ኢትዮጵያውያን ዥጉርጉሮች ነን፤ በአንድ በኩል የተለያየ ቋንቋን፣ ባህልን ፣ ወግና ሥርዓትን እንዲሁም ሃይማኖትን ይዘን በአንድ ሰንደቅ ዓላማ ስር የምንኖር ሕዝቦች ስንሆን፤ በሌላ በኩል ተቻችለንና ተደጋግፈን ከመኖር ባለፈ በደምና በሥጋ ተጋምደን፣ ስለሀገራችን ጉዳይ እንደ አንድ ሰው እያሰብን የምንኖር ነን።
ስለ ዳር ድንበሯ እና ስለ ክብሯ እንደአስፈላጊነቱ የሕይወት መስዋዕትነት እየከፈልን በአንድ ጉድጓድ የምንቀበር፣ በእንዲህ ዓይነት የጋራ ተጋድሎ ዓለምን ያስደመመ የጋራ ታሪክ ያስመዘገብን ፣ የቀደምት ስልጣኔ ባለቤቶች ፣የሰው ዘር መገኛ እና የተፈጥሮ ጸጋ ባለቤቶች ነን።
የቋንቋ ፣ የብሔር ፣ የባህል ፣ የሃይማኖት ልዩነቶቻችን የአንድነታችን መሠረቶች ናቸው። ልዩነቶቻችን እንደ ጥለት ክር ኅብር ፈጥረው ኅብረ-ብሔራዊ አንድነታችንን የሚያስጌጡልን ውበቶቻችን የሚያደምቁልን ናቸው እንጂ የሚያራርቁን አይደሉም። ኦሮምኛ፣ አማርኛ፣ አፋርኛ፣ ትግርኛ ወላይትኛ ሶማሌኛ፣ ወዘተ ለየብሔረሰቡ የአፍ መፍቻ ቋንቋ ይሁኑ እንጂ የመላው ሕዝብ መገለጫዎችና የኢትዮጵያ ምልክቶች ናቸው።
ይህንን እውነታ የበለጠ ሕይወት ለመሥጠት በሚልም “ኅዳር 29 1987 ዓ.ም የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ሕዝቦች የጋራ መተዳደሪያችን ነው” ያሉትን ሕገ-መንግሥት አጽድቀዋል ። ቀኑንም የብሔር ብሔረሰቦች ቀን በሚል በየዓመቱ ማክበር ከጀመርን ዓመታት ተቆጥረዋል።
ሕገ መንግሥቱን አስመልክቶ የተለያዩ አዎንታዊና አሉታዊ አስተሳሰቦች መስተናገድ ከጀመሩም ያንን ያህል ዓመታት ተቆጥረዋል ። ፌደራል ሥርዓቱ የኢትዮጵያን የአንድነት መንፈስ ያደከመ፤ ሰዎች ስለኢትዮጵያ ማሰብ ትተው ስለዘራቸውና ስለሚኖሩበት አካባቢ ብቻ እንዲያስቡ ያስገደደ ነው ከሚሉት ጀምሮ ፤በሀገሪቱ ለሚገኙ ብሔር ፤ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ማንነት በአደባባይ እውቅና እንዲያገኝ ያስቻለ ነው እስከሚለው ድረስ ያሉ ሀሳቦች እንደየፈርጃቸው የሚስተናገዱበት ነው።
በእርግጥ የፌደራል ሥርዓት መገለጫው ልዩነትን በማስፋት አንድነትን ማቀጨጭ ባሆንም፤ ባለፉት የኢሕአዴግ አገዛዝ ዓመታት ከአንድነት ይልቅ ልዩነት ጎልቶ እንዲታይ የተደረገበት አሠራር እንደነበር መካድ አይቻልም። በኢሕአዴግ አገዛዝ ዘመን ፌደራሊዝም የተተገበረበት መንገድ ሰዎችን ጫፍ የረገጠ የዘረኝነት መንፈስ እንዲላበሱ ያደረገ በመሆኑ ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ ለተፈጠረው ግጭት ትልቅ ምክንያት ነው ብለው የሚከራከሩ ሰዎች አሉ። ያም ብቻ ሳይሆን ሕገ- መንግሥቱን ለምን በዓይናችን አየነው የሚሉ በርካቶች ናቸው።
የአተገባበር ስህተት ካልሆነ በስተቀር ፌደራሊዝም በመሠረቱ ሰዎችን የሚለያይ ሳይሆን ለማንነት እውቅና የሚሰጥና የሚያከብር ሁሉም የሀገሪቱ ብሔር ብሔረሰቦች በኢኮኖሚያዊ፣ በፖለቲካዊና በማኅበራዊ ጉዳዮች እኩል ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ሥርዓት የሚያሰፍን ነው።
የአንድ ሀገር ሰዎች አንድነታቸው የሚጠናከረው፤ ወንድማማችነታቸው እያበበ የሚሄደው፤ ሀገራቸውን በሙሉ ልብ የሚወዱትና የሚያከብሩት የጋራ ተጠቃሚነታቸውን ሲያረጋግጡ እንደሆነ ግልጽ ነው። የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ሀገራት የተሻለ ነው ብለው ጥቅም ላይ ከሚያውሉት የመንግሥት አስተዳደር አንዱ ፌዴራሊዝም ነው። በአግባቡ መተግበሩ እንደተጠበቀ ሆኖ ማለት ነው።
ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ብሔር ብሔረሰቦች የሚናገሯቸውን ከሰማኒያ በላይ ቋንቋዎች ትተው በአንድ ቋንቋ ቢናገሩ፤ አንድ ወጥ የሆነ ባህል ብቻ ቢኖራቸው፤ በአንድ የሃይማኖት ጥላስር እንዲገቡ ቢገደዱ ዝጉርጉርነታቸው ይጠፋል፤ ውበታቸው ይደበዝዛል፤ የፍቅር ምሳሌ ፤ የቱሪስት መስህብ፤ የሀብት ምንጭ መሆናቸው ይቀራል።
የአንድነት ትርጉሙ ከሰዎች ጋር ኅብረት መፍጠርና በጋራ መኖር ነው። በጋራ ለመኖር ደግሞ የጋራ እሴቶችን ማክበር ያስፈልጋል ። ስለዚህ ለራሳችን የምንሰጠውን ክብር ለሌሎችም መስጠት ስንችል አንድነታችን ይጠናከራል። እርስ በእርስ መደጋገፍ ፤ መመካከር ፤ መቀራረብ ፤ መረዳዳት ፤ መዋደድ የሚኖረው አንዱ ለአንዱ የሚገባውን እውቅና ሲሰጠው ነው። ያ ካልሆነ እንደ ጠላትነት መተያየትና መገፋፋት መራራቅና መናናቅ ይመጣል። ምክንያቱም የማንነት ጥያቄ ነውና።
ሰው በተፈጥሮው እራሱን አይጠላም። እራሱን የማይጠላ ሰው ደግሞ ልክ እንደ እርሱ ሌሎችም ለራሳቸው ቦታ እንደሚሰጡ ተረድቶ መብታቸውን ማክበር ይኖርበታል። በተለይ ደግሞ የመኖር መብት በቋንቋ የማናገር መብት ሕገ-መንግሥታዊ ብቻ ሳይሆኑ ተፈጥሯዊም መሆናቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል። እዚህ ጋር ስለቋንቋ አፈጣጠር ሀሳባውያን እና ቁስ አካላውያን የሚያቀርቡትን ሀሳብ ማስታወስ የሚያስፈልግ ይመስለኛል።
ሀሳባውያን ቋንቋን ለሰው ልጅ የሰጠው ፈጣሪ ነው ብለው ያምናሉ። በእነርሱ አረዳድ እያንዳንዱ ቋንቋ ፈጣሪ ለሰው እንዲግባባበት ብሎ የሠጠው የተፈጥሮ ጸጋ ነው ማለት ነው። ስለዚህ ቋንቋዎች በሌሎች ቋንቋዎች እንዳይዋጡ ማድረግና ማሳደግ የፈጣሪን ስጦታ ማክበር ነው ብለን እንድናስብ ያደርገናል።
እንደቁስ አካላውያን አረዳድም ቋንቋ በሰው ልጆች ማኅበራዊ እንቅስቃሴ የተፈጠረ የሥራ ውጤት ነው። ሰዎች በተለያዩ ቦታዎች በማኅበር መሥራት ፤መኖር ሲጀምሩ ለመግባባት በሚያደርጉት ጥረት ምክንያት ቋንቋዎች ተፈጥረዋል ይላሉ። ከዚህ አንጻር ካየነውም ቋንቋ የዕደ ጥበብ ውጤቶቻችን ከሆኑትና እንደዓይናችን ብሌን ከምንሳሳላቸው ቅርሶቻችን የበለጠ እንጂ ያነሰ ዋጋ ሊሰጠው አይገባም ማለት ነው። ቅርሶቻችን ያለፈውን ዘመን ማንነታችንን የሚገልጹ እንደሆኑ ሁሉ ቋንቋንም እንደ ቅርስ ካየነው የብሔረሰቡን ሁለንተናዊ ገጽታ የሚገልጽ ስለሆነ ለንጠብቀው የሚገባ ሀብታችን ነው።
ኢትዮጵያ የሁሉም ብሔረሰብ ውክልና ያላት የቋንቋ፣ የብሔር ፣ የሃይማኖት እኩልት የሰፈነባት ሀገር ስትሆን አንድነቷ ይረጋገጣል። ባህላቸውን እና ቋንቋቸውን ጨፍልቀው አንድ ለመሆን በሚጥሩ ሕዝቦች አንድ ዓይነትነት እንጂ አንድነት አይረጋገጥም። በመሆኑም ሀገራችን አሁን ያላትን ዥጉርጉር መልክ ትታ አንድ ዓይነት ትሁን ማለት በርካታ ጥያቄዎችን የሚያስነሳና ጭራሽ አንድነትን የሚያሳጣ ቀውስ የሚፈጥር ነው። ስለዚህ ልዩነትን ማክበር በሕዝቦች መካከል ያለውን ችግር የሚፈታ እንጂ የሚባባስ አይደለም።
ነገር ግን በአንዲት ሀገር ላይ የፌደራል ሥርዓትን ማስፈን ሲያስፈልግ መጀመሪያ ሕልውናዋ የተረጋገጠና ጥያቄዎችን በአግባቡ የመመለስ አቅም ያላትን ሀገር መገንባት ያስፈልጋል። ለዚህም አካባቢያዊ አስተሳሰብ ላይ ከተቸነከረ አመለካከት መውጣት ያስፈልጋል። የፌደራሊዝም አስተዳደር ፍልስፍናው በብሔርና በቋንቋ ላይ ተንጠልጥሎ በመቅረት ብሔር ብሔረሰቦችን አቅፋ የያዘችውን ትልቋን ሀገር መርሳት ሳይሆን የጋራ ተጠቃሚነትን እያረጋገጡ በሀገር ጉዳይ በጋራና በአንድነት መቆም ነው።
ሜላት ኢያሱ
አዲስ ዘመን ዓርብ ኅዳር 30 ቀን 2015 ዓ.ም