የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎ ባለፈው ሰኞ መቀሌ ላይ ባደረጉት ንግግር የደረሰውን ጥፋት ‹‹መማሪያ እናድርገው›› ብለው ነበር። ዳግም እንዳይከሰት መማሪያ ይሁነን ማለታቸው ነው። ሰው የሚማረው ከመከራ ጭምር ነው፤ እንዲያውም ከመከራ መማር ያንን ነገር ላለመድገም የተሻለ አቅም ይሆናል፡፡
በርግጥ ጦርነት የሚያስከትለው ጣጣ ለማንም ግልጽ ነው፡፡ ሰብዓዊ እና ቁሳዊ ጥፋት፤ ማህበራዊ ምስቅልቅል ወዘተ ለእኛ ኢትዮጵያውያን እንደ አዲስ የሚነገረን አይደለም። የመጣንባቸው መንገዶች በዚህ ተግዳሮት የተፈጠሩ እና ብዙ ዋጋ ያስከፈሉን ናቸው፡፡
ከዚህም የተነሳ ወደ መቀሌ የሄደው የልዑካን ቡድን መቀሌ አሉላ አባ ነጋ አየር ማረፊያ ሲደርስ በሕወሓት አመራሮችና በመቀሌ ከተማ ነዋሪዎች አቀባበል ሲደረግለት ፤ የፌዴራል መንግሥት ተወካዮች እና የሕወሓት አመራሮች ሲተቃቀፉ ማየት ብዙዎችን አስደስቷል፡፡ ‹‹ኧረ በቃ ይበለን!›› ሲሉ ለነበሩ ሁሉ ፀሎታቸው ተሰምቶ፣ ምህላቸው ደርሷል፡፡
ከአዲስ አበባ መቀሌ የቀጥታ በረራ ተጀምሮ ተጓዦች መቀሌ ደርሰው ከቤተሰቦቻቸው ጋር ሲገናኙ የነበረው ሁነት የብዙዎችን ቀልብ ስቧል ፤ የማህበራዊ ገጾችን እና የመገናኛ ብዙሃን ዋንኛ አጀንዳ ሆኖም ሰንብቷል፡፡
ከመቀሌ አየር ማረፊያ የነበረውን ልብ የሚነካ የተጓዦች አቀባበል አስመልክተው የተለቀቁ ፎቶዎች፤ በጦርነቱ ምክንያት ተለያይተው የነበሩ ቤተሰቦች ተቃቅፈው ሲላቀሱ፣ መሬት ላይ ተደፍተው ምድሩን ሲስሙ፣ አንጋጠው ፈጣሪያቸውን ሲያመሰግኑ … እንድናይና የስሜቱ ተካፋይ እንድንሆን አድርገውናል። እንኳን በጦርነት በሰላም ጊዜ እንኳን ከቤተሰብ አለመገናኘት ምን ስሜት እንደሚፈጥር ለማንም ግልጽ ነው፡፡
ይህን መልካም ነገር እንድናይ ላደረጉን የፌዴራሉ መንግሥትም ሆነ የሕወሓት አመራሮች ምስጋና ይገባል። ምክንያቱም በጦርነቱ ወቅት የወቀስናቸው ‹‹ለምን ወደ ጥፋት ይሄዳሉ?›› ብለን ነው አይደል? ስለዚህ ያንን የወቀስንባቸውን ነገር ትተው ወደ ሰላም ሲሄዱ ማመስገን የግድ ነው፡፡ አለበለዚያ ያለመርህ ነበር ስንወቅሳቸው የነበረው ማለት ነው፡፡ ደቡብ አፍሪካ የተደረገውን ስምምነት እነሆ እስከ አሁን በተባለው መሰረት እየሄዱበት ነው፡፡
በአደባባይ ያየናቸው የዜጎቻችን ስሜቶች ለሰላም ስምምነቱ ተፈጻሚነት የሚመለከታቸው አካላት ከፍ ባለ ቁርጠኝነት እንዲንቀሳቀሱ የበለጠ ሀላፊነት እንዲሰማቸው የሚያስገድድ ነው፡፡ የተጀመረው የሰላም ጥረት በስኬት እንዲጠናቀቅ የበለጠ ለሰላም ታማኝ መሆን እንደሚኖርባቸው በተጨባጭ የሚያሳስብ ነው።
የሕወሓት ሊቀመንበር ዶክተር ደብረጽዮን ገብረ ሚካኤል የሰብዓዊ ድጋፍ እርዳታዎች መግባት እንዳለባቸው ሲያሳስቡ ቆይተው ‹‹ያለውን ሁኔታ ስለምናውቅ ቃል በተገባበት ማግስት ለምን አልገባም! አንልም›› ብለዋል፡፡ እንዲህ አይነት አስተዋይነትና መረዳዳት ሲኖር የታሰበው ሰላም ይመጣል፡፡
አመራሮቹ እንዲህ ቁርጠኛ ሲሆኑ ሕዝብም ቁርጠኛ መሆን አለበት፡፡ ለምሳሌ፤ ከአንዳንድ ወገኖች የሚሰማ አንድ የሚገርም ነገር አለ፡፡ ‹‹እንዲህ ሊተቃቀፉ ነው ያ ሁሉ ሰው ያለቀ?›› የሚል፡፡
ሰላምን ማምጣት የሚቻለው እኮ ያለፈውን በመተው እንጂ በዚያ ልክ ከተሄደ መቼም ቢሆን ሰላም የሚባል ነገር አይታሰብም፡፡ ለእነዚህ ሰዎች ሰላም የሚመጣው እንዴት ቢሆን ነበር? ምናልባት ጦርነቱ ቢቀጥል ነበር ሰላም የሚመጣ? ተጨማሪ ሰዎች ቢሞቱ ነበር ሰላም የሚመጣ? መሪዎች እንካ ሰላንትያ ቢሰዳደቡ ነበር ሰላም የሚመጣ?
ለተገኘው ሰላም የፌዴራሉ መንግሥትም ሆነ የሕወሓት አመራሮች እጅግ ሊመሰገኑ ይገባል ባይ ነኝ። እንዲያ ስንማረርበት የነበረው የውጭ አገራት ጣልቃ ገብነት ተረሳ ወይ? እንደዚያ ሲያደርጉ የነበረው እኮ የአፍሪካ አገራት በራሳቸው የሚፈቱት ችግር የለም፤ ያለ እኛ ጣልቃ ገብነት ምንም ነገር ማስተካከል አይችሉም በሚል ስሜት ነበር፡፡
አንድ አገሬን እወዳለሁ የሚል ኢትዮጵያዊ ዜጋ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አገራት ተምሳሌት ሆና የራሷን ችግር በራሷ ስትፈታ ከማየት በላይ ምን ሊያስደስተው ይችላል? እነዚያን ሊበታተኑ ከዓመት በፊት በጦርነት ሲፋለሙ የነበሩ አካላት ያለማንም ጣልቃ ገብነት መፍትሔ አበጅተው ሲተቃቀፉ ማየት የመሰልጠን መለያ ነው፡፡
ይህን ማድረግ የሚችሉት ምዕራባውያን ብቻ ናቸው ተብሎ የሚታሰበውን ነው ኢትዮጵያ ያደረገችው። ለአፍሪካውያን የሚመኙትም ሆነ ‹‹ነው›› ብለው የሚያምኑት የራስን ችግር በራስ መፍታት ሳይሆን ያላቋረጠ ጦርነት ውስጥ መቆየትን ነው፡፡
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ተምሳሌት እና ገናና አገር ናት ስንል ማሳያው ይሄው ነው፡፡ ለሌሎችም አገራት አስታራቂ እና ሰላም አስከባሪ ናት ሲባል ማረጋገጫው ይሄው ነው፤ የራሷን ችግር በራሷ መፍታት! ይሄ እንደ ቀላል የሚታይ አይደለም፡፡
እነዚያ ‹‹አለቀላቸው!›› ሲሉን የነበሩ ባላንጣ አገራት ስንተቃቀፍ ሲያዩ ምን ይሉ ይሆን? ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ ይህን የኢትዮጵያን ማንነት ማሳየት ለቀጣይም ማንነቷን የማታስደፍር መሆኗን ማሳየት ነው። ‹‹እነርሱ ቢጣሉም ገመናቸውን ወደ ውጭ አያወጡም›› የሚል ስም እንዲኖረን ያደርጋል፡፡ ተከፋፍለዋል ብሎ ለመዳፈር የሚያስብ እንኳን ቢኖር ‹‹እንዲህ መታረቅና መተቃቀፍ የሚችሉ ናቸው›› የሚል እሳቤ እንዲኖረው ያደርጋል፡፡
ኢትዮጵያ ከጥንትም ጀምሮ ያላት ታሪክ ይሄው ነው። በየትኛውም የውጭ የጥቃት ሙከራ ወቅት የተጣሉ ሁሉ አንድ ሆነው ጥቃት ሞካሪውን ጠላት የሚያዋርድ ታሪክ ነው ያለን፡፡ ይህ የጥንት ታሪክ እነሆ በ21ኛው ክፍለ ዘመንም ተደግሞ አረጋገጡ ማለት ነው፡፡
ባለፈው ሐሙስ የአፍሪካ ሕብረት ልዩ መልዕክተኛ ኦሊሴንጎን ኦባሳንጆ በመቀሌ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ የራሷን ችግር በራሷ መፍታቷን ‹‹Confidence Building›› ነበር ያሉት፡፡ በራስ መተማመንን የመገንባት አቅም መፍጠር በኢትዮጵያ ያለና የነበረ ነው፤ ይህን ለሌሎች አገራት ማሳየት ነው አገር ወዳድነት ማለት፡፡
በሰሜን ኢትዮጵያ ተፈጥሮ የነበረውን ችግር የምዕራባውያን ሚዲያዎች እንዴት ሲዘግቡት እንደነበር አይተናል፤ ሰምተናል፡፡ እነዚህ ተበታተኑ፣ ፈራረሱ ያሏቸው ወገኖች ሲተቃቀፉ ማሳየት ለአንድ ኢትዮጵያዊ ኩራት ነው መሆን ያለበት፡፡
የተጀመረውን ነገር ለማስቀጠል ከጊዜያዊ ስሜት መውጣት አለብን፡፡ ከግለሰባዊ ብሽሽቅ መውጣት አለብን፡፡ ምክንያቱም ይህ የአገር ጉዳይ ነው፡፡ የአገር ጉዳይ ደግሞ ከግለሰብ ስሜት በላይ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ከራሳቸው ስሜት በመነሳት ‹‹እንዲህ መደረግ ነበረበት!›› ሊሉ ይችላሉ፡፡ የአገርን ክብር ለማስጠበቅና በውጭ ገናና ሆኖ ለመታየት ግን የውስጥ ገመናን ሸፈን ተደርጎ ነው፡፡
ለእነዚህ ሁሉ ውሳኔዎቻቸው ነው የፌዴራሉን መንግሥት እና የሕወሓት አመራሮችን ማመስገን አለብን ያልኩት፡፡ በጦርነቱ ወቅት የወቀስናቸው የውጭ ጠላት መከፋፈላችንን አይቶ ይደፋፈረናል፣ ታሪካችንም ይህ አይደለም በሚል ነበር፡፡ ስለዚህ ይህን ተረድተው ወደ ሰላም ሲመጡ አለማመስገን የአገርን ኋላቀርነት እንደመመኘት ነው፡፡ በእነዚያ ለረሃብ በተዳረጉ የጦርነቱ ሰለባዎች ላይ ግፍ መሥራት ነው፡፡ በቀጣይም ሌላ መከራ እንደመጋበዝ ነው፡፡
ካለፈው መከራ እንማር!
ሚሊዮን ሺበሺ
አዲስ ዘመን እሁድ ታኅሣሥ 23 ቀን 2015 ዓ.ም