አሜሪካ ራሷን የነጻው ዓለም መሪና የዴሞክራሲ ጠበቃ፣ የፍትሕና ርትዕ ዘብ አድርጋ ብታይም ግብሯ ግን ለየቅል ነው። ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን እንዳሉት ዘረኝነት ዛሬም በ2022 ዓ.ም ተቋማዊ ነው። ከመራጩ ሕዝብ ግማሽ ያህሉ በዴሞክራሲያዊ ተቋሟ እምነት አጥቷል። ሀሰተኛ መረጃና የሴራ ፖለቲካ በዜጎቿ መሐል ልዩነት እየጎነቆለ፤ ጥላቻን እየከዘነ ይገኛል። በአገራት የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ ስትገባ የራሷ አሮባት የሰው ታማስላለች የሚባለው ለዚህ ነው።
እንደ ንጉሳዊ አገዛዝ ወይም እንደነ የሮማን ኢምፓየር ዘመንም ያደርጋታል። ለዚህ አንድ መገለጫ ላንሳ። ስለ አሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ልዑክ ወይም ፕሬዚዴንሺያል ኦንትራዥ። የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የውጭ አገር ጉዞ የሚያደርጉ ከሆነ በደህንነትና በጸጥታ ስም እሺዎች ይከተሏቸዋል። ቢስት በመባል የሚታወቁ ፕሬዚዳንታዊ ኒሞዚኖችን ጨምሮ አምቡላንስ ሳይቀር ከ50 በላይ ጥይትና ፈንጅ ከል ተሽከርካሪዎች በበርካታ ግዙፍ አንቶኖቮች ተጭነው ቀድመው ይጓጓዛሉ። አስፈላጊ ከሆነም ሔሊኮፕተሮች ይላካሉ።
ፕሬዚዳንቱ በልዩው ኤር ፎርስ ዋን ጉብኝት ወይም ስብሰባ የሚያደርጉበት አገር እንደ ደረሱ ከእነ ጋሻ ጃግሬያቸው መንገድ ተዘግቶላቸው በእነዚህ ተሽከርካሪዎች ታጅበው ቀድሞ በጥልቅና በጥብቅ ሚስጥር በተያዘው መርሀ ግብራቸው አማካኝነት ጉብኝነታቸውን ይጀምራሉ። የተወሰኑ የደህንነትና የጸጥታ ሰዎች ፕሬዚዳንቱን ቀድመው ይገባሉ። ከፕሬዚዳንቱ ጋር ደግሞ ከፍተኛ ሹማምንት ከእነ ረዳቶቻቸው፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ የደህንነትና የጸጥታ ሰዎች፤ በርካታ የሚዲያ ልዑክ አባላት፣ የፕሬዚዳንቱ የህክምና፣ የኋይታወስ ባልደረቦችና ሌሎች አብረው ይጓዛሉ።
ምን አለፋችሁ የልዑኩ ብዛት ከአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ አጠቃላይ ልዑካን አይተናነስም። በሚጎበኘው አገር ሎጂስቲክ ላይ የሚፈጥረውን ጫና ልተወውና፤ በተቀባይ አገር መሪ ስነ ልቦና ላይ የሚያስከትለው ተጽዕኖ ቀላል አይደለም። አንድምታውም ከእኛ የደህንነትና የጸጥታ ተቋም፤ መጓጓዣና ሎጂስቲክስ ውጭ በእናንተ ዕምነት የለንም። በገደምዳሜ ከእናንተ የበለጥን ነን። ኃያልነታችን እዚህ ድረስ ነው ማለታቸው ነው። ከዚያ ፕሬዚዳንቱ ልዑካቸውም በተራው ይናገራል። የሚጎበኘው አገር ያደምጣል።
እኛ የምንወደውን ውደዱ፤ የምንጠላውን ጥሉ፤ ያዘዝናችሁን የፖሊሲ ማሻሻያ አድርጉ፤ ወዘተረፈ ሲሉ ቀጭን ትዕዛዝ ያስተላልፋሉ። የአገራት መሪዎች የተባለውን ከማድመጥ ባሻገር መልስ ለመስጠትና ለመገዳደር ወይም ለመሞገት እድል ላያገኝ ይችላል። የአሜሪካና የአገራት ግንኙነት የጌታና የሎሌ ያህል ነው የሚባለው ለዚህ ነው። ሉዓላዊነትን የሚዳፈርና ክብረ ነክ ነው የሚባለው ለዚህ ነው። ተላላኪ አልሆንም ያለ መንግስት፤ ምን ሊከተለው እንደሚችል እና እንዴት አሳሩን እንደሚበላ ከመንግስታችን በላይ ጥሩ መሳያ የለም ማለት ይቻላል።
የመንግስቷ ንጉሳዊ ባህሪ ሌላ ጥሩ ማሳያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋ ነው ። በአገራት ላይ እሴቶቼ የምትላቸውን ዴሞክራሲያዊ ስርዓትና የሰብዓዊ መብት ጥበቃን በቅድመ ሁኔታነት ታስቀምጣለች። ይሄን በተላለፉ አገራት ላይ ደግሞ ማዕቀብ ታዥጎደጉዳለች። ሲያሻትም መሪዎችን በሲአይኤ ሴራና ሸፍጥ ጠልፋ ትጥላለች። ይህ አልሆን ካላት ጦሯን አዝምታ የመንግስት ለውጥ ታደርጋለች። ሆኖም ይህ ፖሊሲዋ ወጥ ካለመሆኑ ባሻገር አድሎአዊ ነው። ብሔራዊ ጥቅሟን እስካስጠበቁላት ድረስ አምባገነንና ፈላጭ ቆራጭ አገዛዞችን አቅፋ ደግፋ ትይዛለች።
በአረብ አገራት፣ በላቲን አሜሪካ፣ በመካከለኛው ምስራቅ፣ በሩቅ ምስራቅና በአፍሪካ ከለየላቸው አምባገነን መሪዎች ጋር በፍቅር እፍ ከንፍ ስትል ኖራለች። በዚህ የተንጋደደ ፖሊሲዋ እንደ አሽዋ የበዛ ጠላት አፍርታለች። አይንሽን ለአፈር ተብላለች። ገዢዎች ሳይወዱ በቻይናና ራሽያ ጉያ ተሸጎጡ። ዛሬ አሜሪካ አገራትን በቻይና ተነጥቃለች። የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋ እስትራቴጂካዊ ስህተት ፍንትው ብሎ እየታያት ነው።
ሰሞነኛውን የሳውዲአረቢያን የቻይናን ስምምነት ልብ ይሏል። የቻይናንና የራሽያን ግንኙነት በአናቱ ይጨምሯል። በአጠቃላይ የአሜሪካ ጂኦፖለቲካዊ ስፍራ እየተሸረሸረ ነው። ዓለም ከአሜሪካ የልዕለ ኃያልነት መዳፍ ፈልቅቃ እየወጣች ነው። የዓለም ፖሊስነቷ እያበቃለት ነው። ቻይና በእግሯ እየተተካች ነው። ሆኖም ቻይና ጃፓንን አስለቅቃ ሁለተኛውን ግዙፍ ኢኮኖሚን ብትገነባም አሜሪካ ላይ ለመድረስ ግን እንደምናስበው ቀላል አይደለም።
በግሌ የአሜሪካን ኃያልነት እስከ ምጽዓት ይዘልቃል ብዬ አምናለሁ። መሠረቱ በማይናወጥ ዐለት ላይ የታነጸና በመላው የሰው ልጆች እርብርብ የተገደገደ ነውና። እንደ የፋርስ፣ የባቢሎን፣ የቤዛንታይን፣ የሮማንና የኦቶማን ኢምፓየር ዘመን በመጣ በሄደ ቁጥር የሚወድቅ አይደለም። የእርስ በርስ ጦርነትን፣ ታላቁ ውድቀትን፣ ሁለቱንም የዓለም ጦርነቶች፣ የ2007/08 ዓ.ም የኢኮኖሚ ቀውስ አልፎ ነውና ዛሬ ላይ የደረሰው። የቻይና ጥቅል የአገር ውስጥ ምርት GDP ከአሜሪካ ጋር ያለው ልዩነት እየጠበበ ቢመጣም ከዕድገት ጥራት አኳያ በአጠገቡ አይደርስም። ለዚህ ነው ከአሜሪካ ጋር የሚኖረን ግንኙነት መተኪያ የሌለው።
ይሁንና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋ ከአገራት ጋር በሚኖራት ግንኙነት ላይ ደንቃራ፣ ክብረ ነክ፣ አዋራጅ፣ አሸማቃቂ፣ ዕብሪተኛ፣ ተጋፊና አድሏዊ መሆኑ አይካድም። የአንድ ሉዓላዊ አገር መሪ ከአሜሪካ ፕሬዚዳንትም ሆነ ከአሜሪካ የሚቀርብለትን ፖሊሲ ያስፈጽማል፤ የሚነገረውን እጁን ወደ ኋላ አጣምሮ ይሰማል እንጂ ቢናገር የሚሰማው የለም። ፕሬዚዳንቱ ይቅርና አዲስ አበባ ያለው አምባሳደር በአገሪቱ የውስጥ ጉዳይ እየገባ እንደሚፈተፍት የአደባባይ ሚስጥር ነው። ባለፉት ሁለት ዓመታት የአሜሪካ የቀጣናው መልዕክተኛ የነበሩት አምባሳደሮች እንዴት እንዴት ያደርጋቸው እንደነበር መቼም አንረሳውም።
በአንጻሩ ለዜጋው አጋም ለአሜሪካ አልጋ የነበረው የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በአሜሪካ አግኝቶት የነበረውን ሞገስና አሁን ያለንበትን ሁኔታ ያጤኑአል። አሁን አሁን ይህ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ዓለም ከምትገኝበት ነባራዊ ሁኔታ ጋር የማይሄድ ወይም ፕራግማቲክ እንዳልሆነ መጀመሪያ በዘርፉ ሊቃውንት፤ በማስከተል በተወሰኑ ፖለቲከኞች ግንዛቤ የተጨበጠ ይመስላል። በዚህ የእነ ቻይና ጂኦፖለቲካዊ ተጽዕኖ፣ የአፍሪካ እምቅ አቅም በዚያ የራሽያና የዩክሬን ጦርነት ታክሎበት እውን አሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋን ትከልስ ይሆን የሚለውን አብረን የምናየው ሆኖ ሰሞነኛው የአሜሪካና የ49 የአፍሪካ አገራት የመሪዎች 2ኛ ጉባኤ አስመልክቶ ከአሜሪካ የሚሰሙ ንግግሮች ተስፋ የሚያሰንቁ ሆነው አግኝቻቸዋለሁ።
ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን በጉባኤው ባደረጉት ንግግር፤” አሜሪካ ለአፍሪካ መጻኢ ዕድል ስኬት ያለ ምንም ገደብ ትተጋለች። የአፍሪካ ስኬት የተቀረው ዓለም ስኬት ጭምር ነው።”ብለዋል። የአሜሪካ ምክትል ፕሬዚደንት ኻሚላ ሐሪስ በበኩላቸው “ይኸ ጉባኤ አሜሪካ ለአፍሪካ አጋሮቻችን ያላትን ዘላቂ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው። ጉባኤው በመከባበር፣ የጋራ ጥቅሞች እና እሴቶች መርኅ ላይ የተመሠረተ ይሆናል። ኤኮኖሚያዊ ግንኙነታችንን ማጎልበት የጉባኤው አንድ ዓላማ ይሆናል” ብለዋል። እንዲሁም የአሜሪካ የብሔራዊ ደኅንነት አማካሪ ጃክ ሱሊቫን ባለፈው ሰኞ በሰጡት መግለጫ፤ “ ጉባዔው… አፍሪካ ወሳኝ ጂኦፖለቲካዊ ሚና እንዳለት ዕውቅና በመስጠት ላይ የተመሠረተ ነው። አህጉሪቱ የአፍሪካን ህዝቦች ብቻ ሳይሆን የዓለምን የወደፊት እጣ ፈንታም ትወስናለች።
አሜሪካ ለሚቀጥሉት ሶስት ዓመታት በአህጉሪቱ 50 ቢሊየን ዶላር ኢንቨስት ታደርጋለች፤” በማለት ያላትን ስትራቴጂካዊ ስፍራ ገልጸዋል። በመግቢያየ ላይ ላነሳሳ የሞከርኩትን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ውስንነት ትንሽ ሰፋ አድርገን እንመልከተው።
አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር የዲፕሎማሲ ግንኙነት ከጀመረች ወደ 120 ዓመታት እየተጠጋት ነው። በአሜሪካም ሆነ በኢትዮጵያ መንግስታት ቢቀያየሩ አንድ ጊዜ ሞቅ ሌላ ጊዜ ቀዝቀዝ አልፎ አልፎም ለብ እያለ ቀጥሏል። የሁለቱ አገራት ግንኙነት አሜሪካ ከሌሎች አገራት ጋር ታራምደው ከነበረ ግንኙነት የተለየ አልነበረም። ከብሔራዊ ጥቅሟ በተጻራሪ የሚቆም መንግስት በመጣ ጊዜ ለመቀየር የማትፈነቅለው ድንጋይ የለም። በ19ኛው መክዘ እኩሌታ ማብቂያ አካባቢ በላቲን አሜሪካ በደቡብ ምዕራብ ፓሲፊክ እንዲሁም በ20ኛው መክዘ መግቢያ ደግሞ በፓናማ፣ ሆንዱራንስ፣ ኒካሯጓ ሜክሲኮ፣ ሄይቲና ዶሚኒካን ሪፐብሊክ መንግስታትን ለውጣለች።
በቀዝቃዛው ጦርነት (1945_1991 እኤአ) ዓለም በሶሻሊስትና በካፒታሊዝም ርዕዮተ ዓለም ጎራ በተከፈለ ጊዜ የኢትዮጵያና የአሜሪካ ግንኙነት ሻክሮ ነበር። ደርግ ሶሻሊስት ስለነበርና አሰላለፉም በሶቭየት ሕብረት ረድፍ ስለነበር አሜሪካና አጋሮቿ ለተቃዋሚዎች በግልጽ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ድጋፍ በማድረግ ደርግን በተራዘመ ትጥቅ ትግል ገርስሰው አስመራንና አዲስ አበባ እንዲገቡና የስልጣን መንበሩን እንዲቆጣጠሩ በማድረግ የማይተካ ሚና ተጫውተዋል።
በተለይ አሜሪካ በኢትዮጵያ እንዳደረገችው በመላው ዓለም የ70 አገራትን መንግስት ለመለወጥ በህቡዕና በይፋ ተንቀሳቀሳለች። የቀዝቃዛው ጦርነት በበርሊን ግብ መፍረስ በሶቪየት ሕብረት መበታተን ከተቋጨ ከ30 ዓመታት በኋላ ዛሬም የማትፈልገውን መሪ ለማስወገድ በምርጫ ጣልቃ ትገባለች በውክልና ወይም በቀጥታ መንግስት ትገለብጣለች። አገሬን ያለ ብሔርተኛ/nationalist/ ተላላኪና አሻንጉሊት አልሆንም ያለና ለዜጋው ጥቅም የቆመ መንግስት ከአሜሪካና ከምዕራባውያን ጥቅም በተጻጻሪ እንደቆመ እንደጠላት ተቆጥሮ እንዲወገድ ይደረጋል።
ባላንጣየ ከምትላት ቻይና ጋር የጠበቀ ግንኙነት ያለውም በጠላትነት ተፈርጆ ጥርስ ይነከስበታል። የቡርኪናፋሶው ቶማስ ሳንካራ የጋናው ኩዋሚ ንኩሩማህ የኢራቁ ሳዳም ሁሴንና የሊቢያው ሞአመር ጋዳፊ ከሰለባዎቿ መካከል ይጠቀሳሉ። በምርጫ ጣልቃ መግባትም ሆነ የመንግስት ለውጥ ማምጣት የአሜሪካንን ጥቅም ለማስከበር አዋጭ ነው ቢባልም መጨረሻው ግን አገራትን ወደለየለት የእርስ በርስ ጦርነት እና ቀውስ ስለሚዘፍቅ ውጤታማ ባይሆንም ዛሬም በጀ ብላ ቀጥላበታለች።
የቅርቦቹን እነ አፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ሶሪያ፣ የመን፣ ቬኒዞላንና ሄይቲ ልብ ይሏል። ዛሬም ጥቅሜን ያስከብርለኛል የምትለውን መንግስት ለማንገስ በኢራንና በሶሪያ በሌሎች በርካታ አገራት አሻንጉሊትና ተላላኪ መንግስት ለመተካት ሌት ተቀን እያሴረች ነው። አሜሪካ እኤአ 1946_2000 በ81 ሉዓላዊ አገራት ምርጫ በይፋ ወይም በስውር ጣልቃ ገብታለች። በጣሊያን፤ በፊሊፒንስ፣ በሊባኖስና በጃፓን ምርጫዎች ጣልቃ በመግባት እንዳሻት የምታሽከረክረው መንግስት እንዲመረጥ አድርጋለች።
የመንግስታቱ ድርጅት ቻርተር አንቀጽ 2 ቁጥር 4 ላይ በግልጽ የአንድን ሉዓላዊ አገር መንግስት በኃይልም ሆነ በሴራ ለመለወጥ የሚደረግ ዕንቅስቃሴን የሚያወግዝ ድንጋጌ ከጸደቀ በኋላ እንኳ አሜሪካ ይህን ዓለማቀፍ ሕግ በመተላለፍ የ70 አገራትን መንግስታት ለውጣለች። ለዓለም ሰላም ለሕግ ልዕልና ለሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ቆሚያለሁ የምትለው አሜሪካ እንዲህ ናት። ቆሜላታለሁ የምትለው እሴትና መርህ የሸፍጧ መሸፈኛ ነው። እስከ ዛሬ በአገራችን እየሆነ ያለው ይሄን የሚያረጋግጥ ነው።
በአራት ዓመታት ከእነ ውስንነቱ በአገሪቱ ታሪክ ሀቀኛ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለማስፈን ሰብዓዊ መብትን ለማክበር አሰራሩንና አደረጃጀቱን ለመለወጥ አፋኝ ሕጎችን በማስወገድና በማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝም አዳዲስ ሕጎችን በማውጣት ምቹ መደላድል እየፈጠረ ለውጡ ዘላቂ እንዲሆንም ገለልተኛና ነጻ ተቋማትን እየገነባ ነው። እንደ ምርጫ ቦርድ ፍርድ ቤት የደህንነትና የጸጥታ መዋቅር የእንባ ጠባቂና የሰብዓዊ መብት ኮሚሽኖችን መስርቷል። በአሸባሪነት ተፈርጀው የነበሩ የፖለቲካ ድርጅቶችና ሚዲያዎች ወደ አገር እንዲገቡና ታግደው የነበሩ ከ200 በላይ ጋዜጦች መጽሔቶች ድረ ገጾች ጦማሮችና ዩቲውቦች በነጻነት እንዲንቀሳቀሱ ከመደረጉ ባሻገር በአገሪቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ነጻ ተአማኒና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በሰላም ተጠናቆ እያለ አሜሪካና ምዕራባውያን በልኩ እውቅና መስጠት አልፈለጉም። ሕዝብ በነቂስ ወጥቶ የመረጠውን መንግስት ከመቀበል ይልቅ በግልጽም ሆነ በስውር የመንግስት ለውጥ ለማድረግ ሴራ ሲሸረቡና በተግባርም ሲንቀሳቀሱ ታዝበናል።
ከፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ወዲህ ግን የአቋም መለሳለስ እየተመለከትን ነው። ከስምንት ዓመታት በኋላ ለ2ኛ ጊዜ በተካሄደው የአሜሪካ-አፍሪካ የመሪዎች ጉባኤ ፕሬዚዳንቱም ሆኑ ሌሎች የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች ያስተላለፉት መልዕክት እውን አሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋን ትከልስ ይሆን የሚል ጥያቄ አጭሮብኛል። የአዲስ ምዕራፍ ጅማሮስ ይሆን !?
የአገራችንን ሰላም ፈጣሪ ያጽናልን !
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን እሁድ ታኅሣሥ 9 ቀን 2015 ዓ.ም