ስለ ምናባዊ ገንዘብ አሁናዊ ሁኔታ እና ምን ያህል ለማጭበርበር አደጋ የተጋለጠ እንደሆነ በተከታታይ ለንባብ በበቁት መጣጥፎቼ ለማሳየት ሞክሬያለሁ። በዛሬው መጣጥፍ ደግሞ ስለ ክሪፕቶ ከረንሲ ንግስቷ መጨረሻና የባለሙያ ምክር ተካቷል። ግንዛቤ ሊጨበጥበት የሚገባው የመጀመሪያው መርህ ፤ ገንዘብ ዋጋ የሚኖረው ሌላው ሰውም ዋጋ ሲሰጠው ነው። በታሪክ ባንክ ያተመው ገንዘብ ይሁን ሳንቲም አልያም የከበሩ ማዕድናት ወይም ዛጎል ለመገበያያነት ይውሉ የነበሩት ብቸኛ ምክንያት በሁሉም ተጠቃሚዎች ዘንድ አመኔታ ስለተጣለባቸው ነው።
በርካቶች ለአመታት በመንግስታት ዘንድ ተቀባይነት እንዳገኙት መደበኛ መገበያያዎች ሁሉ ተቀባይነት ያለው ዲጂታል ከረንሲ ለመፍጠር ያደረጉት ጥረት ከንቱ ሆኖ የኖረው አመኔታን ሊያገኙ ስላልቻሉ ነው ይለናል ባርትሌት፤ ቢትኮይን ይሄን ሁሉ አልፎ በሕዝብና ተቋማት ዘንድ ተቀባይነትን እያገኘ የመጣው አመኔታን ያተረፈለትን አሰራር ተግባራዊ በማድረጉ ነው። ቢትኮይን ስራ ላይ ያዋለው ልዩ”የሒሳብ መዝገብ”ወይም የመረጃ ቋት “ብሎክቼይን” ይባላል። አንድ የቢትኮይን ባለቤት ራሱን የቻለ ግን ደግሞ ተመሳሳይ ቅጂዎች በተለያዩ ቦታዎች እንዲኖሩት ያደርጋል።
ቢትኮይን ለሆነ ሰው ባስተላለፍኩ ቁጥር የዚህ ልውውጥ ቅጂ ወደ ሁሉም መዝገቦች ይተላለፋል። ባንክ ይሁን መንግስት ሌላ ማንም አካል ፤ ራሱ የቢትኮይን ፈጣሪ እንኳ ይሄን ዝውውር ሊቀይረውና ለግል ጥቅሙ ሊያውለው አይችልም። ከዚህ ጀርባ ረቂቅ የሒሳብ ቀመር አለ። ለዚህ ነው ቢትኮይን የማይጭበረበረው፤ በመንታፊዎች የማይበረበረው ወይም ተመሳሳይ ቢትኮይን ሁለት ጊዜ መጠቀም የማይቻለው።
ተንቀሳቃሽ ስልክ ያለው ሁሉ ባንኮችን ወይም የሀገሩን ገንዘብ ወደጎን በማድረግ ወይም በማለፍ የባንክ አገልግሎትን ተክቶ ግብይቱን ወይም የገንዘብ ዝውውሩን ከመፈጸሙ ባሻገር ኢንቨስት ያደረገ ደግሞ ጠቀም ያለ ትርፍ ያገኛል። እንግዲህ ዶ/ር ሩጃ ስለክሪፕቶከረንሲ ያላትን ዕውቀት ነው ለማጭበርበርና በአቋራጭ ለመክበር የተጠቀመችበት። የክሪፕቶ ንግስቷ በዌምብሌ አሪና ተገኝታ ዋንኮይንን ካስተዋወቀች ከ4 ወር በኋላ በጥቅምት 2016 ዓ.ም መቀመጫውን በቡልጋሪያ ያደረገው ዋንኮይን ቴክኒካል ኦፊሰር ለመቅጠር በወኪሉ አማካኝነት ማስታወቂያ ያወጣል።
ከቤትና ከመኪና በተጨማሪ በአመት 250ሺህ ፓውንድ የሚያስከፍለው አጓጊ የስራ ማስታወቂያ ማርኳቸው ከአመለከቱት የብሎክቼይኑ ባለሙያ ቢዦርን ዠርኬ ይመረጥና በቀጣሪ ኤጀንሲው ለቃለ_መጠይቅ ይጠራል። ቃለ_መጠይቅ የሚያደርግለትን ሰው ኩባንያው ምን እንድሰራለትና እንዳሳካለት ነው የሚፈልገው ሲል ይጠይቀዋል። ብሎክቼይን ስለሌለው ትሰራለታለህ ሲል ይመልስለታል። ዠርኬ ክው ብሎ ደነገጠ ፤ ጀሮውን ማመን ስላቃተው ፤ ኩባንያው ክሪፕቶከረንሲ አይደለም እንዴ ሲል መልሶ ይጠይቀዋል።
ያለምንም ማቅማማት አዎ ክሪፕቶከረንሲ ነው ይለዋል። ከተመሠረተ የቆየ ቢሆንም ብሎክቼየን ግን የለውም። በሁኔታው ግራ የተጋባው ዠርኬ ለመሆኑ ክሪፕቶከረንሲው ማን ነው ሲል የቀጣሪ የኤጀንሲውን ሰው ይጠይቀዋል። ”ዋንኮይን”ሲል ይመልስለታል። ዠርኬ የዚህን ጊዜ ችግር እንዳለ ስለጠረጠረ ቅጥሩን ተወው። ያለ ብሎክቼይን ክሪፕቶከረንሲ አይታሰብም። መስራቹ በቀላሉ የኢንቨስተሮችን ገንዘብ ለግሉ ጥቅሙ ያውለዋል። በዋንኮይን የሆነው ይሄው ነው። ዠርኬ ስራውን ካለመቀበል ባሻገር ሁኔታውን ለሚዲያ ወይም ለሚመለከተው አካል ቢጠቁም ኖሮ ብዙዎችን ያድን ነበር። ሆኖም ባልታወቀ ምክንያት ይሄን አላደረገም።
የእሷ አልበቃ ብሎ ቤተሰቦቿንና ጓደኞቿን አግባብታ ዋንኮይን ላይ ኢንቨስት እንዲያደርጉ ወትውታና ገፋፍታ ያስበላቻቸው ጄን ማክአዳምስ እንዴት እንደተሸወደች ትናንት የሆነ ያህል በቁጭት ታስታውሰዋለች። በዌቢናር ያገኘችው የዋንኮይን አወያይ ፤”በዚህ ሰዓት ይሄን ዌቢናር የምትመለከቱ እድለኞች ናችሁ። በአጭር ጊዜ ከቢትኮይን የሚበልጠው ዋንኮይን ላይ ኢንቨስት በማድረግ ዳጎስ ያለ ጥቅም ታገኛላችሁ። ” አለ። አወያዩ በመቀጠል ስለ ዋንኮይን መስራች ዶ/ር ሩጃ ማንነት ገለጻ ማድረግ ጀመረ።
“የመጀመሪያና 2ኛ ዲግሪዋን በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ እንደሰራች፤ ፒኤችዲዋን በሀገረ ጀርመን ከሚገኘው ኮንስታንዝ እንደተቀበለች በኩራት ገለጸ። የተጨበጨበላት አማካሪ/ኮንሰልታንት/መሆኗንም አስታወሰ። ታዋቂው ዘ ኢኮኖሚስት መጽሔት ባዘጋጀው አንድ ጉባኤ ያደረገችውን ንግግርም አባሪ አደረገ። ማክአዳም በዶ/ር ሩጃ ስኬት ተደመመች። ሴት በመሆኗ ኮራች። ዋንኮይን ላይ ኢንቨስት ለማድረግ ወሰነች። ወዲያው በ1000 ፓውንድ ዋንኮይን ገዛች። ጠቀም ያለ ትርፍ ለማግኘት ኢንቨስትመንቷን ወደ 10,000 ፓውንድ አሳደገች። ቤተሰቦቿንና ጓደኞችን አግባብታ 250,000 ፓውንድ ኢንቨስት አደረጉ።
ማክአዳም ነጋ ጠባ የዋንኮይንን ድረ ገጽ በጉጉት ትመለከታለች። በጥቂት ቀናት ኢንቨስትመንቷ በአስር እጥፍ አድጎ 100,000 ፓውንድ ደረሰ። ማክአዳም በደስታ ጮቤ ረገጠች። የት ሄዳ እንደምትዝናና ማሰብና ማቀድ ጀመረች። የሸመታ ዕቅድም አወጣች። ትርፏን እያሰላች እንደ ህጻን ፈነደቀች። ዳሩ ግን በአመቱ መገባደጃ አካባቢ ጄን ማክአዳም በበይነ መረብ ራሱን በፈቃዱ ሰውን የሚረዳ ሳምራዊ/good Samaritan/ብሎ ከሚጠራ ሰው ጋር ተዋወቀች።
በሉቃስ ወንጌል(10÷30_37) ላይ ከእየሩሳሌም ወደ እያሪኮ እየሄደ ሳለ ወንበዴዎች ደብድበውና ገፈው ከመንገድ የጣሉትን ሰው አላፊ አግዳሚው እንዳላየ ሲያልፈው ፤ አንድ ሳምራዊ ግን አይቶ ያዝንለታል ቁስሉ ላይ ዘይትና የወይን ጠጅ አፍስሶ ያስርለትና በአህያው ጭኖ ወደ እንግዳ ማረፊያ በመውሰድ ገንዘብ ከፍሎ እስኪያገግም እንክብካቤ እንዲደረግለት አደራ ብሎ ይሄዳል።
ጄን ማክአዳምን ራሱን ጉድ ሰማሪታን ብሎ የተዋወቃት እንደ መጽሐፉ ቅዱሱ ሳምራዊ በገዛ ፈቃዴ ሰዎችን የምረዳ ነኝ ለማለት ነው። በእርግጥ ይሄ ሰው እንደ ሉቃስ ወንጌሉ ሳምራዊ ይሆናል !? አብረን እናያለን። በዋንኮይን ላይ ሰፊ ጥናት ያደረገና ዋንኮይን ላይ ኢንቨስት ያደረጉትን በማነጋገር ላይ መሆኑን ሲገልጽላት ማክአዳም እያመነታች በስካይፕ ለማውራት ፈቃደኝነቷን ትገልጻለች። ሆኖም ውይይታቸው ወደ ክርክርና መጯጯህ ተቀየረ፤ ዳሩ ግን የማክአዳምን ህይወት ወደ አዲስ አቅጣጫ መውሰዱ አልቀረም።
ሳምራዊ ነኝ ብሎ የተዋወቃት ሰው ቲሞቲ ከሪ መሆኑን ነገራት። የክሪፕቶከረንሲ አቀንቃኝና የቢትኮይን አድናቂ እንደሆነ አስረዳት። ሆኖም ዋንኮይን ክሪፕቶከረንሲ እንዳልሆነና አጭበርባሪ መሆኑን አረዳት። ይሄንም ሊያረጋግጥላት እንደሚችል አስረዳት። ማክአዳም ምንድን ነው ማረጋገጫህ ስትል አፋጠጠችው። ከሪ እሺ አረጋግጥልሻለሁ ብሎ መረጃዎችን መላክ ጀመረ። ለተከታታይ ሳምንታት ስለ ክሪፕቶከረንሲ አሰራር የሚያብራሩ ሊንኮችን ፣ መጣጥፎችንና ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ላከላት።
ዋንኮይን ብሎክቼይን እንደሌለው ካረጋገጠው ዠርኬ ጋርም አስተዋወቃት። ማክአዳም ይሄን ሀቅ አምኖ ለመቀበልና በዋንኮይን ላይ ጥያቄ ለማንሳት ሶስት ወር ወስዶባታል። ከሪ እንዳላት ዋንኮይን ብሎክቼይን ከሌለው ችግር አለበት ማለት ነው በማለት መፍራት ጀመረች። የዋንኮይን ቡድን አባላትን ነጋ ጠባ ክሪፕቶከረንሲው ብሎክቼይን አለው ወይስ የለውም እያለች ስትጨቀጭቃቸውና መቆሚያ መቀመጫ ስታሳጣቸው በሚያዚያ 2017 ዓ.ም ዋንኮይን ብሎክቼይን እንደሌለው አረዷት። ማክአዳም ተዝለፍልፋ ወለሉ ላይ ተዘረረች። እነ ማክአዳም ይይዙት ይጨብጡት አጥተው ግራ በተጋቡበት ፤ የክሪፕቶ ንግስት ዋንኮይንን ለማስተዋወቅ አለምን እየዞረች ነው። ከማካው እስከ ዱባይ ፣ ከኳላሉፓር እስከ ሲንጋፓር ፤ ዋንኮይን እድገቱን ቀጥሏል።
ወዲህ ንግስቷ የእነ ማክአዳምን ኢንቨስትመንት እንደ ግል ሀብቷ ትረጨው ይዛለች። በቡልጋሪያ መዲና ሶፊያና በጥቁር ባሕር ሶዞፓል ቅንጡ ሕንጻዎችንና ጀልባ ገዛች። ሲደብራት በቅንጡው ጀልባዋ እንደ ቤቤ ሬክሳ ያሉ የፓፕ ከዋክብትን በመጋበዝ ድል ያለ ፓርቲ ትደግሳለች። ወዲህ ዋንኮይን በገባው ቃል መሠረት ለኢንቨስተሮች ክፍያ መፈጸም አልቻለም። በዚህ የተነሳ በመላው አለም የሚገኙ የዋንኮይን ኢንቬስተሮች ግራ ተጋብተዋል። ገንዘባችንን ማለት ጀምረዋል።
ለእነዚህና ለሌሎች ኢንቨስተሮች ጥያቄ መልስ ለመስጠት በፓርቹጋል ሊዝበን በጥቅምት 2017 ዓ.ም ቀን ተቆጥሯል። ኢንቨስተሮችና የዋንኮይን አስተዋዋቂዎች፤ በቀጠሮ አክባሪነት የማትታማውን ዶ/ር ሩጃን በመጠበቅ በርበሩን ቢያዩም የክሪፕቶ ንግስቷ የውሃ ሽታ ሆነች። አንዴ ሶፊያ ወደ ሚገኘው የዋንኮይን ዋና መስሪያ ቤት ፤ ሌላ ጊዜ እጅ ስልኳ ላይ ቢደውል ፤ መልዕክት ቢላክ መልስ የለም። የበላት ጅብ አልጮህ አለ። ከሊዝበኑ ሁነት ከሁለት ሳምንት በኋላ ማለትም በወርሀ ጥቅምት መገባደጃ ላይ ከሶፊያ ወደ ግሪክ አቴንስ ከበረረች በኋላ አየሁም ሰማሁም ያለ ጠፋ። በኋላ ላይ ሲጣራ ዋንኮይን ሀሰተኛ ክሪፕቶከረንሲ ከመሆኑ ባሻገር ያረጀው ያፈጀው የፒራሚድ ንግድ መሆኑ ተደረሰበት።
በዚህ ማጭበርበር የስንቱ ቤት እንደፈረሰ ፤ የስንቱ ህልም እንደጨነገፈ ቤት ይቁጠረው። ለዚህ ነው “አዲስ ዘመን”ዜጎችን ከዚህ መጭበርበር ለማስጠንቀቅ ተደጋጋሚና ተከታታይ ግንዛቤ ማስጨበጫ ዜናዎችንና መጣጥፎችን እያዘጋጀ ያለው። ነገርን ነገር ያነሳዋል እንዲሉ ጋዜጣው በዚያ ሰሞን ያስነበበንን ምክርና ማስጠንቀቂያ እዚህ ላይ ላስታውስ። ክሪፕቶ ከረንሲ የተሰኘውን ዲጂታል መገበያያ ያላቸው ዜጎች ምናባዊው ገንዘብ ህጋዊ ፍቃድ እስኪያገኝ ድረስ የያዙትን ክሪፕቶ ከረንሲ ወደ ህጋዊ ገንዘብና ዕቃ ቢቀይሩት ይመከራል ሲሉ በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ መምህር ረዳት ፕሮፌሰር ሁሴን ሰይድ ይመክራሉ።
ረዳት ፕሮፌሰር ሁሴን ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ህጋዊ ዕውቅና የሌለውን ክሪፕቶ ከረንሲ ወደ ዶላርና ወደብር እንዲሁም ወደ ዕቃ መቀየር ይኖርባቸዋል። ይህም በቅጽበት ምናባዊው ገንዘብ አሰራሩን ቢቀይር አሊያም አገራት ቢያስቆሙት ከሚደርሰው ኪሳራ እራስን ለመጠበቅ ይረዳል። እንደ አዲስ ቴክኖሎጂ ወደፊት በስፋት ጥቅም ላይ መዋሉ አይቀርም በሚል ተስፋ ብዙዎች ወደዚህ ክሪፕቶ ከረንሲ ግብይት እንደሚገቡ የገለጹት ረዳት ፕሮፌሰር ሁሴን ፤ ይሁንና ገንዘባችንን ስናወጣ በብዙ መልኩ ህጋዊ አካሄዱን ማሰብ ይገባናል ሲሉ ያስጠነቅቃሉ። ክሪፕቶ ከረንሲ ኢትዮጵያ ውስጥ እስካሁን ፍቃድ ያገኘ መገበያያ አይደለም። ይህ ዲጂታል ገንዘብ ጥቅምም እንዳለው ሁሉ አሉታዊ ተጽእኖው ስላለው ህጋዊ ማዕቀፍ ተዘጋጅቶለት እስኪወጣ ድረስ እራስን ከኪሳራ መጠበቅ ያስፈልጋል።
በተለይ አገራት የእራሳቸውን ስምምነት አድርገው እስካልተጠቀሙበት ድረስ በምናባዊው ገንዘብ ተማምኖ ለመቆየት አስቸጋሪ ነው። እንደ ረዳት ፕሮፌሰር ሁሴን ሃሳብ ከሆነ ፤ አንድ አገር የወረቀት ገንዘብ አትሞ ሲያሰራጭ በወርቅ ክምችት ተግባብቶ ነው ገንዘቡን ወደሥራ የሚያስገባው። ክሪፕቶ ከረንሲውን የሚያሰራጭ ሰው ግን ካለምንም ዓለም አቀፍ ስምምነት መገበያያ ብሎ የሚያከፋፍለው እራሱ ያዘጋጃቸውን የኮምፒዩተር ኮዶችን ነው።
ባለቤቱ የኮምፒዩተር ኮዶቹን ለተለያዩ ሰዎች እያከፋፈለ በአንጻሩ ደግሞ ህጋዊ ገንዘቦችን የሚሰበስብበትና ሃብትን በእጁ የሚያስገባበት መንገድ እየሰፋ መሄዱ ደግሞ አይቀርም። አንድ የኮምፒዩተር ባለሙያ ወይም ድርጅት አንድ የክሪፕቶ ከረንሲ መገበያያ ቢፈጥርና ያ ገንዘብ ገበያው ቢገባ ኮዶችን ብቻ እያከፋፈለ በቅጽበት የዓለም ሃብታም የሚሆንበትና በአንድ ጀንበር የዓለምን ኢኮኖሚ የሚቆጣጠርበት ዕድሉ ሰፊ መሆኑን ረዳት ፕሮፌሰሩ ጠቁመዋል።
በተጨማሪ አጨቃጫቂ የሚሆነው ጉዳይ ክሪፕቶ ከረንሲን ማን እንደሚያሰራጨውና ባለቤቱ ማን እንደሆነ እንኳን አይለይም። በመሆኑም ካለው ስጋት አኳያ አንድ ቀን አገራት በሙሉ ምናባዊውን ገንዘብ ሊያቋርጡበት የሚችልበት ዕድል እንዳለ ማሰብ ያስፈልጋል ሲሉ ምክረ ሃሳባቸውን አስቀምጠዋል።
አንድ ድርጅት ቢት ኮይን የተባለ ወይም ሌላ ስም ሰጥቶ ይህንን ምናባዊ ገንዘብ አስተዋውቄያለሁ ስላለ ብቻ ሰዎች ገንዘባቸውንም ንብረታቸውንም ሰጥተው ያንን ምናባዊ ገንዘብ ለማግኘት የሚሯሯጡ ከሆነ እጃቸው ላይ የሚቀራቸው ሃብት እንደማይኖር ሊያስቡ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። ስለዚህ ይህን ምናባዊ የኮምፒዩተር ኮዶች የገዙ ሰዎች በተቻለ መጠን እራሳቸውን ከአደጋ ለመጠበቅ የያዙትን ምናባዊ ገንዘብ ወደህጋዊ ንብረት አሊያም በባንክ መገበያያነት እያገለገሉ ወደሚገኙ ገንዘቦች ቢቀይሩ ሃብታቸውን በቅጽበት ከማጣት ስጋት መላቀቅ ይችላሉ።
እንደ አገርም ይህንን ምናባዊ ገንዘብ ተግባራዊ ለማድረግ ሰፊ ዝግጅት ይጠይቃል ያሉት መምህሩ፤ ብዙ ሕጎችም መውጣት አለባቸው። በተጨማሪም በአገራት መካከል ጭምር ድርድሮችና ማካሄድና ምናባዊው ገንዘብ ላይ ስምምነቶች ማካሄድ ይኖርባቸዋል። ያን ጊዜ በሙሉ ልብ ይህንን ክሪፕቶ ከረንሲ መጠቀም እንደሚቻል ዕምነታቸው መሆኑን ገልጸዋል። ዲጂታል መገበያያ ገንዘብ አለያም ምናባዊ ንብረትን ለግብይት መጠቀም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ዕውቅና ያልተሰጠው ድርጊት በመሆኑ ህብረተሰቡ ከእንደዚህ አይነት ሕገ-ወጥ ተግባር እራሱን እንዲጠብቅ ባንኩ ማሳሰቡ የሚታወስ ነው።
ፈጣሪ ሀገራችንን በቃ ይበላት !
አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@admin
አዲስ ዘመን ታህሳስ 1 ቀን 2015 ዓ.ም