ቀደም ባሉት ሣምንታትና ቀናት ውስጥ የመላውን ዓለም መገናኛ ብዙኃን አየርና ገጾች ተቆጣጥሮ የሰነበተው በአሜሪካ የፖለቲካ መዘወሪያ ማዕከል በሆነው በዋሽንግተን ዲሲ ከታህሣሥ አራት ቀን ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት የተደረገው “የአሜሪካ አፍሪካ የመሪዎች ጉባዔ” ነበር። ጉባዔው በዋነኛነት እንዲካሄድ አዘጋጇን አሜሪካንን ግድ ያላት ወይንም የገፋፋት ሰበብ ምክንያት ምን እንደነበር በሀገሪቱ የብሔራዊ ደህንነት አማካሪ ጋዜጣዊ መግለጫ በኩል የተገጸው እንዲህ ተብሎ ነበር።
“አሜሪካ ይህንን ጉባዔ ያዘጋጀችው የአፍሪካ አህጉር የጂኦ ፖለቲካ ሚና ከፍ ያለ መሆኑን ስለምታምን ብቻም ሳይሆን ዕውቅና ለመስጠት በማሰብም ጭምር ነው። የዓለማችንን ሁለንተናዊ መስተጋብር ለመቅረጽ አህጉረ አሜሪካ ትልቅ አቅም እንዳላት ሀገሬ አሜሪካ በሚገባ ትረዳለች። ስለዚህም ከአፍሪካ ጋር ለመሥራት ግድ የሆነው አስፈላጊያችን ብቻም ሳይሆን ግድ ስለሆነም ነው።”
በጉባዔው ላይ የተጋበዙት አርባ ዘጠኝ ያህል የአፍሪካ አህጉር ርዕሳነ ብሔሮችና የአፍሪካ ኅብረትን የወከሉ የልዑካን ቡድን አባላት ይህንን መሰሉን ምስክርነት ሲሰሙ ልባቸው ምን ያህል በደስታ እንደሚግል ለመገመት አይከብድም። “አያት ቅድመ አያቶቻችሁን በባርነት አፍልሰን አሜሪካን ዛሬ ለደረሰችበት ደረጃ እንድትበቃ ስላደረጉም ምሥጋና እናቀርባለን” የሚለው የፕሬዚዳንት ጆ. ባይደን ንግግርም ትርጉሙ ላቅ ያለ ብቻ ሳይሆን ንስሃ እንደማውረድም ተቆጥሯል።
ከጥናታዊ የግሪክ አማልክት መካከል አንዱ የነበረውና ዓላማችንን ለዘለዓለሙ በጫንቃው ላይ እንዲሸከም በብጤዎቹ አማልክት ግዞተኛ እንዲሆን ተፈርዶበታል ተብሎ እንደሚታመነው የተረት ተረቱ ዋና ገጸ ባህርይ እንደ አትላስ፤ ቀደም ብሎም ሆነ በጉባዔው መክፈቻ ላይ የተላለፈው መልዕክት የየግላቸውን ሀገር “በረከተ መርገም” በጀርባቸው ላይ አዝለው ለሚንገዳገዱት አፍሪካዊያኑ መሪዎቻችን ቀርቶ ለእኛ ለተራ ተገዢ ዜጎችም ቢሆን ከልብም ይሁን ከአፍ “የታላቅነት ዋነኛው ቁንጮ እኔ ነኝ” ከምትል ሀገር መሪዎች ይህንን መሰል ምሥክርነት መስማት እንደምን እንደሚያፍነከንክ “እኛን ሆኖ ማሰቡ” ብቻ በቂ ይሆናል።
የምሥክርነቶቹ ሁሉ የተስፋ “አዝመራ” በርግጥም በገቢር የሚለወጥ ከሆነና በተለይም “በተባበሩት መንግሥታት የጸጥታው ምክር ቤት ውስጥ አፍሪካ በቋሚ አባልነት እንድትሳተፍ” ግፊት እንደሚያደርጉ በስብሰባው አጋፋሪ በአሜሪካው ፕሬዚዳንት የተሰጠው ማረጋገጫ በርግጡ ተፈጻሚ የሚሆን ከሆነ የአፍሪካ ጌቶቻችን “ዋንጫ ኖር! Cheers!” እያሉ መለኪያቸውን ቢያጋጩ ሀብታችን በግብዣ ባከነ ብለን ላንወቅሳቸው ቃል እንገባለን።
“ከጉባዔው የተገኘው ዝርዝር ፋይዳ ምንድን ነበር? ምንስ ጉዳት ያስከትላል? ወዘተ.” ለሚሉት ጥያቄዎች ምልከታችንን በፈርጅ በፈርጁ እየተነተንን ለማጋራት ከጽሑፋችን ቢጋር እንዳያስወጣን በመስጋት እንጂ የጋባዧን ሀገር ድብቅ ፍላጎት፣ ግልጽ መሻትና የመሪዎቻችንን የልብ ትርታ ሳይቀር እየፈተሽን ብዙ ብዙ በተጨዋወትን ነበር።
“ኢትዮጵያስ ብትሆን ከጉባዔው ምን አተረፈች? ምንስ ተማረች?” ለሚለው እኛን ጠቀስ ስጋትና ጥያቄዎችም በዚህ ጽሑፍ ምላሽ አከል ሃሳቦችን አንሰነዝርም። ምክንያቱም የሰሞንኛውን የጉባዔ ጠበል ተቃምሰው የተመለሱት የልዑካን ቡድኑ አባላት በተደጋጋሚ “ከአግዋ እስከ ማእቀብ ማላላት፣ ከእርዳታ እስከ ሰፋፊ የብድር ተስፋ፣ ከፊት መጥቆር እስከ ፈገግታ” ስለተገኘው ፖለቲካዊ፣ ዲፕሎማሲያዊና ኢኮኖሚያዊ ድርብ ድርብርብ ድል ተገቢውን ማብራሪያ ሲሰጡ ስለሰነበቱ “እንኳን ቀናችሁ፤ እንኳን ቀናን!” በማለት የተገኙት ትሩፋቶች ደጃፋችን ደርሰው እስኪታዩ ድረስ በትዕግሥት መጠበቁ ይበጃል። ከወዲሁ እየታዩ ያሉ አንዳንድ ምልክቶች አበረታች ስለመሆናቸውም አንክድም።
“እልህ ምላጫ ያስውጣል”፡- ለዲፕሎማሲ አይሠራም፤
ቀለም ዘልቆ ገብቷቸዋል የሚባሉት የሀገሬ ልጆችም ሆኑ (ልጆች ማለቴን ልብ ይሏል) የዕለት እንጀራቸውን ለማሸነፍ ሲጥሩና ሲግሩ የሚውሉት እኛን መሰል ሠርቶ በሌ ተራ ዜጎች የአሜሪካንንና የኢትዮጵያን ሰሞንኛ ቅርርብና መደናነቅ ሲሰሙ ምቾት ነስቶ እንደሚቆረቁራቸው ሲተቹና ሲቃወሙ ማድመጣችንንና ማንበባችንን አንዘነጋም። አንዳንድ “ወኔ ሙቅ” ምሁራንማ ከነጭራሹ “አሜሪካን መጣች ቀረች ምን ሊጎድልብን? ምንስ ሊሞላልን?” እያሉ በየሚዲያው ሲፎክሩ “ወይ እብደት!” እያልን በትዝብት ፈገግታ እንደሞሸለቅናቸው አላወቁ ከሆኑ ይወቁት። “ቻይና፣ ራሽያና ህንድን የመሳሰሉ ሀገራት ይኑሩልን እንጂ አሜሪካ መጣች ቀረች ኬሬዳሽ!” በማለትም “ምክረ ፍላጎታቸውን” አስረግጠው ለመንግሥት ሲገልጹ እያጉተመተምንም ቢሆን አድምጠናቸዋል።
በመሠረቱ “እልህ ምላጭ እንደሚያስውጥ” መዳፈር ወይንም “ለእልኸኛ ልጅ ቁርሱ ለእራት እንደሚቀመጥለት” ያለማወቅ ግትርነት እንጂ ትርፉ ምንም ነው። “እልኸኛ መዥገር ከቆዳ ጋር ተጣብቆ የሚሞተውም” ከአፈርኩ አይመልሰኝ በሚመስል የልብ ድንዳኔ በመጽናቱ ሳይሆን አይቀርም። ከመዥገር ጋር በቋንቋ መግባባት ስለማይቻል “ይሆን እንደሆን” በሚል ግምት ብሂሉን ለማስታወስ መገደዳችን አይዘንጋ።
እውነታው እንዲህ ነው፡- “በፖለቲካና በዲፕሎማሲ የዘላለም ጠላት ወይንም የዕድሜ ልክ ወዳጅ” የሚባል በደም የፀና ቃል ኪዳን የለም። ለወደፊቱም ይኖራል ተብሎ የሚታሰብ አይደለም። ትናንት የሰላም ርግብን እድኜ ካልፈጀሁ እያለ ሲያቅራራ የነበረ አንድ መንግሥት፤ የዲፕሎማሲውና የፖለቲካው አካሄድ እንደሚጎዳውና አላዋጣ እንደሚለው ወይንም አልፎ አልፎ ሰብዓዊ ኅሊናው እየሸነቆጠ እንቅልፍ ሲነሳው ወዲያው መለስ ብሎ “ራሱን ልክ እንደ አበባ ምንጣፍ አንጥፎ ካልተረማመዳችሁብኝ” በማለት የመላዕክትን መሰል ክንፍ አቆጥቁጦ ልናስተውል እንችላለን።
እርግጥ ነው አሜሪካንን መሰል “ጡንቸኞች ነን” ባይ መንግሥታት ሰኞ ዕለት የንጉሥ ሳኦል እብሪት ተጣብቷቸው ያለምንም ምክንያት በንጹሐን ሀገራት ላይ ጦር ሲሰብቁ እንዳልዋሉ፤ በማግሥቱ ማክሰኞ የዳዊትን በገና ካልሰጣችሁንና ሰማያዊ ቅኔ ካልተቀኘን በማለት የኮሚክ ገጸ ባሕርያትን ሚና ተውሰው ቢተውኑ ሊገርመን አይገባም። በዲፕሎማሲ ውሏቸውም መልከ ብዙ ባሕርያቶቻቸውን (Double Face Jacket እንዲሉ) እያለዋወጡ ተውኔት ሊሠሩ ይችላሉ። አንዳንድ የፖለቲካ ሳይንስ በሳሎች እንዲህ መሰሉን የዲፕሎማሲ ግሪንቢጥ “The Joy Luck Club” በሚል ርእስ በሚታወቀው ዝነኛ የኮሚክ ድርሰቶች ይመስሉታል።
ስለዚህም ነው አምና “እርኩስ” ተብሎ የተብጠለጠለ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ውሳኔ ሳይውል ሳያድር እንደ “ቅዱስ” እየተቆጠረ እንዲካ ደምለት የሚፈለገው። በአጭሩ በዲፕሎማሲ መዝገበ ቃላት ውስጥ “ዘላለም” የሚለው ቃል ቤትኛ አይደለም። በዲፕሎማሲ ፖለቲካ አሠራር ውስጥ እልኸኝነት ቦታ የለውም። እልኸኛ ሀገርና መንግሥታት የሚተቹትም “የዱባ ጥጋብ ያለ ስንቅ ያዘምታል” እየተባለ ነው።
መንግሥታት “ረጅም ዘመናት ያስቆጠረ ወዳጅነት አዳብረናል” እያሉ የሚሸነጋገሉት በካሜራ ፊት ሲቆሙና ሲቀመጡ እንጂ በየጓዳቸው ውለው የሚያድሩት እንዴት አድርገን የፖለቲካውንና የዲፕሎማሲውን ልጓም ጨብጠን የፊት አውራሪነቱን ኮርቻ ልንቆናጠጥ እንችላለን እያሉ ነው። ሩቅ ማማተሩ ይቅርብንና ሀገራችን ከአሜሪካ ጋር ያለፈችበትን የቅርቡን ሁኔታና የዛሬውን ሁኔታ መለስ ብለን ብናስተውል ይህ እውነታ ፍንትው ብሎ ሊታየን ይችላል።
በራሷ ታዛ ሥር ብቻ ሳይሆን በተባበሩት መንግሥታት በርካታ ጉባዔዎችም ሳይቀር “ኢትዮጵያ በዚህና በዚያ” ምክንያት ካልተቀጣችና በማዕቀብ ካልተሽመደመደች እንቅልፍ አይወስደኝም እያለች እንዳልፎከረች ሁሉ ሰሞኑን በነበረው ጉባዔ ላይ “ጠብ እርግፍ” እያለች በክብሮትና በአንቱታ የልዑካን ቡድናችንን እንዴት ስታስተናግድ እንደባጀች ዐይተናል፤ ሰምተናል። እንዴት ሊሆን ቻለ? ከተባለ መልሱ “ዲፕሎማሲ ባህርይው ነው” ዋናው መልስ ነው። “የዲፕሎማሲ እልህ ምላጭ ላለማስዋጡም” ጥሩ ማሳያ ይሆናል።
“እንኳንም ከተዛተ፤ ከተወረወረም የሚታደግ አምላክ አለ” በሚል እምነቷ ኢትዮጵያ በጽናቷ እንደበረታች የዲፕሎማሲ የበላይነቱን የተቀዳጀችው በቀላሉ እንዳልሆነ በሚገባ ሊታወስ ይገባል። ተገዳዳሪዎቻችን ሲጮኹና ያዙን ልቀቁን እያሉ ሲፎገሉ ኢትዮጵያ በስንዴ እርሻዋ ላይ ተጠምዳ ነበር። በተንቆጠቆጠው የመንግሥታቱ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ውስጥ በጋለ ትንፋሽ “ማዕቀብ ለመጣል ሲሟገቱብን” ሀገሬ የታላቁ ህዳሴ ግድቧን ሌት ተቀን ሳትል ግንባታውን ታጧጡፍ ነበር።
በአንድ እጇ የሉዓላዊ ክብሯን መመከቻ የጦር መሣሪያ፤ በሌላው እጇ የልማት ትጥቋን አጥብቃ ጠላቶቿን ስትፋለምና ልማቷን ስታጧጡፍ እያዩ እንዳልተዘባበቱባት ሁሉ ዛሬ ደርሰው ታላቅነቷን፣ ቃሏን ጠባቂነቷን፣ ለተፈራረመችው የሰላም ውል ተግባራዊነት ቁርጠኝነቷን፣ ለወደፊቷ ብሩህ አፍሪካ የብርሃን ፀዳል አከፋፋይ እንደምትሆን በአደባባይ ሲመሰክሩ ስናስተውል ሊገርመን አይገባም። ስለምን ቢሉ “ተግባር ከቃላት የበለጠ ስለሚከራከር ነው” ብለን “በዲፕሎማሲ ጥበብ” አሜንታቸውን ልናከብርላቸው ይገባል።
ይህ ዐምደኛ አንድም በሀገረ አሜሪካ በትምህርት ላይ በቆየባቸው ዓመታት የመንግሥ ታቸውን ሥርዓትና ባህርይ በቅርበት ለማወቅ በሚገባ ይተጋ ስለነበር፣ ሁለትም ከኢትዮጵያ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት እንደ አንዱ ሆኖ በበርካታ ሀገራት ጉብኝት ለማድረግና ከየመንግሥታቱ መሪዎች ጋር ለመወያየት ሀገሩ ዕድሉን አመቻችታለት ስለነበር የዲፕሎማሲን ተለዋዋጭ ባህርያትና አካሄድን የሚከታተለው በተለየ ፍላጎትና ቅርበት ነው።
ይህንን ጠነን ያለ ርዕሰ ጉዳይ ሊያዋዛ የሚችል አንድ ክስተት እናጋራ። ቀደም ተብሎ ለመጥቀስ እንደተሞከረው ጸሐፊው በምድረ አሜሪካ በትምህርት ላይ እያለ እንደማንም የውጭ ሀገር ተማሪ ዩኒቨርስቲው በሚያዘጋጃቸው የባህል ልውውጥ መርሃ ግብሮች ላይ የራሱን ሀገር ማስተዋወቅ ይጠበቅበት ነበር።
እናም በአንድ ዝግጅት ላይ በዚያ አካባቢ የሚገኙ የሀገሩን ወንድም እህቶች ባህሉን እንዲያደምቁለት ትብብር ጠይቋቸው የየብሔረሰባቸውን አልባሳት ለብስው እንዲመጡ አደራ አሸከማቸው። እነርሱም “እንኳንም ተጠይቀው ይቅርና በየምክንያቱም ቢሆን ሀገራቸውን ለማስተዋወቅ ይተጉ ስለነበር” ሴቶቹ የጋሞ እጀ ጠቢባን በተራቀቁበት የሀገር ልብስ፤ ወንዶቹም የየብሔረሰባቸውን አልባሳት ለብሰው በበዓሉ ላይ ልክ እንደ ከዋክብት ብርሃን እየተንቦገቦጉ የተዘጋጁበትን ትርዒት አቀረቡ።
የባህል ትርዒቱ እንደተጠናቀቀ ከግራ ከቀኝ የከበቧቸው ታዳሚዎች እንዲህ እያሉ በጥያቄ ያጣድፏቸው ጀመር፤ “እነዚህን አልባሳት የምትለብሱት በየትኞቹ በዓላቶቻችሁና ወራት ነው? በበረዶ ወራት የምትለብሱት ሌላ የተለየ የልብስ ዓይነት አላችሁ? በዓመት ስንት ቀናት ነው እነዚህን ልብሶች የምትለብሱት? ወዘተ.” የተዥጎደጎዱት የጥያቄ ዓይነቶች ከ እስከ የሚባሉ አልነበሩም።
ለሁለም ጠያቂዎች እንሰጥ የነበረው መልስ አንድና ተመሳሳይ ነበር። “እኛ የተለየ የበረዶ ወቅት የለንም። ከዓመት ዓመት እነዚህን ልብሶች መልበስ እንችላለን። አስቸጋሪ የምንለው የአየር ንብረት እምብዛም የለንም። በሁሉም የሀገሪቱ ክፍል በየትኞቹም ወራትና በዓላት እነዚህ አልባሳት ይለበሳሉ” በማለት ልባችንን ትክት እስኪለው ድረስ ለጠያቂዎቻችን በሙሉ መልስ ሰጠን ስንጨርስ እንደተመካከሩ ሁሉ በአድናቆት እንዲህ ሲሉ መለሱልን።
“እናንተ ኢትዮጵያዊያን ለካስ በችግርም ሆነ በደስታችሁ ተረጋግታችሁ የምትኖሩት፣ በባህርያችሁም ቅብጥብጥነት የማይስተዋልባችሁ ተፈጥሮ በተረጋጋ መስመር ስላኖረቻችሁ ነው። ርሃብን በትእግሥት፣ ችግሮችን በመቻል፣ ጦርነታችሁንም በስክነት መርታችሁ በማሸነፍ የኖራችሁት ለካንስ ተፈጥሮ ገርታችሁ ነው። እኛ አሜሪካኖችማ እንደምታዩትና እንደምታውቁን በተፈጥሮ የአየር ንብረት እንደ እናንት አልተባረክንም።”
“በክረምት ወቅት በረዶውና ቅዝቃዜው አይጣል ያሰኛል። የበጋው መክረርና ሙቀት መፈጠርን ያሰጠላል። ጠዋት ብራ የመሰለው ከደቂቃዎች በኋላ በውሽፍር ዝናብ ሊጠቃ ይችላል። ሱናሚን መሰል አደጋዎች አብረውን የኖሩ መርገምቶች ናቸው። ስለዚህም የእኛ የአሜሪካ ዜጎች ባህርይ ልክ እንደ ተፈጥሮ ስክነት አይስተዋልበትም። ደስታችንም ሆነ ሀዘናችን አርቲፊሻልና የይምሰል ነው። አኗኗራችንም በለበጣ የተሸፈነ ነው። ከአለባበስ እስከ አመጋገባችን “ኦርጂናል” ብለን የምንለው ነገር እጅግም ነው።”
“እንኳንስ ማሕበራዊ አኗኗራችን ቀርቶ ፖለቲካችንንና ዲፕሎማሲያችንም ቅብጥብጥ ባህርያት ይስተዋልባቸዋል። ስክነት ይጎላቸዋል። አሜሪካ በዓለም ላይ የምትወስዳቸው በጎም ይሁን ክፉ ውሳኔዎችና እርምጃዎች ስሜታዊነት ያጠላባቸዋል። ረግተንና ሰክነን ለማሰብ ይህን መሰሉ ሥር የሰደደው ባህርያችን እድል አይሰጠንም። ችግሩ የተፈጥሮ ይሁን የማሕበረሰብ ሥሪታችን በሚገባ አላወቅነውም…” ሌላም በብዙ ጉዳዮች ዙሪያ መጨዋወታችንን አንዘነጋውም።
የአሜሪካ ፖለቲካና ዲፕሎማሲ ስክነት ጎሎት የሚቅበጠበጠው ምክንያቱ ከዚህ ጋር ይያያዝ ይሆን? የሀገሬ መሪዎችስ እንደተባለው በእርጋታና በማስተዋል የዲፕሎማሲውን የበላይነት ሊጎናጸፉ የቻሉት እንደተመሰከረልን የተፈጥሯችን ባህርይ አግዟቸው ይሆንን!? ለድምዳሜው ባንቻኮልም፤ አይሆንም ለማለቱም አንጣደፍም። የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ አካሄድ በርጋታ መመስገን ብቻም ሳይሆን፣ በሰፋ ዝግምተኛነቱም የሚወቀሰው ምናልባት ካነሳነው የባዕዳን ርዕሰ ጉዳይ ጋር ይገጣጠም እንደሆነ ጥናት ማድረጉና ደጋግሞ ማሰላሰሉ ክፋት ያለው አይመስለንም። ሰላም ይሁን።
(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ) gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ረቡዕ ታኅሣሥ 12 ቀን 2015 ዓ.ም