ባለፉት ሁለት አመታት በሀሰተኛ ፣ ሆን ተብሎ በተዛባና በተጣመመ መረጃ እና በሴራ ፓለቲካ የአገራችን ገጽታና ስም ክፉኛ ጠልሽቷል ፤ ጠፍቷል ። በዘር ማጥፋት ፣ በአስገድዶ መድፈር ፣ በሰብዓዊ ፍጡር ላይ በሚፈጠር ወንጀል ፣ በጦር ወንጀል ፣ ሰብዓዊ ዕርዳታን እንደ ጦር መሳሪያ በመጠቀም ፤ አንድን ማህበረሰብ በመክበብና በማገት ፣ ወዘተረፈ በሚሉ የፈጠራ ክሶች ታሪካዊ ጠላቶቻችን ከተላላኪዎቻቸው ፣ ከአለም ዓቀፍ ሚዲያውና ተቋማት ጋር በማበር ፣ በመቀናጀትና በመናበብ አገራችንን ምድራዊ ሲኦል አድርገዋታል ።
ለተከታታይ ሁለት አመታት በአለም ዓቀፍ ብዙኃን መገናኛዎች የሀሰተኛ ዜና ማሟሻ አድርገዋታል ። እውነትንና ፍትሕን ይዛ ሆን ተብሎ ሰሚና ተመልካች እንድታጣና እንድትገለል ተደርጓል ። ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይም በሀሰትና በፈጠራ ወሬ በአለም ዓቀፍ መገናኛ ብዙኃን በሰላም የኖቤል አሸናፊው ጠቅላይ ሚንስትር ይሄን አደረገ ፣ ያን ፈጸመ እየተባለ ተሽሟጠዋል ፤ ስማቸው ጎድፏል ። የአረንጓዴ አሻራ እንግዲህ ከዚህ ሁሉ ነው ከፍ ብሎ ገዝፎ የታየው ። ግሎባል ሆፕ ኮአሊሽንም በዚህ ሰዓት ለጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ እውቅና መስጠትና ሽልማት ማበርከት ሊያመጣ የሚችለውን ውርጅብኝ ንቆ በድፍረት ስለ አረንጓዴ አሻራ ለጠቅላይ ሚንስትሩ የአፍሪካ የላቀ አመራር ሽልማት የሰጠው ከሀሰተኛ መረጃውና ስም ማጠልሸቱ የገዘፈ ታላቅ ተግባር ስለሆነ ነው ።
ለአፍሪካ – አሜሪካ የመሪዎች 2ኛ ጉባኤ ዋሽንግተን ለተገኙት ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ ፤ ግሎባል ሆፕ ኮአሊሽን የተሰኘው ተቋም በዋሽንግተን ዲሲ ባዘጋጀው ልዩ ዝግጅት ላይ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄን አስመልክቶ ላሳዩት አመራር ‘የአፍሪካ የላቀ አመራር’ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።ኢትዮጵያ በ2011 ዓ.ም. የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብርን ስታስጀምር፣ በአራት ዓመታት ውስጥ 20 ቢልዮን ችግኞችን ለመትከል ማቀዷ የሚታወስ ነው።
ኢትዮጵያ ከታቀደው ግብ አልፋ በመላ አገሪቱ 25 ቢልዮን ችግኞች በመትከል የአራት ዓመት ዕቅዷን አሳክታለች ይላል የ”አዲስ ዘመን”ዘገባ ። በዚህም የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እና ለደን መልሶ ልማት ላደረገችው አስተዋጽዖ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና አግኝታለች ። ለመሆኑ ጠቅላይ ሚንስትሩ እንደ አመራር ፣ ኢትዮጵያ እንደ አገርና ኢትዮጵያውያን እንደ ሕዝብ በአለም አደባባይ ሞገስና ክብር ያገኙት ምን ሰርተው ነው የሚለውን ለመገንዘብ 25 ቢሊየን ችግኝ መትከል ከአኅዝ በላይ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል ።
በመንግስታቱ ድርጅት የአየር ንብረት ፕሮግራም (ዩኤንኢፒ)አገራችን ኢትዮጵያን ለአየር ንብረት ለውጥ ክፉኛ ከተጋለጡ 10 አገራት አንዷ መሆኗን ይገልጣል ። መልሶ ኢትዮጵያውያን ግን የአየር ንብረት ለውጥን ከማያባብሱ ዜጎች ተርታ ይሰለፋሉ ይለናል ። ኢትዮጵያውያን በአማካኝ ወደ ከባቢ አየር የሚለቁት ግሪንሀውስ ጋዝ 1.3 ሜትሪክ ቶን ወይም 1300 ኪግ ሲሆን በአንጻሩ የአሜሪካውያን 20ሺህ ኪግ ፤ ኩየታውያን ደግሞ 60 ሺህ ኪግ ግሪን ሀውስ ጋዝ ወደ ከባቢ አየር ነው ። የቻይናና የሕንድማ አይነሳ ።
ይህ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ለከባቢ አየር ሙቀት መጨመር እዚህ ግባ የሚባል ድርሻ የሌላቸው አገራት የበለጸጉ አገራት ከኢንዱስትሪ አብዮት ጀምሮ ወደ ከባቢ አየር በለቀቁት ከፍተኛ መጠን ያለው ግሪንሀውስ ጋዝ በተፈጠረ የአየር ንብረት ለውጥና የከባቢ አየር ሙቀት የተነሳ ለተደጋጋሚ የዝናብ ዕጥረት ፣ ለድርቅና ረሃብ ተዳርገዋል ።
አገራችን ከ1966 ዓም ጀምሮ በየአስር አመቱ ይጎበኛት የነበረው ድርቅ ከቅርብ አመታት ወዲህ በየአመቱ የሚከሰት ሁኗል ። አምና ፣ ካች አምናና ዘንድሮ እንኳ በቦረና ፣ በሱማሌና በደቡብ ክልል የተከሰተው ድርቅ በእንስሳትና በአርብቶ አደሩ ላይ ያስከተለውን ከፍተኛ ጉዳት አይተናል ። በመንግስት ርብርብ ድርቁ በሰዎች ላይ የከፋ ጉዳት ባያስከትልም የህልውናቸው መሠረት የሆኑ እንስሳቱ ላይ ግን የከፋ ጉዳት አድርሷል ። መጠኑ ቢለያይም እንደ 1966ቱ ፣ 77ቱና 87 ሰዎች በረሃብ እንደ ቅጠል አልረገፉም ።
በአናቱ የሕዝብ ቁጥር ዕድገቱን የሚመጥን ምርት ባለመመረቱ ፤ በፍላጎትና በአቅርቦት መካከል ያለው ሰፊ ክፍተት ባለመጥበቡ ፤ በሰሜኑ የአገራችን ክፍል ህወሓት በከፈተው ጦርነትና እዚህም እዚያም በተከሰቱ ቀውሶች ፤ በኮቪድ 19ና ራሽያ ዩክሬንን በመውረሯ በተፈጠረ የዋጋ ግሽበቱና የኑሮ ውድነቱ የተነሳ በከተሞች ሳይቀር ድምጽ አልባ ረሃብ ተከስቷል ። ኑሮው አልቀመስ ብሏል ።
አገራችን ዛሬ ለምትገኝበት ውስብስብ ችግር በርካታ ምክንያቶችን መደርደር ቢቻልም ዋነኛዎቹ ግን ሁለት ናቸው ። እነሱም አበክረን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት አለመገንባታችን ፤ የተፈጥሮ ሃብታችንና የሰው ኃይላችንን በአግባቡ አቀናጅተንና አልምተን አለመጠቀማችን ናቸው ። ሰፊ ለም መሬት ፣ አመቱን ሙሉ የሚፈሱ ወንዞች ፣ የከርሰ ምድር ውሃ ፣ ዝናብና ወደ 123 ሚሊየን ከሚገመተው ሕዝብ 70 በመቶው ወጣት ስለሆነ ከምግብ ዋስትና አልፈን የተትረፈረፈ ምርት አምርተን ኢንድስትሪውን ፣ የአገልግሎት ዘርፉንና የውጭ ንግዱን ይዘን መነሳት እየቻልን ዛሬም እርዳታን የምንቀላውጥ መሆናችን አንገት ያስደፋል ።
ከለውጡ ወዲህ ግን የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታውን ከግብርና ልማቱ ፣ ከአካባቢ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ጋር መሳ ለመሳ በማስኬድ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያልተጠበቀ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ ችለናል ። በ2025 ዓም ደግሞ የግሪንሀውስ ጋዝ ልቀቷን ወደ ዜሮ ለማውረድ ግብ ተጥሎ እየተሰራ ነው ። ባለፉት አራት አመታት 25 ቢሊየን ችግኞችን ተክላለች ። የኤሌክትሪክ ፍላጎቷንም ከታዳሽ ኃይል ማለትም ከግድብና ከንፋስ እያገኘች ሲሆን በቀጣይም ለማመንጨትም እየሰራች ትገኛለች ።
አገራችን በታሪኳ ከፈጸመቻቸው እየፈጸመ ቻቸው ካሉ ግዙፋን ፕሮጀክቶች ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጨምሮ አንድ ላይ ቢደመሩ የ” አረንጓዴ አሻራ “ን ያህል ክብደት አልሰጣቸውም ። የህዳሴውም ሆነ የሌሎች ታላላቅ ግድቦች ህልውና እንዲሁ 80 በመቶ አገሬው ኑሮ የተመሰረተበት ግብርና እጣ ፈንታ የሚወሰነው ዛሬ በትጋት በምንከውነው የአካባቢ ወይም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ነውና።
በቀደሙት ሶስት አመታት ከ18 ቢሊዮን በላይ አገር በቀል ችግኞችን ለዛውም ከሞላ ጎደል ስነ ምህዳርን ታሳቢ ያደረጉ በመላው የአገሪቱ ክፍሎች መትከል ተችሏል። ከተተከሉ ችግኞች መካከል እንደ አቡካዶ፣ ማንጎ፣ አፕል፣ ፓፓየ፣ ሙዝ እንዲሁም ቡና የመሳሰሉት ይገኙበታል። በአራቱም ዙር ከ90 ሚሊየን በላይ ሕዝብ በችግኝ ተከላው ተሳትፏል።
ከፍ ብዬ ለመግለጽ እንደሞከርሁት ችግኝ መትከል የአየር ንብረት ለውጥን ፣ የአለም ሙቀት መጨመርን ወይም የአካባቢ ጥበቃ ችግሮቻችን ለመፍታት የማይተካ ሚና አለው ። ድህነትን ፣ የምግብ ዋስትና ጉድለትን ፣ የምርታማነት ተግዳሮትን ፣ ድርቅን ፣ ረሃብን ፣ የዝናብ መቆራረጥንና መቅረት ፣ የውሃ እጥረትን ፣ የኑሮ ውድነትን ፣ በፈጣን የሕዝብ ቁጥር እድገትና በምርት አቅርቦት መካከል ያለውን ክፍተት ፣ ስራ አጥነት ፣ ከገጠር ወደ ከተማ የሚደረግ ፍልሰትን ፣ የጸጥታና የደህንነት ችግርን ፣ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን ሽግግር በማሳለጥ እና ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማለም መስፈንጠሪያ በመሆን ያገለግላል ። ለዚህ ነው ችግኝ ተከላን የችግሮቻችን ሁሉ መፍቻ ዋና ቁልፍ /ማስተር ኪይ/ ነውየምለው ።
በየአመቱ በአገራችን ከ92ሽህ ሔክታር መሬት በላይ ደን ይመነጠራል ፤ ይጨፈጨፋል ። በዚህ የተነሳ የደን ሽፋናችን ከ50 አመታት በፊት ከ35 በመቶ ከነበረበት ደረጃ ወደ ሶስት በመቶ አሽቆልቁሎ ነበር ። ለዝናብ እጥረት ፣ ለድርቅና ለከባቢ አየር ሙቀት ተዳረግን ። በየአመቱ ምርታችን ከ10 በመቶ በላይ መቀነስ ጀመረ ። በየአመቱ ከ35 እስከ 40 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይቀንሳል። ሆኖም ባለፉት አራት አመታትም ሆነ ከዚያ በፊት በተከናወኑ የችግኝ ተከላና የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የደን ሸፋኑን ወደ 17 በመቶ ማገገሙ ይበል የሚያሰኝ ነው።
የበጋ ስንዴ ፣ የኩታ ገጠም ግብርናን ፣ በተወሰነ ደረጃ ስነ ምህዳርን ታሳቢ ያደረገ የቴክኖሎጂና የሜካናይዜሽን እገዛ ፣ የከርሰና የገጸ ውሃን አሟጦ የመጠቀም ፣ ፍራፍሬና አትክልት ላይ ለመስራት ፣ በተለይ ከአለፈው አመት ጀምሮ የከተማ ግብርና ትኩረት ማግኘቱ ፤ ሰሞኑን ደግሞ የሌማት ትሩፋት መጀመሩ ፤ በአርብቶ አደሩ የሚገኙ ጦም ያደሩ ሰፋፊ መሬቶችን በመስኖ ለማልማት አበረታች ጥረትና ርብርብ መደረጉ እና ከውጭ የሚገባውን ስንዴ ለማስቀረት ግብ መጣሉ የአተያይ ለውጥ በማምጣቱ ተስፋ ያስቆረጠን ግን ደግሞ ብቸኛ ሊባል በሚችለው ግብርና ከምግብ ዋስትና ባሻገር ተስፋችንን እንድናድስ አድርጎናል። ለዚህ ነው ተስፋ ሰጭ ጅምር እውቅና መስጠት የሚያስፈልገው።
ችግሮቻችንን ሁሉ ፈታተን ፣ በታትነንና አገላብጠን ብንመረምራቸው አብዛኛዎቹ ከአንድ ቅርጫት የሚገኙ ናቸው ። የተፈጥሮ ሀብታችንን በአግባቡ ካለመንከባከብ ፣ ካለመጠበቅና ካለማልማት ቅርጫት የአለም ሙቀት መጨመርን ተከትሎ በመጣ የአየር ንብረት ለውጥ የተነሳ የተፈጥሮ ሀብታችን እየተጎሳቆለ በመምጣቱ ማለትም መሬታችን የተራቆተ ፣ ዝናባችን የአጠረና የተቆራረጠ በመሆኑ የከርሰና የገጸ ምድር ውሃችን በመመናመኑ ግብርናው ውጤታማ ሊሆን አልቻለም ።
በዚህ የተነሳ በግብርና ላይ የተመሰረተው የዜጋው ህይወት ፤ የአገሪቱ ልማት ችግር ላይ ወድቋል ። ይህ የሀብት ውስንነትን ፈጥሯል ። በዚህ የተነሳ ማህበራዊ ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮች ከአመት አመት እየተባባሱ መጡ ። እነዚህን ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ደግሞ የተፈጥሮ ሀብታችን እንዲያገግም ሌት ተቀን መሰራት አለበት። መሬት ማገገም ፣ ውሃ መያዝ አለባት ።
ይህ ደግሞ እውን ሊሆን የሚችለው ችግኝ በመትከልና የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በስፋት በማከናወን ነው።“ አረንጓዴ አሻራ “ የበሽታውን ምልክት ከማከም ይልቅ መነሻውን በማያዳግም ሁኔታ የመፈወስ አቅም እንዳለው በማመን ነው፤” አረንጓዴ አሻራ ! “ የእንቆቅልሾቻችን ሁሉ መፍቻ ዋና ቁልፍ (ማስተር ኪይ) የምለው ።
ለዚህም ነው 25 ቢሊየን ችግኞችን መትከል ከቁጥርና ከአኃዝ በላይ በየአመቱ የሚከሰተውን ድርቅ ፣ የበርሃማነት መስፋፋት ፣ የአፈር መከላት ፣ የዝናብ ዕጥረትና መቆራረጥ ፣ የገጸና የከርሰ ምድር ውሃ መቀነስን በመከላከል ፤ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ከተመጽዋችነት የመላቀቅ የማሪያም መንገዳችን ፤ ሉዓላዊነታችን ሙሉኡ ማድረጊያችን ፤ የአገሪቱ ሁለንተናዊ ብልጽግና ማርሽ መቀየሪያ ፤ አስተማማኝ ሰላም ማስፈኛችን ፤ እውነተኛ አንድነትና እርቅ ማረጋገጫችን ፤ ወዘተረፈ ስለሆነ አረንጓዴ አሻራ ከአኃዝ በላይ ከመሆኑ ባሻገር ጠቅላይ ሚንስትሩ እንዳሉትም እንደ አገርና ሕዝብ ብቸኛ መዳኛችን ነው ።
አረንጓዴ አሻራ የሕዳሴያችን ዋልታና ማገር ነው !
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሐሙስ ታኅሣሥ 13 ቀን 2015 ዓ.ም