አገር እንደ ዘንድሮ ሰላምን በሚሹ ድምጾች ተሞልታ አታውቅም። ዛሬ ዛሬ ለአገራችን ድምጻችን አንድ አይነት ነው..ሰላምና ሰላም። ሰላም ይናፍቃል። ሰላም ከመቼውም ጊዜ በላይ ናፍቆናል። በርግጥ በድህነት በምትማቅቅ አገር ላይ፣ ተስፋ በራቀው ሕዝብ መካከል ሰላም እጅጉን ትናፍቃለች፡፡
በተለይ ደግሞ በወንድማማች መካከል በሚደረግ መገፋፋት ውስጥ ሰላም ከመቼውም ጊዜ በላይ ይናፈቃል። እንዳለፉት አመታት ዘንድሮም ሰላምን በመናፈቅ ብቻ ግዜው መጥቶ እንዲሄድ አንፈልግም። የምናየውም፤ የምንሰማውም ይህ እንደማይሆን ተስፋ ሰጭ ነው።
በመንግስት ሰላም ፈላጊነት፣ በኢትዮጵያውያን የጋራ ጸሎት፣ የጋራ ምኞት፣ የጋራ ስለት የዘንድሮ አመት በርካታ አዲስ ነገሮችን ጀባ ብሎን እንደሚያልፍ ተስፋ እናደርጋለን። ከዚህ ውስጥ አንዱና ዋነኛው ሰላም ነው። ዛሬ ላይ እርቅ የዋጃት አዲስ ሀገር፣ አዲስ አስተሳሰብ ያስፈልገናል፡፡
በእርቅ የተዋጀ አዲስ አገርና አዲስ አስተሳሰብ እንዲኖረን የሰላምን ዋጋ መረዳት ይኖርብናል። በጦርነት ማሸነፍ እንደሌለ፣ በድሃ አገርና በድሃ ሕዝብ መካከል ጦርነት ከኪሳራ ውጪ ትርፍ እንደሌለው መረዳት ያስፈልገናል።
ባለፉት ጥቂት አመታት ውስጥ ተስፋ የጣልንባቸው ቀናቶች ተስፋዎቻችንን ሰልቅጠው የተመኘነውን ሰላም ሳይሰጡን አልፈዋል። አሁን ግን ተስፋ ባላቸው የሰላም፤ የአንድነት እና የእርቅ ቀናት ውስጥ መጓዝ ከጀመርን ቀናት ተቆጥረዋል እነዚህን ቀናት በጋራ እንባችን፣ በጋራ ጸሎታችን ያመጣናቸው ናቸው፡፡
አሁን የሚጠቅመን ሰላምን ከፊት አድርገን መራመድ ብሎም በድርድርና በእርቅ ችግሮቻችንን ማሸነፍ ነው። ችግር በተፈጠረብን ቁጥር ወደጦርነትና ወደ መገዳደል ከገባን ተስፈኛዋን ኢትዮጵያ መፍጠር አንችልም። ሲጀመር ተስፋ ጦርነት ውስጥ የለም። ተስፋ ያለው በሰላምና በመነጋገር ውስጥ ነው።
ዓለም በጦርነት የተገኘ ተስፋ አይታ አታውቅም። የሰው ልጅ በታሪኩ ሰላምና ተስፋውን በመገዳደል አምጥቶ አያውቅም። እኛም ጦርነት አቁመን እየቆጠርናቸው ያሉት ቀናቶች የሚበረታቱ ፤ በእርቅ ሰላማችንን መጠበቅ እንደምንችል ያመላከቱ ናቸው ፡፡
በሰነቅንው የሰላም ተስፋና በተጨባጭ በምናያቸው እውነታዎች ይህ ዓመት እንዳለፉት አመታቶች የሞትና የጉስቁልና፣ የዋይታና የሮሮ እንደማይሆን እርግጠኛ ወደ መሆን እየተጓዝን ነው። በቀጣይ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን ለሚደረገው ጥረት አገራዊ የምክክር መድረኩ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆንም ይታመናል፡፡
ሰላም በአንድ ወገን ብቻ የሚሆን አይደለም..እንደዛ ቢሆንማ በመንግስት የሰላም ጥረት ላይ ተመርኩዘን ብዙ ባፈራን ነበር። በሰላም መድረክ ላይ ሰላም ፈላጊ ነን የሚሉ ልቦች ሁሉ ትጥቃቸውን መፍታት አለባቸው። መሳሪያቸውን መጣል አለባቸው። ይልቁንም ልባቸውን ለአንድነትና ለመነጋገር ዝግጁ መሆን አለባቸው፡፡
የዘንድሮው ዓመት የሰላማችን ብስራት እንደሚሆን እናምናለን። ለኢትዮጵያ የሚሆን በርካታ የተስፋና የመንጋት ብስራት አንግበው ሰላም የሚዘምሩ ድምጾችን እንደምንሰማ፤ በአፋቸው የዘምባባ ዝንጣፊ የያዙ ከዚም ከዛም የሚበኑ የሰላም ርግቦች በኢትዮጵያ ሰማይ ላይ እንደምናይ ተስፋ እናደርጋለን፤ በርግጥ ማየትም ጀምረናል ።
ባለፉት ጊዜያቶች የተከሰቱ ስቃዮች እንዳይደገሙ፣ ፍቅር በማጣት፣ የይቅርታ ልብ በማጣት፣ ተነጋግሮ መግባባት በማጣት የዘጋናቸው የሰላም መንገዶች በዚህኛው አመት ተከፍተው አዲስ የሰላም አየር እንደምንተነፍስ እንተማመናለን።
እየታዩ ያሉት የሰላም አማራጮች ኢትዮጵያን ከመታደግና ችግሮቿን ከማጽዳት ባለፈ ነውር የላቸውም። ለሰላም እጅ መስጠት መሸነፍ አይደለም። ለሰላም እጅ መስጠት ማሸነፍ ብቻ ነው.. ከዚህ ውጭ ምንም መሆን አይችልም። መንግስት ለሰላም የዘረጋው እጅ ለኢትዮጵያ የተዘረጋ የማሸነፍ እጅ ነው፡፡
መጪዎቹ ጊዜያት የመከራችን ማብቂያ ናቸው። በጥላቻና በመገፋፋት የጨቀየውን የሰኔን ገመገም፣ የሐምሌን ጨለማ፣ የነሐሴን ጭጋግ በተስፋና በብርሃን የሚለውጡ ናቸው። በኢትዮጵያ ምድር እንዳናያቸው፣ እንዳንሰማቸው የምንፈልጋቸው የሞትና የጥይት መርዶዎች ሽሮ ብስራት የሚነግረን የመታደስ መልከታችን ነው።
ጊዜ ሚዛን ነውና የመከራችን አመት 2014 በተፈጥሮ ለበቅ ሸኮናውን ተብሎ ከነችግሩና ከነችግራችን በዘመን ጉያ ውስጥ ተሸጉጧል። አዲሱ አመት ደግሞ ብኩርናውን እንደያዘ የጠፋብንን ሊሰጠን፣ ያጣንውን ጀባ ሊለን ራሱን በተስፋና በአዲስነት ሞሽሮ በመሀከላቸን እየተጓዘ ነው፡፡
ሰላም በሌለበት አገር ላይ ምንም ነገር ምንም ነው..ትርጉም የለውም። የአዲስ አመት መንፈስ ሳይርቀን፣ ወግ ማረጉን አጣጥመን ሳናበቃ፣ የመስቀል ወፍና የአደይ አበባ ከቀየው ላይ ሳይሰወሩ በንግግር የከበረ ሰላምን ለአገራችን ጀባ ልንላት ይገባል። በጥላቻ የማይታጠፉ ለሰላም የተዘረጉ ሰላማዊ እጆች በኢትዮጵያ ምድር ላይ ሊበረክቱ ግድ ይላል።
ከፍ ብዬ በርዕሴ ላይ እርቅ የዋጀው አዲስ አገር እና አዲስ አስተሳሰብም ያሻናል ስል የተነሳሁት በምክንያት ነው። ምክንያቴን ግልጽ ለማድረግ ያክል አዲስ አገር ስል ብዕሬን ያሰላሁት ከጥላቻና ከዘረኝነት ከጦርነትም የራቀች አገር እንድትኖረን በመመኘት ነው፡፡
አገራችን አሁን ላይ ምንድነው የሚያስፈልጋት ብለን ብንጠይቅ መልሱ አንድ ነው .. ሰላም። አሁን ላይ ጥያቄዎቻችን ሁሉ የሰላም ጥያቄዎች ናቸው። ጥያቄና መልሶቻችን ሰላም በሆኑበት ወቅት ላይ እርቅ የዋጀው አዲስ አገር ብዬ መነሳቴ ይሁንታን ያሰጠኛል ብዬ አምናለሁ። አሁን ላይ ሩጫችን ሁሉ በጦርነት በቆየንባቸው ጊዜያቶች ያጣናቸውን በጎ ኢትዮጵያዊ ቀለሞች ለመመለስ መሆን ይኖርበታል፡፡
እኚህ ቀለሞቻችን የሚመለሱት ደግሞ በእርቅ አዲስ አገር ስንፈጥር ብቻ ነው። ይሄ ብቻ አይደለም ለሰላም በተዘረጉና ሰላማዊ እጆች የሳሏት ኢትዮጵያም ታስፈልገናለች። የኢትዮጵያን ጉድፍ የሚያጠሩ፣ ነውሯን የሚሸፍኑ የወንድማማችነት ካባዎች ያስፈልጉናል። ከዚህ በኋላ የምንራመድባቸው መንገዶች በአዲስነት የተበጁ መሆን አለባቸው። በፖለቲካው፣ በኢኮኖሚው በተለያዩ ዘርፎች ላይ አዲስነት የዋጀው ለውጥ ያስፈልገናል፡፡
ፍቅርን የሚያውቅ ሁሉ አዲስ ነው። ፍቅር በሌለበት ልብ ውስጥ አዲስነት የማይታሰብ ነው። ለሰላም የተዘረጉ የመንግስት እጆች ከአዲስነትም በላይ አንጸባራቂዎች ናቸው። እኚህ አዲስና አንጸባራቂ የሰላም እጆች እንደ መስቀል ወፍ ወቅት እንዳይኖራቸው ሁሌም ለሰላም ተዘርግተው ሊኖሩ ይገባል።
የኢትዮጵያ አዲስነት ከእርቅና ከመተቃቀፍ እንዲጀመር እሻለሁ። ነውጥ ናፋቂዎች ዓላማ አለን የሚሉ ከሆነ ከተዘረጋው ከመንግስት የሰላም እጅ ጋር መጨባበጥ አለባቸው። መነጋገር አለባቸው። የኢትዮጵያ አዲስነት ከእርቅ የሚጀምር ከሆነ ሁሌም የሰላም እጆች ይኖራሉ። ከዚህም ባለፈ እንደ አገር ከጦርነት በፊት የሚዘረጉ የሰላም እጆች ያስፈልጉናል። የሰላም እጆቻችን ከጦርነት በኋላ የሚዘረጉ ከሆነ ዋጋ ያስከፍሉናል።
አዲስነት አስተሳሰብ ነው። ሰው ሀሳቡን ማረቅ ከቻለ አዲስ መሆን ይችላል። ይሄ ብቻ አይደለም ሰው ሀሳቡን ማሸነፍ ሲችል መጀመሪያ የሚማረው ፍቅርን ነው..በፍቅር ማሸነፍን። እናም ለሁሉ በሚበጅ ሰላም ውስጥ በመኖር በጦርነት የምንከፍለው ዋጋ ማስቀረት ይጠበቅብናል።
በእርቅ ችግሮችን እንደመፍታት፣ ለሰላም በተዘረጉ እጆች መከራዎችን እንደማስቀረት ምን አዲስነት አለ? ዛሬ ከትላንት የተሻልን ሌላ እንሁን። ከዚህ ቀደም በተለያየ ጽሁፌ ላይ እንዳስቀመጥኩት እኛ ካልተቀየርን የሚቀየር ዘመን የለም። መስከረም አዲስ የሚሆነው በእኛ ሃሳብ ውስጥ፣ በእኛ መታደስ ውስጥ ነው።
ከላይ የገለጽኩላችሁ ሰላምና አንድነት፣ ከላይ የገለጽኩላችሁ ለውጥና ስኬት ይሄን ጽንሰ ሀሳብ ተንተርሰው ነፍስ የሚዘሩ ናቸው። ይሄ ሀሳብ የትም ቦታ ላይ ህልውና ያለው ሀሳብ ነው። ተጀምሮ የሚያበቃበት የሕይወት ስፍራ የለውም። ሁሉም ቦታ ላይ መሪና ቀዳሚ ሆኖ የሚቆም እውነት ነው፡፡
እርቅ በዋጀው ቁምነገር አዲስ አስተሳሰብን መውረስ ይኖርብናል። ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ አደረጃጀቶቻችን ተግባቦትን መሰረት ያደረጉ የአዲስ አስተሳሰብ መሰረት ሊሆኑ ይገባል። እየገነባን የሚፈርስብን፣ ችግር በተፈጠረብን ቁጥር ወደጦርነት የምንገባው ባልተደራጁና ለተግባቦት ዝግ በሆኑ እሳቤዎቻችን ነው፡፡
ከኃይል ወጥታ ውይይት መር በሆነ ፖለቲካዊ ፍልስፍና የምትመራ ኢትዮጵያ ሩቅ እንደማትሆን ፤ ለሰላም በተዘረጉ እጆች በችግሮቻችን ላይ የበላይ ሆነን የምናሸንፍበት ጊዜ ቅርብ እንደሚሆን ይሰማኛል። አስታራቂ ሀሳቦች ጠፍተው በውሸት ትርክት የምንሞትበት ጊዜ እንደሚያበቃ ይታየኛል፡፡
ይሄ ጊዜ እንዲመጣ ሁላችንም ሰላም ወዳድ መሆን አለብን። ይሄ ጊዜ የአገራችን መከራ እንደ እርኩስ መንፈስ ሶስት ጊዜ አጓርቶ የሚወጣበት ጊዜ ነው። ይሄ ጊዜ እንዲመጣ በእርቅ የዳበረ፣ በውይይት የጠነቀረ አዲስ አስተሳሰብ ያስፈልገናል። እጆቻችን ከነውር ርቀው ለሰላም እንዲዘረጉ፣ ልቦቻችን ከክፋት ሸሽተው ለፍቅር እንዲከፈቱ ኢትዮጵያን እናስብ። እርቅ የዋጀው አዲስ አገር እና አዲስ አስተሳሰብ እንዲኖረን ወደ ሰላም አገር ወደ ምስራቅ እናስተውል።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ሰኞ ታኅሣሥ 10 ቀን 2015 ዓ.ም