በአለማችን ”ሁሉንም” ከሆኑት አንዱ ስፖርት ነው። በአምስቱ ቀለበቶች ይታጠር እንጂ ስፖርት የማይነካካው ጉዳይ እስከ ዛሬ አልታየም። በመሆኑም የሕዝብ ስለሆነው ስፖርት ሀሳብ መለዋወጥ፣ የሁሉም ይሆናል ማለት ነውና በርእሳችን ዙሪያ እንቀጥል።
እርግጥ ነው፣ ዘመናዊ ሥልጣኔ ካፈራቸው ስፖርቶች አንዱ፤ በ19ኛው ምዕተ አመት መጀመሪያ አካባቢ ወደ አገራችን የገባውና የመጀመሪያውን ውድድር በ1919 ዓ.ም በት/ቤቶች ያደረገው የእግር ኳስ (ቡድናችን) ጉዳይ እማይንጠው ሰው ማግኘት ይከብዳል። ይህ እስከ ዛሬ ድረስ በነበረው የስፖርት ቤተሰቦች ዘንድ ሲታይ የነበረ ሲሆን፣ ዝቅ ብለን እንደ ምናየው ዛሬ ነገር አለሙ ሁሉ ተለዋውጧል።
ምንም ጥያቄ የለም፣ ያለንበት ዘመን ስለስፖርት የሚዘግቡ ሚዲያዎች እንደ አሸን የፈሉበት ነው። በመሆኑም የብዙዎችን ልብና አእምሮ ከመማርክ አልፈው አይንና ጆሮን ቀስፈው ለመያዝ ችለዋል። ግን፣ ግን እየዘገቡ ያሉት ስለስፖርት፣ ኳስ ጥበቡ፣ ቴክኒክና ታክቲኩ ነው? አይደለም።
ስለ እውነት እንነጋገር ከተባለ ስለስፖርት በሚቀርቡት ትረካዎች (በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ) ስለ ተጫዋቾች የሽያጭ ሁኔታ፣ የገዥዎች የመግዛት አቅም፣ የተገዥው የመሸጥ አለመሸጥ እድል ወዘተ እንጂ ስለ ኳስ ጥበብ፣ ሳይንስ፣ ፊዚክስና የመሳሰሉት አይደለም። እግር ኳስንና ተጫዋቾችን ከስነልቦና አኳያ የሚያስተነትን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ይህ ጸሐፊ አላጋጠመውም።
ከላይ እንዳልነው በተደጋጋሚ የሚያጋጥመው ትንፋሾች ሁሉ የሚያጥሩት ስለ ግዥና ሽያጭ፤ ፌደሬሽኖች አካባቢ ስለሚታይ ሽኩቻ እንጂ እግር ኳሱ እንዴት ወደፊት መሄድ እንዳለበት፤ ፕሮግራሞቹ ከማስታወቂያ ጋር ተስማምተው እንዲሄዱ ሲደረጉ እንጂ እግር ኳሱን ታሳቢ ያደረጉ፤ እግር ኳሱ ያለበትን አጠቃላይ ሁኔታ የሚያጠይቁ አይደለም። ያለው ሁኔታ ያው ያለው ሁኔታ ብቻ ነው። በመሆኑም ያሳስባል።
እዚህ ላይ ከስነልቦናም እንበለው ሙያዊ ዲሲፕሊን አኳያ ተጫዋቹ(ቾቹ) የት ጋ ነው ያለው/ሉት? ብለን ስንጠይቅ ለራሳችን የምናገኘው መልስ አስደንጋጭ ነው ፤ አስደንጋጭነቱም የሚጀምረው ”ቤቲንግ ሲፍቅ የተገኘው የቡና ተጫዋች ’ቡና ይሸነፋል’” ብሎ መወራረዱ፤ በዚህም ምክንያት ”ቦርዱ ላይመለስ ያሰናበተው” መሆኑን በፕራይም ዜና ስንሰማ ነው። በዚህ ሁኔታ ስለአለም ዋንጫ ማሰብ ይቻላል? ይህን ማሰብ እራሱ ስለ አለም ዋንጫ ምንነት ካለማወቅ የመነጨ እንጂ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል?።
ይህንን ሁሉ ስንል አቅም ሲጠፋ፣ ውጤት ”ሲሄድ”፣ ባለጋራ የበላይነቱን ሲይዝ … ”ጫማው ይዞኝ … ነው”፤ ”ቁንጣው አጥሮኝ … ነው”፤ ”ገምባሌው ጠቦኝ …”፤ ”ዳኛው ቂሙን በፊሽካው ስር ቋጥሮ …፣ ለባለጋራ ወግኖ… ነው” ወዘተርፈን ሳናካትት መሆኑን አንባቢ ልብ ሊልልን ይገባል።
የመሀል ዳኛውን በማራገቢያ እንጨት ሲያሳድድ (የአዲግራቱን ጨዋታ ያስታውሷል) የታየ ብቸኛ ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ መታዩትን ረስተን አለመሆኑንም ከግምት ውስጥ ያስገባልን ዘንድ፤ እየተካሄደ ስላለው የአለም ዋንጫ ስንል መሆኑን እንዲያውቅልን አደራ እንላለን።
ግራዚያቶ የተባሉና ”የተበሉ” አሰልጣኝ ”የኢትዮጵያ ቡድን ብላ ያልከውን ትቶ ጥብስና ቅቅሉን ሲወርድበት ታየዋለህ” ያሉትም ከግምት የማይገባ እንዳልሆነም እንዲሁ።
ሌላው አስደንጋጭ ”ነገ ለውድድር ወደ ውጭ አገር ሊሄድ የተዘጋጀ ቡድን አባል የሆነ ተጫዋች ማታ ከእጮኛው ጋር ምሽት ቤት ታየ። ’ምነው?’ ሲባል፣ ሽኝት እያደረገችልኝ ነው” የሚለውም ለዘፈንና ግጥሙ አወራረድ ሲባል የተደረደረ አለመሆኑን ያልዘለልነው ለአለም ዋንጫ ለመድረስ መንገዱ ይህ አለመሆኑን ለመጥቀስ በመፈለግ እንጂ ሌላ አይደለምና ”አፉ” እንደምንባል ተስፋ አለን።
”የድሮ ናፋቂዎች” ሲናገሩ እንደሚሰማው መንግስቱ ወርቁ ቀን፣ በልምምድ ወቅት ያሳየውን ድክመትና በአሰልጣኙ የተሰጠውን ምክር ጠዋት አርሞና ልቆ ይገኝ ነበር፤ ”እንዴት?” ሲባል ከተያዘለት መኝታ ቤት ጠፍቶ በመውጣት ለሊቱን ልምምድ በማድረግና ስህተቱን በማረም ጠዋት ብቁ ሆኖ መገኘት በመቻሉ እንደ ሆነ ይነገራል። በመሆኑ መንግሥቱ ወርቁ ያው መንግሥቱ ወርቁን ሆኖ ሊያልፍ ቻለ።
”የድሮ ናፋቂዎች” ሲያማርሩና ሲያዝኑም እንደሚታየው በ1943 (እ.ኤ.አ.) ከተመሰረተው (በ1953 የፊፋ፣ በ1957 የካፍ አባል ከሆነው) እግር ኳስ ፌደሬሽን አካባቢ ”አልፎ አልፎ” የሚሰማው ተኩስ የሚረብሽና ለእግር ኳሱም እንደ በሬ ሽንት ወደ ኋላ መሄድ ምክንያት ነው፤ ከእነ ይድነቃቸው ተሰማ የፀጥታ ዘመን ጋር ሲወዳደር ከደረጃ በታች ነው። የአሁኑ ዘመን የፌደሬሽኑ ባለ ስልጣናት “ደረት የማያስነፋ፤ አንገት የሚያስደፋ ሥራ እንጂ ሌላ የተሰራ ስራ የለም”። ይህ ሌላው ለ138ኛነታችን ምክንያት ነው።
እነዚሁ ”የድሮ ናፋቂዎች” እንደሚሉት የድሮው ብሔራዊ ቡድን በአየር ንብረትና የተለያዩ ምክንያቶች የልምምድ ስፍራ ሲያጣ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመነጋገር ልደት አዳራሽ ውስጥ ልምምድ ያደርግ ነበር። ዛሬ ግን አገር ሙሉ ስታዲየም ለምንም ሳይሆን ምንም ሆኖ እየቀረ ይገኛልና የዛሬም ሆነ የወደፊቱ የአለም ዋንጫ ለኢትዮጵያ፣ የመድረኩ ንጉስ እንዳለው ”ርቆ የተሰቀለ ዳቦ …” እንዳይሆን ያሰጋል።
የድሮዎቹ ተጫዋቾች ምርጥ ምርጥ ጨዋታዎችን በቪዲዮ አስቀርተው እቤታቸው ቁጭ ብለው የሚያዩ ሲሆን፤ ይህ በአሁነኞቹ ዘንድ ”የማይረባ” አስተሳሰብ ሆኖ ነው የሚለውም በቀላሉ ሊዘለል የሚገባው ጉዳይ አይደለም።
እንደ ”የድሮ ናፋቂዎቹ” አባባልም ሆነ ነፃ አስተያየት ተመልካችም እንበለው ቲፎዞ ጋ የከፋ ችግር አለ። ኳስን እሚመለከተው ከኳስ ፍቅር ወይም ጥበብ አንፃር ሳይሆን ከተወራረደበትና አገኛለሁ (አሸንፋለሁ) ብሎ በእቅድ ከያዘው ገንዘብ (ብሄራዊ ባንክ ”መንፈሳዊ ገንዘብ” ይለዋል) አኳያ ነውና ችግሩ የአንድ ወገን ብቻ አይደለም ማለት ነው። ኳስ አደጋ ላይ ነች (ለነገሩ በስፖንሰር አድራጊነት ምክንያት የአንደኛው ስያሜ ”ቤቲኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ” አይደል እንዴ)። ዝርዝሩ ብዙ ነው።
ያለንበት ይዞታ
በ2018 በተደረገ ጥናት የ”አደረጃጀት እና አወቃቀር፣ የተዝረከረከ ልማዳዊ አሰራር … ችግር” እንዳለበት የተረጋገጠው፤ በአሁኑ ሰአት ለአፍሪካ ዋንጫ እየተዘጋጀ ያለው ብሄራዊ እግር ኳሳ ቡድናችን (ሉሲም ሆነ ዋሊያ) በአሁኑ ሰአት ከዓለም 138ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። እንደ ፊፋ ደረጃ አሰጣጥ ከ2019 ጀምሮ ቡድናችን ምንም አይነት መሻሻል ሳያሳይ በዚሁ ደረጃ ላይ ጮቤ እየረገጠ ነው።
እንደ ”የድሮ ናፋቂዎች” ከሆነ፣ በዚሁ ከገፋን የአለም ዋንጫ እንዳማረን የሚቀጥለው ሚሌኒየም እንዳይመጣ ያሰጋል። የሕዝቡም ወሽመጥ መበጠሱም እንደዛው። (በነገራችን ላይ፣ ቡድናችን የመጀመሪያው ኢንተርናሽናል ውድድር የተደረገው ጂቡቲ ከነበረው የፈረንሳዊያን መርከበኞች ቡድን ጋር በ1940 ዓ.ም ነበር፡፡)
የአለም እግር ኳስ ይዞታ
ወቅቱ የዓለም ዋንጫ እየተካሄደ ያለበት ነው። ያልተጠበቁት ሴኔጋልና ሞሮኮ 16 ውስጥ ሲገቡ (ሞሮኮ 8 ውስጥም ገብታለች) እነጀርመን፣ ቤልጂየም (ቡድኑ በመሸነፉ ምክንያት ሕዝባዊ ተቃውሞ ገጥሞታል) … የተሰናበቱበት ሁኔታ ነው ያለው። ይህ የሚያሳየን እግር ኳስ እንኳን ተቀልዶበት እንዲሁም ከባድ ነውና ”የእኛዎቹ ከዚህ ምን ይማሩ ይሆን?” የሚለውን ለማንሳት ያህል ነውና መልካም የዓለም ዋንጫ!!!
በነገራችን ላይ፣ በአሁኑ ሰአት የስፖርቱ ባለቤት ግን ማን ነው? ፌዴሬሽኖች፣ ወይስ …
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን ታህሳስ 1 ቀን 2015 ዓ.ም