በኢትዮጵያ ያሉ ብሔር ፣ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች የሀገር ምሰሶዎች ናቸው። ምሰሶው የቆመው ደግሞ በፍቅርና በአንድነት መንፈስ ነው። በምሰሶው ዙሪያ ሀገሪቱን ደግፈውና አድምቀው የቆሙት ባሕልና ሥርዓቶቻችን፣ ወግና ልማዶቻችን እንደ ማገር ናቸው። እናም ሀገራችን የቆመችው በእኔና በእናንተ ልዩ ልዩ ባሕልና ልማድ ዋልታና ማገርነት ነው ማለት ነው።
ኢትዮጵያን መሐል አድርገን ነው የቆምነው። ምንም ጥርጥር የለውም ኢትዮጵያ የቆመችው ከሰማኒያ በላይ ብሔረሰቦችን ተደግፋ ነው። ያቆማት ፍቅራችን ነው..ያጸናት አንድነታችን ነው። በጋራ ከተጓዝን ብዙ በረከት ከፊታችን አለ። የእኛን አንድነት፣ የእኛን ፍቅር የሚፈልጉ ብዙ ሀገራዊ በረከቶች ከፊታችን እየጠበቁን ነው። የሀገር ምሰሶ እንደሆንን፣ የወገን አለኝታ እንደሆንን እንደተጋመድን ወደ ፊት መቀጠል ይጠበቅብናል።
አንዳንድ ነገሮች ቀላል ናቸው..ማሰብና መመራመር አይጠይቁም። ሀገር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለመረዳት ልዩ እውቀት የሚጠይቅ አይመስለኝም። የትኛውም ሀገር በዜጎቹ ባሕልና ወግ የቆመ ነው። የትኛውም ታሪክ በብሔረሰብ ሥርዓት የተጻፈ ነው። ሀገር ለማቆም መሠረታዊ ከሆኑ ቁም ነገሮች ውስጥ ቀዳሚው የብሔረሰቦች ተፋቅሮና ተቻችሎ መኖር ነው።
ሀገራችን ኢትዮጵያ ደግሞ በዚህ የታደለች ናት። ከጥንት እስከዛሬ ተፋቅሮና ተዋዶ በሚኖር ማኅበረሰብ የተከበበች ናት። እነዩጎዝላቪያ፣ የቀድሞዋ ሶቭየት ኅብረት የፈረሱት እና ታሪክ አልባ የሆኑት በልዩነታቸው ውስጥ መኖር ስላቃታቸው ነው። በተቃራኒው እንደ ኢትዮጵያ ያሉ በብዙ የብሔር ስብጥር ውስጥ የሚኖሩ ሀገራት ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን የአብሮነትና የመቻቻል አንድነትን ገንብተዋል።
ይሄ ዓለም አቀፋዊ ወንድማማችነት የመጣው ከእያንዳንዳችን በተዋጣ ሰላምና አንድነት፣ መቻቻልና አብሮነት ነው። ሀገራችን አንዱን ጥላ አንዱን አንጠልጥላ ተጉዛ አታወቅም። እዚህ የደረስነው በጋራ ነው። የብቻ ታሪክ የለንም። ታሪካችን የጋራ ነው። ታሪካችን ከእያንዳንዳችን የተውጣጣ ነው። ታሪካችን በጋራ አስበን፣ በጋራ የጻፍንው የአብሮነት ታሪክ ነው።
እኔና እናንተ በሀገሪቱ ያሉ ብሔር ፣ብሔረሰቦች ቅይጥ መልኮች ነን። ኢትዮጵያ ውስጥ እየኖረ አንድ ዓይነት ብቻ የሆነ ዜጋ፣ አንድ ዓይነት ብቻ የሆነ ብሔር የለም። ተጋብተን ተዋልደናል። ተዋልደን አንድ ሆነናል። ይሄ ሁሉ ባይሆን እንኳን ኢትዮጵያዊነት ከአንዱ ወደ አንዱ የሚተላለፍ የሰላም ወረርሽኝ ነው።
ኦሮሞ ሆነን አማራነት የተጋባብን፣ አማራ ሆነን ኦሮሞነት የተላለፈብን፣ ጉራጌ ሆነን እንደ ትግራዋይ የሆንን፣ ትግሬ ሆነን እንደ ጉራጌ የቆምን፣ ሲዳማ ሆነን ወላይታነት፣ ወላይታ ሆነን ሲዳማነት የተላበስን፣ ጋሞ ሆነን ሌላውን ብሔር የምንመስል ብዙ ነን። ኢትዮጵያዊነት ቅይጥ ነው።
ኢትዮጵያዊነት ነጠላ ሆኖ አያውቅም..ድርብ ድርብርብ ነው። ራሳችንን ብንመረምር ብዙ ዓይነት መልክ፣ ብዙ ዓይነት ማንነት ሆነን ነው የምናገኘው። በኢትዮጵያ ደግ እጆች ያልታቀፍን፣ በኢትዮጵያ ቅን ልቦች ያልተፈቀርን አንገኝም።
ተጠጋግተንና ተነካክተን እስከኖርን ድረስ፣ በአንድ ሀገርና በአንድ ታሪክ ላይ እስከቆምን ድረስ ሁላችንም አማራም፣ ኦሮሞም፣ ትግሬም ሌላውንም ብሔር ብሔረሰብ ነን። ኢትዮጵያዊ ስንባል ዝም ብሎ አይደለም..በዚህ ሁሉ የብሔር ስብጥር ውስጥ አልፈን ነው።
ሀበሻ ስንባል የይስሙላ አይደለም በዚህ ሁሉ ድብልቅ እውነት ውስጥ ተሻግረን ነው። ማናችሁ ስንባል ኢትዮጵያዊ ነን ምንለው እኮ የክብር ሸማ ባለበሱን ብሔር ፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ተመጻድቀን ነው። ኢትዮጵያዊ ነን የምንለው እኮ የአንድነት ካባ ባጎናጸፉን ወርቆቻችን ተማምነን ነው። በዚህ ሁሉ ውስጥ በቅለን፣ በዚህ ሁሉ ውስጥ ቆመን፣ በዚህ ሁሉ ውስጥ ኢትዮጵያዊ ሆነን ነው ። ከዚህ ውጪ ምናችን ነው የግል? ምናችን ነው ኦሮሞና አማራ፣ ትግሬና ጉራጌ ብቻ ? የብቻ ኢትዮጵያዊነት የለም።
ከዚህ ሁሉ አንድነት ውስጥ፣ ከዚህ ሁሉ ድብልቅልቅ ውስጥ ራስን ማውጣት ፍጹም የማይቻል ነገር ነው። ከዚህ አንድ ዓይነት ፈትል ውስጥ፣ ከዚህ የጋራ ታሪክ ውስጥ የራስን አንድ ታሪክ መዞ ማውጣት ኢትዮጵያዊነትን ማጉደል ነው። ከዛ ሁሉ ብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቅይጥ ታሪክ ውስጥ የራስን አንድ ታሪክ ለመምዘዝ መሞከር ኢትዮጵያን ማፍረስ ነው።
እናንተ፣ እኛ ሁላችን የኢትዮጵያ ድርና ማጎች ነን። የኢትዮጵያ ቀሚስ የተሰፋው በእኔና በእናንተ ባህልና ወግ፣ ልማድና ሥርዓት፣ ቋንቋና ዘዬ ነውና ከዛ ሁሉ ብዙ አይነት መርፌና ክር ውስጥ የራስን ብቻ መፈለግ ኢትዮጵያን ርቃኗን ማስቀረት ነው። ለኩራት ሲሆን የምንለብሰው፣ ለጥላቻ ሲሆን የምናወልቀው ኢትዮጵያዊነት የለም።
ኢትዮጵያዊነት የትም መቼም ለብሰነው የምንዞረው የኩራት፣ የጽናትና የጀግንነት መንፈስ ነው። ዛሬ ላይ እንደ ሀገር ግራ የተጋባነው ይሄን የአንድነት ካባ ሲሞቀን እያወለቅን ሲበርደን መደረባችን ነው። በብርዱም በፀሐዩም፣ በክረምቱም በበጋውም ኢትዮጵያዊነት ሁልጊዜም አንድ ዓይነት ነው። ሲመቸን የምንለው ዜግነት የለም። በችግሯም በደስታዋም ለሀገራችን ታማኝ መሆን አለብን።
ኢትዮጵያዊነት ትርጉም የሚኖረው እንደ አሁኑ ባለው አስቸጋሪ የፈተና ጊዜ ላይ ከጎኗ ስንቆም ነው። በነፈሰበት መንፈስ ሳይሆን ለሀገርና ሕዝብ ሕልውና ሲባል ሰላምን፣ አንድነትን ማስቀደም ነው። በኃይል ሳይሆን በጥበብ፣ በአፈሙዝ ሳይሆን በመልካም አንደበት ተነጋግሮ መግባባት ነው። በልዩነታችን ውስጥ ያለውን ድል፣ ያለውን በረከት ማጣጣም ነው።
እንዳይፈታ ሆኖ የተገመደውን አንድነታችንን እያሰብን፣ እንዳንለያይ ሆኖ የተሳሰረውን ታሪካችንን እያሰብን መጥፎ ነገሮችን መጸየፍ አለብን። ይሄ ሀገራችንን ከጦርነት ወደ ሰላም፣ ከእኔነት ወደ እኛነት፣ ከብሔር ፖለቲካ ወደ ኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ የምንመልስበት ጥበብ ነው። እናትነት መውለድ ብቻ አይደለም..እናትነት ማረጋገጫው የወለደቻቸውን እልፍ ልጆቿን የምትይዝበት መንገድ ነው።
ልጅነት ዜግነት ብቻ አይደለም..ታማኝ እና ግብረ ገብ ልጅ ሆኖ መኖር ነው። ኢትዮጵያ ሀገራችን በእናትነት አትታማም..ልጆቿ ይክዷታል እንጂ እሷ መልካም እናት ናት። በድህነቷ ውስጥ ለሁላችንም የሚሆን ብዙ ነገር አላት።
ስልጣኔ በምንም መልኩ ራስን አያስክድም። በምንም መልኩ ባሕልና ሥርዓትን አይደፍርም። በምንም መልኩ መረንና ራስ ወዳድ አያደርግም። በምንም መልኩ ተነጋግሮ የመስማማትን ጥበብ አይሰውርም። የዘመነ ጭንቅላት ከሥርዓትና ከነውር ወጥቶ አያውቅም። ራሳችንን መፈተሽ ይኖርብናል።
ትልቅ ሀገርና ሕዝብ ይዘን በአንድነት መቆም ያልቻልነው ለምንድነው ብለን ራሳችንን መጠየቅ አለብን። ሰፊ ታሪክ፣ ጥልቅ ባሕል ከቦን በችግሮች አዙሪት ውስጥ ሆነን የምንኖረው ለምንድነው ስንል እንጠይቅ። ለብዙዎቻችን አራዳነት ሥርዓትን መተው፣ ነውር አለማወቅ ወይም ደግሞ ከባሕልና ወግ ያፈነገጡ ድርጊቶችን መከወን ይመስለናል።
ይሄ የዘመናዊነት ባህሪ አይደለም። ይሄ በማኅበረሰባችን “ተረት ከርሞ ጥጃነት” ነው። ስልጣኔ ከትላንት ሌላ መሆን፣ ከአምናው አንድ ርምጃ ፈቀቅ ማለት ነው። ስልጣኔ በግብረገብነት ሀገር ማሻገር፣ ትውልድ መቅረጽ ነው። ዘመናዊነት በሥርዓት ውስጥ መቆም ነው። አሁን ላይ ብዙዎቻችን ስልጣኔ ሳይገባን በከንቱ የምንኖር ነው። መልካም ስብዕናን ሳንላበስ ብሩህ ነገን የምንናፍቅ ነን። ተነጋግረን ሳንግባባ ትልቅ ተስፋ የምንጠብቅ ነን። መልካም ነገሮች ያሉት በመልካም አመለካከት ውስጥ እንደሆነ ገና አልገባንም። እንዲገባን እፈልጋለሁ..በጎ ስብዕናን ተላብሰን በጎ ሀገር መፍጠር ይጠበቅብናል።
መልካም አስተሳሰብን ሳንይዝ የምንሻገረው ወንዝ፣ የምናሳካው ሕልምና ራዕይ የለም። ራሳችንን በስብዕና ሳንገነባ የምንጀምረው ማንኛውም ነገር ጊዜያዊ ነው። ስብዕና የማንነት መስተዋት ነው። ራሳችንን የምናይበትና የምናሳይበት..ነጸብራቃችን ነው። ማን እንደሆንን፣ ከየት ተነስተን ወዴት እንደምንሄድ የምንመራበት አቅጣጫ ጠቋሚ መሣሪያችን ነው።
ተቻችሎ ለመኖር አቻችሎ ያኖረን የአባቶች ሥርዓት ያስፈልገናል። ዛሬ ላይ ሌላ ነን..የአባቶቻችን ፀዐዳ መልክ መልካችን ላይ የለም። የአያት ቅድመ አያቶቻችን መልካም ነፍስ ነፍሳችን ላይ የለም..በፍቅር ያጌጡ የፊተኞቻችን ቅን ልቦች በልቦቻችን ላይ የሉም። ዛሬ ሌላ ነን። በወንድሞቻችን ሞትና መፈናቀል የምንደሰት፣ በኃጢያት የምንስቅ፣ ፈጣሪን በመርሳት የምንኖር እንደዚህ ነን።
ብዙ ነገራችን አባቶቻችንን አይመስልም። እነሱ የሌሎች መደነቂያ ነበሩ ዛሬ እኛ በሌሎች መደነቅ ግብራችን ሆኗል። በሌሎች ሀገራት ባሕልና ወግ እምነትና ሥርዓት ኖረን የእኛ የሆነውን አጥተናል። እኛነታችንን ተነጥቀናል። የአባቶቻችንን የአደራ መልክ አጠይመናል። የሌሎችን ለብሰን፣ በሌሎች አጊጠን የእኛ የሆነውን ድንቅ ባሕል፣ ውብ ተፈጥሮ በርዘናል።
የውጪውን የባዕድ አስተሳሰብ አንድ ሳይቀር ወስደን ብዙዎች የሚፈልጉትን ምርጡን ሀበሻነት ከሌላ መጤ ባህል ጋር ቀይጠነዋል። አሁን እኛ የቱን እንደሆንን አናውቅም። ብዙ ነገራችን ድብልቅ ነው። የራሳችን መልክ ጠፍቶብናል። መሐል ላይ ነን..ገና ራሳችንን ፈልገን አላገኘነውም።
የእውቀት ማነስ በፈጠረብን አደገኛ ተጽዕኖ ከሁሉም ትልቁን ራሳችንን አጥተን የሰዎች ሆነናል። አባቶቻችን እንዲህ አልነበሩም። ሌሎች እየፈለጓቸው፣ ሌሎች እየናፈቋቸው በብዙ መፈለግ ውስጥ ኖረው ያለፉ ነበር። እኛ የነሱ ልጅ ዛሬ ላይ ስልጣኔ መስሎን ሀገር ሸጠን ባሕል በርዘን በሀበሻና በፈረንጅኛ መካከል ላይ ቆመናል።
አውሮፓና እስያ ለአንድ ወር ሄደን አማርኛ የሚጠፋብን። ተወልደን ያደግንበትን ኢትዮጵያዊነት የምንረሳ እንዲህ ነን። ራሳችንንም ሆነን ታሪካችንን ለመታደግ ጊዜው አሁን ነው። የእኛ የሆነውን ወግና ባሕላችንን፣ እምነትና ሥርዓታችንን፣ ቋንቋና ልማዳችንን ትሩፋታችንንም በሚገባ በመጠቀም አንቆ ከያዘን ፈረንጅኛ አስተሳሰብ ጉራማይሌ አስተሳሰብ እንውጣ።
ለአዲሷ ኢትዮጵያ አዲስ ሆነን መብቀል አለብን። የእኛ የሆነውን በመቻቻል የበረታውን የአባቶቻችንን እውነት በመኖር ቀጣይ ዕድላችንን እንወስን ። ያኔ ምናልባት ካሰብነው የስልጣኔ ጥግ እንደርስ ይሆናል። ዓለምም ራሳችንን ሆነን ሲያየን በባሕላችንና በሥርዓታችን ተደንቆ እኛ እነሱን ለመምሰላችን ቀርቶ እነሱ እኛን የሚመስሉበት ጊዜ ይፈጠራል።
ስልጣኔ ያለው ራስን በመሆንና የራስ የሆነን ነገር በማድነቅ ውስጥ ነው። ወደ ኋላ ሄደን የተውነውን፣ የረሳነውን ማንነታችንን ማየትና መረዳት ይኖርብናል። ይህን ማድረግ ከቻልን አንድ ሊያደርገን የሚችል ብዙ ነገር አለን። ብዙ ነገራችን የተዋረሰና የተጋመደ ነው። በዚህ ድብልቅ እውነት ውስጥ የአንድነት ሀሳብ እልፍ ነው። በፍቅር ኢትዮጵያ ወዛችንን እንመልሰው። የመጣንበት፣ የበቀልንበት የአባቶቻችን ማህጸን አብሮ በመብላት የላመ ነው።
ኢትዮጵያን እንደፈለግን አድርገን ልንስላት ብሩሹም ሸራውም እጃችን ላይ ነው። ልብ ልንለው የሚገባ አንድ ነገር ቢኖር ባበላሸናት ሀገራችን ላይ የምንኖረው እኛና ልጆቻችን ናቸውና የዛሬ ድርጊታችን ነገም ይከተለናልና ምርጧን ሀገር ለመሳል ምርጥ ሰዓሊ መሆን ይጠበቅብናል።
በአባቶቻችን ስም እንጠራ። መልካም አባት፣ መልካም ትውልድ አናጺና መሐንዲስም በመሆን ይቺን ሀገር ላቆዩልን ጥበበኛ እጆች፣ ቅን ልቦች፣ አዛኝ ነፍሶች ራሳችንን እናስገዛ። ሀገራችን ጫንቃችን ላይ ናት..በፍቅር ካልሆነ፣ በመቻቻል ካልሆነ፣ ተነጋግሮ በመግባባት ካልሆነ በምንም አናሻግራትም።
በትረ ሙሴ (መልከ ኢትዮጵ)
አዲስ ዘመን ዓርብ ኅዳር 30 ቀን 2015 ዓ.ም