ክርስቶስ ከነፍስም ሆነ ከአሳብ በፊት ልብን እንዳስቀደም እንረዳለን።
የ32ኛው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የፍራንክሊን ዴሎን ሮዝቬልት ባለቤትና ቀዳማይ እመቤት ኤሌንኖር ሮዝቬልት ፤ ሮዝቬልትን ጨምሮ የበርካታ ፕሬዝዳንቶች አማካሪና ሊቅ የነበረውን በርናንድ በሩክ ፤ “ አእምሮዬና ልቤ በሀሳብ ቢለያዩ ማንኛውን ልከተል !? “ ስትል ትጠይቀዋለች ፣ እሱም ያለምንም ማወላወል ፣” ልብሽን ተከተይ “ ሲል ይመልስላታል። እነዚህ መንፈሳዊና አለማዊ ዋቢዎች ልብ በሰው ልጅ ዘንድ ያለውን ከፍ ያለ ስፍራ ያሳያል። በነገራችን ላይ ይህ የሰላም ስምምነት ሁለት ግንባሮች አሉት። የመጀመሪያው ሀሰተኛ፣ የተዛባና በሴራ ኀልዮት የተለወሰና የተበረዘ መረጃ የሚነዛው መደበኛና ማህበራዊ ሚዲያ ሲሆን ፤ ሁለተኛው ግንባር ደግሞ ከ50 አመት በላይ የተዘራው የተሳሳተ ትርክት ያሸፈተውን የትግራዋይን ልብ መማረክ ነው።
በዲፕሎማሲው መልክዓ ከ30 አመታት ወዲህ ብቅ እንዳለ የሚነገርለት የመማረክ ወይም የማግባባት ጥረት (የሶፍት ፓወር) መንግስታት እንዴት በሌሎች ሀገራት ላይ ተፅዕኖ እንደሚያሳድሩ ለመረዳት የማይተካ ሚና እንዳለው መስከረም መግቢያ ላይ ለንባብ የበቃው “ ፎሪን ፓሊሲ “ መጽሔት ያትታል ። አሜሪካዊው የፖለቲካ ሳይንቲስት ጆሴፍ ኔይ ፤ ሶፍት ፓወር አንድ ሀገር በምትከተለው የፖለቲካ ስርዓት ፤ ፖሊሲ ፣ እሴቶች እንዲሁም በሲቪል ማህበረሰቧና በባህሏ አማካኝነት ሀገራትን የመማረክና የመሳብ ዲፕሎማሲያዊ ሀቲት ነው።
የሕዝቦችን አእምሮና ልብ በመማረክ (አትራክሽን) ላይ የተመሰረተ የዲፕሎማሲ አይነት ነው። ሀርድ ዲፕሎማሲ ከዚህ በተቃራኒው ወታደራዊ ኃይልንና ጉልበትን የሚጠቀም ነው። አሜሪካ የሳዳምን በማስከተል የታሊባንን አገዛዞች በጦር ሜዳ ማንበርከክ ብትችልም ፤ የኢራቃውያንንና የአፍጋኒስታውያንን ልብና አእምሮ መማረክ ላይ ባለመስራቱ ተልዕኮውን ሙሉ በሙሉ ሊያሳካና ግቡን ሊመታ አልቻለም። ሶፍት ፓወር ምን ያህል ወሳኝ ሚና እንዳለው ከዚህ መረዳት ይቻላል። የአሜሪካ ዴሞክራሲ፣ እሴቶች ፣ ኢኮኖሚያዊ ብልጽግና ፣ የሰላም ጓድ ፣ ዩኤስኤይድ፣ ሆሊውድ ፣ የትምህርት ተቋማት ሙዚቃው ፣ ወዘተረፈ የሀገራትን ልብና አእምሮ መማረኪያ የሶፍት ፓወር አካል ናቸው።
እንደ መውጫ
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የመጀመሪያውን የወይራ ዝንጣፊ ሀገር እየተመለከተና እያዳመጠ በግልፅ የላኩት በመጋቢት 24 ቀን ፣ 2010 ዓ.ም በፓርላማ የበዓለ ሲመት ንግግራቸው ነበር። ስለ ሕወሓት/ኢህአዴግ ኃጢያት ተሸካሚ ሆነው የኢትዮጵያ ሕዝብን ይቅርታ ጠይቀው ነበር። ከዚያ በኋላም በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ስለሰላም ፣ እርቅና አካታችነት ያላነሱበት ጊዜ አልነበረም።
ይህ ጽኑ አቋማቸው እሳቸውንም ፓርቲያቸውን ውድ ዋጋ አስከፍሏል። ለውጡ ግለቱን ጠብቆ እንዳይሄድ ተፅዕኖ እስከማሳደርና ለሴራ ፖለቲካ እንዲጋለጥ በር እስከመክፈት ደርሶ ነበር። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መረጃ ማጣሪያ በዚያው ሰሞን ይፋ ባደረገው ሰነድ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ክልሉ በልማትና በሰላም ላይ እንዲያተኩር በተደጋጋሚ መክረዋል። ዘክረዋል።
ሕወሓት በተደጋጋሚ በሰላማዊ መልኩ እንዲንቀሳቀስና ለውጡን ለትግራይ ሕዝብ ሰላም እንዲጠቀምበት ይፋዊ ሊባሉ የሚችሉ ወደ 20 የሚጠጉ የሰላም ጥሪዎች ተደርገዋል። ይህ መንግስት ትላንትም ዛሬም ለሰላም የነበረውን መሻት ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ነው። የዛሬው ሰላም የዚህ ያልተቋረጠ የሰላም ጥረት አካል ነው። መንግስት ከሰላም ስምምነቱ ጎን ለጎን የጀመረውን የትግራይን ሕዝብ ልብና አእምሮ የመማረክ ጥረት አጠናክሮ በመቀጠል የሰላም ስምምነቱን ማጽናት ይጠበቅበታል።
ሻሎም አሜን፡፡
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን እሁድ ታኅሣሥ 23 ቀን 2015 ዓ.ም