ለግማሽ ክፍለ ዘመን ያህል መዋቅራዊና ተቋማዊ ሆኖ የተዘራው የጥላቻ፣ የልዩነት፣ የሀሰተኛ ትርክትና የሴራና አሚካላና ኩርንችት ሳያንስ፤ በተቃዋሚዎች፣ በአክቲቪስቶችና በዩቲውበሮች ዕለት ዕለት እንደ ፍላጻ የሚንበለበለው የጥላቻና የልዩነት ፍላጻና ፖለቲካዊ ኢ-ትክክለኝነት ጨርቃችንን ማስጣሉ አልበቃ ብሎ የአገር መሪዎች ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ጤፉ ሲሆኑ ማድመጥና እንካ ስላንትያውን ሲቀላቀሉ ማየት ያማል። ለሚዲያ የሚሰጥ ቃለ መጠይቅም ሆነ መግለጫ እንዴት ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን ከግምት ማስገባት ይሳነዋል።
የሚታረቁ የማይመስሉ ልዩነቶች በጦዙበት፤ በለውጥ ሒደት ላይ እንዳለ፤ ለአገራዊ ምክክር እየተዘጋጀ፤ የሰላም ስምምነትን ዳር ለማድረስ ደፋ ቀና እንደሚል፤ በጎሳና በቋንቋ ላይ የተመሰረተ ፌደራላዊ ስርዓት እንዳቆመ፤ በማንነት ፍላጎቶች እና ጥያቄዎች እንደሚሳሳብ፤ የሕግ የበላይነት ክፍተት እንደሚስተዋልበት፣ ማንነትን ኢላማ ያደረጉ ጭፍጨፋዎች እንደሚፈጸሙበት፤ ወዘተ . አገርና ሕዝብ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት Political Correcteness (PC) የልብ ትርታው መሆኑ ለቅፅበት እንኳ ሊዘነጋ አይገባም። ለውጡ ከባተ ካለፉት አራት አመት ወዲህ እንኳ ብዙ ብዙ ዋጋ እያስከፈለን ይገኛል፡፡
በገለልተኛ ወገን በጥናት ባይረጋገጥም በለውጡ ተቀባይነት legitimacy ላይ ያስከተለውን አሉታዊ ተፅዕኖ በአብነት ማንሳት ይቻላል። የሴራ ፖለቲካና የበሬ ወለደ “ ወሬ “ ከፖለቲካ ትክክለኝነት ልምሻ ጋር ተጃምሎ፣ አብሮና ተባብሮ እንደ ሰደድ እሳት ሲዛመት ታዝበናል። በሁለቱ እኩይ ኃይላት መካከል ማለትም በሴራና በፖለቲካዊ ኢትክክለኝነት ያለውን እሳትና ጭድነት ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ተከስተው ከነበሩ ግጭቶች አኳያ ያስተውሏል፡፡
የፖለቲካዊ ትክክለኝነትን አንድምታዊና ታሪካዊ ዳራ በስሱ ከሸመን በኋላ ወደ አገራችን ፖለቲካዊ መልክዓ አውርደን እንከናነበዋለን። ክንንቡን ግን ለአገራችን ለሕዝባችን ክብር ስንል መልሰን እናወርደዋለን። ፖለቲካዊ ትክክለኝነት በ1930ዎቹ ጀምሮ ጥቅም ላይ እንደዋለ የተለያዩ በዘርፉ ላይ የተከተቡ ድርሳናት ያትታሉ። ወደ ኋላ ተመልሰን ይሄን ዘመን ስንቃኝ የዘር፣ የሀይማኖት፣ የፆታ፣ ሰብዓዊ መብት፣ የእኩልነት ጥያቄዎቸ ወዘተ . ጮህ ብለው መሰማት የጀመረበት ነበር ።
ፅንሰ ሀሳቡ በዚህ ተመሳሳይ ዘመን ጥቅም ላይ መዋል የጀመረበት መግፍኤም ይሄው ነው። በሌላ በኩል ፅንሰ ሀሳቡ ከግራ ዘመም አይዶሎጂ ማለትም ከሶሻሊስትና ኮምኒስት ርዕዮት ጋር ተያይዞ እንደመጣ ይነገራል። ሆኖም ብያኔው ግን በርዕዮት አለሙ ልክ የተሰፋ ነው። የፓርቲውን ሕገ ደንብ የሚያከብር መሪ ወይም አባል እንደ ፖለቲካዊ ትክክለኛ ይቆጠራል። በ1980ዎቹ አጋማሽ ደግሞ ሀሳቡ ከተለያዩ የስርዓተ ትምህርት ማሻሻያ ፕሮግራሞች እና ከአካዳሚያዊ ነፃነት ጋር ተያይዞ ይወሳ ነበር። ይሁንና እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1991 ፕሬዚዳንት ጆርጅ ቡሽ በሚቺጋን ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ ስለ “ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት “ አሳሳቢነት ከተናገሩ ወዲህ ፅንሰ ሀሳቡ ከስርዓተ ትምህርት ክለሳ፣ ከምረቃ ስነ ስርዓት ንግግር ደንብ፣ ከጾታና ዘር ጥቃት፣ ወዘተ ጋር መያያዝ ጀመረ፡፡
የፅንሰ ሀሳቡ ተገዳዳሪዎች ደግሞ ከአስተሳሰብ ፖሊስነት thought police እና መልካም ስምን፣ ዝናን ከማጥፋት፣ ከማጉደፍ ( McCarthyism) ጋር ያያይዙታል። ሆኖም ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ፖለቲካን ከሁሉም ማለትም ከሰብዓዊነት፣ ከፍትሐዊነት፣ ከእኩልነት፣ ከግልፅነት፣ ከተጠያቂነት፣ ከመብት፣ ከአብሮነት፣ ከእርቅ፣ ከሰላም፣ ከመነጋገር፣ ከመቀባበል፣ ወዘተ . አስበልጦ የመመልከት መጥፎ አባዜን መሞገት ነው፡፡
ፅንሰ ሀሳቡ ስራ ላይ ከዋለ ከ80 ዓመታት በኋላም ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ዛሬም አወዛጋቢ፣ አነጋጋሪ ነው። በተለይ የአሜሪካው የቀድሞ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቲዊተርም ሆነ በመደበኛ ሚዲያዎች መግለጫ ከመስጠታቸው በፊት ማንን እንደሚያስቀይም ? የማንን መብት እንደሚጋፋ ? የንግግራቸው፣ የቲውታቸው ትርጉሙ፣ አንድምታው ምን ሊሆን እንደሚችል አስቀድመው ስለማያመዛዝኑ ከፖለቲካዊ ትክክለኝነት አንጻር በተደጋጋሚ ነጥብ ሲጥሉ ይስተዋላል።
ቲዊት ባደረጉ ለጋዜጠኞች መልስ በሰጡ ቁጥር ፊደላቸው፣ አፋቸው ወለም እያለው ምህረት የማያውቀው ሚዲያም እግር በእግር እየተከተለ ሲያብጠለጥላቸው እሳቸውም አፋቸውን ጣታቸውን መሰብሰብ ቢቸግራቸው እውነቱን መዘርገፍ እንጂ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ጉዳዬ አይደለም ማለት ጀመሩ። በእርግጥ ጠንካራ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት ማለትም ሚዲያ፣ ሕግ አውጭና ተርጓሚ፣ ሲቪል ማህበራት፣ ወዘተ . ባለበት አገር የፕሬዚዳንቱም ሆነ የፖለቲከኞች፣ የጋዜጠኞች፣ የተሟጋቾች፣ የሀይማኖት መሪዎች፣ ወዘተ . የአፍ ወለምታ ሆነ ፖለቲካዊ ኢትክክለኝነት ሳይውል ሳያድር በቅቤ ስለሚታሽ ስለሚታረም ያስተዛዝብ ይሆናል እንጂ ያን ያህል ዘላቂ ጉዳት አያደርስም።
ፕሬዚዳንት ትራምፕ ስልጣን ላይ እያሉ አስተዳደራቸው ከሳኡዲ አረቢያ ጎን የሚቆመው” ለምናደርግላት ወታደራዊ እገዛ እጅ በእጅ በጥሬው ስለምትከፍለን ነው። “ በማለት የሳቱት ፖለቲካዊ ትክክለኝነት የአሜሪካ ወታደሮች ለግዳጅ የሚሰማሩት የአገራቸውን ደህንነት፣ ጥቅምና እሴት ለማስከበር እንጂ በቅጥረኛ ነፍሰ ገዳይነት mercenaries አይደለም በሚል ከግራም ከቀኝም አቧራ ማስነሳቱ አይዘነጋም ።
ፕሬዚዳንቱ በዚው ሰሞን ትውልደ ሶማሊያዊ ሴት የምክር ቤት አባልንና ሌሎችን ሶስት ባልጀሮቿን “ የምንሰራው ነገር ካልተዋጠላቸው ወደ አገራቸው መመለስ ይችላሉ። …” ከዚያ በፊት ደግሞ ሴቶችን፣ ቀደምት አሜሪካውያንን፣ አካል ጉዳተኞችን፣ አፍሪካውያንና ሜክሲኮአውያን በተመለከተ አይደለም ከአሜሪካ ፕሬዚዳንት ትላንት ከተወለደ ብላቴና የማይጠበቅ ነውረኛ ነገር በመናገራቸው ማወዛገቡ ይታወሳል። በአገራችንም በየደረጃው ያሉ የብልጽግና አመራሮች፣ ተቃዋሚዎች፣ አክቲቪስቶች፣ ዩቲውበሮችና ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች ደረጃው ይለያይ እንጂ እስከዛሬ በፖለቲካዊ ኢትክክለኝነት አሳራችንን እያበዙት ነው።
በሽግግር ወይም በመሰራት ላይ ላለች እንዲሁም አንድነቷ በቋፍ ላይ ለሚገኝ አገር ግን ፖለቲካዊ ትክክለኝነት የልብ ትረታዋ ነው። እንደ’ ጥላ ወጊ ‘ stroke በድንገት ሊጥላት፣ ሽባ አድርጎ አሳስሮ የአልጋ ቁራኛ ሊያደርጋት ይችላል። ለውጡን ሊቀለብሰው ከፍ ሲልም ወደለየለት ብጥብጥ ሊዘፍቀን ይችላል። ለመሆኑ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ምንድን ነው ? መሪዎች፣ ፖለቲከኞች፣ ተሟጋቾች፣ ጋዜጠኞች፣ ልሒቃን፣ መምህራን፣ የሀይማኖት መሪዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ አባ እማ ወራዎች፣ በአጠቃላይ ሰዎች አንድን ቡድንም ሆነ የሕብረተሰብ ክፍል የሚያስከፋ፣ የሚያስቆጣ ንግግርም ሆነ ሌላ ያልተገባ ድርገት መፈፀም እንደሌለባቸው የሚያሳስብ ፅንሰ ሀሳብ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት ይባላል።
አገራችንም በፖለቲካዊ ኢትክክለኝነት የምትንጠራወዝ፣ የምትላጋ፣ የምታተኩር (Obssesed) ናት ማለት ይቻላል። በተለይ ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ስድ ከተለቀቀው ማህበራዊ ሚዲያ ጋር ተዳምሮ፤ በአዳራሽ፣ በአደባባይ፣ በመደበኛ ሚዲያ፣ በማህበራዊ ሚዲያ፣ ወዘተ . በለውጥ ኃይሉ፣ በተፎካካሪው፣ በተሟጋቹ፣ በልሒቁ፣ በአገር ሽማግሌው፣ በኃይማኖት መሪው፣ በታዋቂ ሰው፣ ወዘተ . በተደረጉ ንግግሮች፣ በተሰጡ አስተያየቶች፣ መልሶች፣ በተላለፉ ንግግሮች፣ በመግለጫዎች፣ ወዘተ . የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ልምሻዎች ተከስተው ያስከፉት ብሔር፣ ኃይማኖት፣ ማንነት፣ አይዶሎጂ፣ “ መስመር “፣ ወዘተ . ነበር። ይሁንና የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ሆን ተብሎም በአፍ ወለምታም ሊጣስ ይችላል።
የቀድሞው የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ “ አክሱም ‘ ለእንቶኔ ‘ ምኑ ነው ? “ እንዲሁም የተወለዱበትን ሕዝብ ስም ጠርተው “… ከዚህ ወርቅ ሕዝብ መፈጠሬ ያኮራኛል። …” በማለታቸው ከፖለቲካዊ ትክክለኝነት አንጻር ትልቅ ነጥብ አስጥሏቸው ነበር። ፓርቲን ከሕዝብ ጋር ማመሳሰል፣ ገዥ መደብን ከአንድ ብሔር ጋር ማያያዝ፣ አንድን ዕምነት ከአንድ ብሔር ጋር ማቆራኘት፣ ሰንደቅ አላማን ከአንድ ቤተ ክርስቲያንና ጎሳ ጋር ማመሳሰል አንድ ማድረግ እንደ ዜጋም እንደ አገርም ሁል ጊዜ የምንስታቸው የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ኢላማዎች ናቸው፡፡
ይሁንና የአገራችንም ሆነ የውጭ አንዳንድ ልሒቃን ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን የንግግርና የሀሳብ ነፃነትን እንደሚገድብ ያወሳሉ። የሜሪ ላንድ ዩኒቨርሲቲው ዳን ሞለር ፖለቲካዊ ትክክለኝነት የንግግር ነፃነት የመገደብ ጉዳይ ሳይሆን ነፃነቱ የሌላውን መብት፣ ባህል፣ ታሪክ፣ ማንነት፣ ወዘተ . በማይነካ፣ በማያንቋሽሽና በማይሸረሽር መንገድ የመጠቀም አግባብ ነው ሲሉ ይሞግታሉ። አላማውም፦
1ኛ . ተጋላጭ፣ ተገላይ እና በታሪክ አጋጣሚ ተጠቂ የሆኑ የሕብረተረብ ክፍሎችን መከላከል፡፡
2ኛ . ሕዝቡ የሚወያይባቸው፣ የሚነጋገርባቸው ርዕሰ ጉዳዮችን በማረቅ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ተጠቂ እንዳይሆኑ መስራት፡፡
3ኛ . በዜጎች መካከል ቁጣን፣ ግጭትን፣ ጥላቻን የሚቀሰቅሱ ንግግሮችን መከላከል መሆኑን ያሳያሉ ፡፡
ይሁን እንጂ ዳን ቀለል ባለ ምሳሌ ሲያስረዱ አንድን የሕብረተሰብ ክፍል ዝቅ የሚያደርግ የታሪክ የመማሪያ መፅሐፍት እንዲታረም መጠየቅ የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ጉዳይ ተደርጎ የሚወሰድ አይደለም፡፡
እንደ ታዋቂው የኢኮኖሚክስ ባለሙያ ግሌን ሎሪ ያሉም ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን ሀሳብን የመግለፅና የንግግር ነፃነትን እንደሚገድብ አድርገው የሚወስዱ አሉ። ሎሪ ፖለቲካዊ ትክክለኝነት የሚቃወሙበት ሌላው መከራከሪያ ራስን መመርመር ማቀብ (self cencorship) ያስከትላል በሚል ነው። የጀርመኑ ፖለቲከኛ ፊሊፕ ጄኒንገር ስለናዚ ዘመን ጀርመናውያን በማውራቱ ብቻ የናዚ ደጋፊ ወይም ፀረ -ፂወናዊ እንዳልሆነ እየታወቀ በመናገሩ ብቻ ከፖለቲካ ህይወቱ እንዲገለል ተደርጓል፡፡
የውሾን ነገር ያነሳ ውሾ በሚል መሆኑ ነው። የዋሽንግተን ከንቲባ ሹመኛም በአንድ ወቅት ጓደኞችን “ niggardly “ (ቆንቋኖች) ብሎ መሳደቡ ቁጣ በመቀስቀሱ ከኃላፊነቱ በገዛ ፈቃዱ ለመልቀቅ ተገዷል። ከዚህ ከዚህ አንፃር ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን ስንመዝነው ለምዕራባውያን ለቅንጦት የቀረበ ሊመስል ይችላል እንደኛ በለውጥ በሽግግር ላይ ላለ አገር ግን የህልውና እንዲሁም የሞት ሽረት ጉዳይ ነው ማለት ይቻላል፡፡
እንደ መውጫ
በአገራችን ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን በማበረታታት ረገድ ገዥው ፓርቲ ብልጽግና የአንበሳውን ድርሻ እና ቀድሞ ተነሳሽነቱን በመውሰድ አርዓያ ሊሆን ይገባል። በሕገ ደንቡ ላይ በማያሻማና ግልፅ በሆነ ቋንቋ ስለፖለቲካዊ ትክክለኝነት አስፈላጊነት ሊደነግግ በቀጣይም ለአባላቱና ለደጋፊዎችም የግንዛቤ ማስጨበጫ ተከታታይ መድረኮችን ሊያዘጋጅ ይገባል፡፡
በከፍተኛ ትምህርትም ሆነ በሌሎች ተቋማት የሚገኙ ልሒቃን በፖለቲካዊ ትክክለኝነትን ምንነትና አስፈላጊነት ላይ ሀሳብ በመለዋወጥና ችግሩን ከእነ መፍትሔው በማመላከት የዜግነት ግዴታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል። ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችም የድርሻቸውን ከመወጣት ባሻገር የፖለቲካዊ ትክክለኝነት ጥያቄን የሚያስነሱ ጉዳዮችን በመለየት መሪዎቻቸው በመግለጫዎቻቸው በንግግሮቻቸው በቅስቀሳቸው ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን ታሳቢ እንዲያደርጉ አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸውም ግንዛቤ እንዲኖራቸው ማድረግ ይገባል፡፡
ሚዲያው በአርትኦት ፖሊሲው ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን በማካተት ኃላፊነቱን ለመወጣት አበክሮ መስራት ይጠበቅበታል። እንደ ዜጋ ደግሞ ሁላችንም የምንፅፈው፣ የምንናገረው፣ የምንስለው፣ የምናዜመው፣ የምንቀርፀው፣ ወዘተ . የሌላውን ወገን ታሪክ፣ ባህል፣ እሴት፣ ሀይማኖት፣ ማንነት፣ ወዘተ . የመያናንቅ፣ የማያንኳስስ እንዲሁም በሌላው ቁስል ላይ እንጨት የማይሰድ መሆኑን ማረጋገጥ ይገባናል፡፡
የሰለጠነ ፖለቲካዊ አስተሳሰብ እስክንጨብጥ፤ የዴሞክራሲያዊ ተቋማት በአግባቡ እስኪጎለብቱ፤ በመንግስት አካላት ማለትም በሕግ አውጭው፣ ተርጓሚውና አስፈፃሚው መካከል ያለው ግንኙነት ሚዛናው እስኪሆን ፖለቲካዊ ትክክለኝነትን የሙጥኝ ብሎ መያዝ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም። ስንከተለው የነበረ አገዛዝ ያመጣብን መለያየት መጠራጠር ሳያንስ በፖለቲካዊ ኢ-ትክክለኝነት አገር ልትታመስ ሕዝብም ሊደናገር አይገባም፡፡
ፖለቲካዊ ትክክለኝነት አሁኑኑ ! ! !
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን) fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ታህሳስ 20 ቀን 2015 ዓም