የሰሞኑ የዓለማችን የአየር ግለት በከፍተኛ ሁኔታ የጨመረ ይመስላል። የግለቱ ምክንያት ደግሞ አንድም የተፈጥሮ መራቆትና ጉስቁልና መንስዔ ስለሆነ ነው፤ ሁለትም በምድራችን ላይ እየናኘ ያለው የዓለም ሕዝቦች የሰሞኑ የጋለ ትንፋሽም የፕላኔታችን ሕዋ እንደ እሳተ ጎሞራ እንዲንቀለቀል ሰበብ ሳይሆን አልቀረም። ዝርዝሩን በምዕራፍ ከፋፍለን ከተመለከትን በኋላ ወደ ዋናው ሀገራዊ ትኩረታችን ተመልሰን የምንለውን እንላለን።
ምዕራፍ አንድ፤
የምድራችን የተፈጥሮ እርቃን መጋለጥ እያስከተለብን ያለውን ከፍተኛ ቀውስ በተመለከተ በየደቂቃውና በየሴኮንዱ ልዩነት ሰማየ ሰማያት ላይ መጥቀውና ተንጠልጥለው በቴክኖሎጂ ዐይናቸው የእናት ምድርን ሥርና መሠረት እየበረበሩ የምድራችንን የአየር ንብረት ፈጣን ለውጥ በተመለከተ መረጃውን የሚልኩልን ሰው ሠራሽ ሳተላይቶች በትጋት እየሰሩ ስለሆነ ብዙም ችግር የለብንም። መረጃዎቹን እየተቀበሉ ለዐይንና ለጆሯችን የሚያቀብሉን ዓለም አቀፍ የሚዲያ ተቋማትም ተግባራቸውን በአግባቡ እየተወጡና “እየመገቡን” ስለሆነ በእነርሱም ላይ ጥያቄ አናነሳም።
በአትተኬዋ ዓለማችን የአየር ንብረት ግለትና ጥፋት ላይ “ለመመካከር” በሚል ሰበብ በየሀገሩ ቅንጡ መዝናኛዎችና የስብሰባ አዳራሾች ውስጥ ሲጠቃቀሱና ሲተማሙ የሚውሉት የስብሰባ ሱሰኞቹ የምድራችን መሪዎች ምክክራቸው ለልማት ሳይሆን ለጥፋት እስኪመስል ድረስ እነሆ ዘመን ጠብቶ ሊመሽ ዳር ዳር እያለ ነው። በቅንጡዋ የግብጽ ሻርም ኤል ሼክ የመዝናኛ “ገነት” ውስጥ ሲካሄድ የሰነበተው የበቀደሙ 27ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ጉባዔ (ኮፕ- 27) ከይምሰል ንስሐ በዘለለ በመርሐ ግብር የተከፋፈል ምን ውሳኔ እንደተላለፈና የአተገባበሩ ዝርዝር ምን እንደሆነ እንኳን ለዓለም ሕዝቦች በሚገባ ተብራርቶ የተገለጸ አልመሰለንም።
በጣም ጎልቶ ሲደመጥ የነበረው የመሪዎች ተረብ፣ የእርስ በእርስ ሽሙጥና አንዱ የሀገር መሪ በሌላኛው መሪ ላይ ሲያሳብብና እርስ በእርስ መካሰሳቸውን ግን በግልጽና በይፋ አድምጠናል፤ ተመልክተናልም። ለምሳሌ፡-የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን “ሳይንስ ስለ አየር ንብረት የሚያውቅ አይመስለኝም” በማለት ተናገሩ የተባለው፤ “ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም” በሚለው ሀገራዊ ብሂላችን ትዝብታችንንና ስጋታችንን መግለጻችን አልቀረም። ሳይንሱ ካልታመነ ማንን እንመን? ይህንን አጠቃላይ ሃሳብ ጫን ያልንበት ምክንያት ከዛሬው ርዕሰ ጉዳያችን ጋር በቀጥታ ስለሚጎዳኝ ሳይሆን ከነካካነው አይቀር ዳስሰነው ማለፉ ክፋት የለውም ብለን በማሰብ ነው።
ምዕራፍ ሁለት፤
ሰሞኑን የዓለማችንን የአየር ንብረት ያጋለው ሌላኛው ምክንያት በኳታር እየተካሄደ ያለው 22ኛው የዓለም እግር ኳስ ዋንጫ ፍልሚያ ነው። ስለ ውድድሮቹ ግለትና ቅዝቃዜ፣ ስለ ተጫዋቾቹ ብርታትና ጥንካሬ እና “ዋንጫውን ማን ያነሳል?” ስለሚለው ትንቢታዊ ብያኔ ይህ ጸሐፊ ሙያውም ሆኖ ውሎው ስለማይፈቅድለት ለመነካካት የሚሞክረው ገራገሩንና የተምሳሌታዊ ትምህርቱን ፋይዳ ብቻ ይሆናል።
በመላው የዓለም ክፍሎች ጨዋታዎቹ በየሚዲያዎቹ ሲተላለፉ ኳስ ወዳድ ተመልካች ዜጎች ጎል ሲገባና ጎል ሲሳት ወይንም ለራስ ቡድን የሚሰጠው የአድናቆት ጩኸት ለፕላኔታችን የአየር ንብረት ሙቀት መጨመር ቢያንስ ቅንጣት ያህል አስተዋፅዖ ሳያደርግ የሚቀር አይመስለንም። አይመስለንም መባሉን ልብ ይሏል። በአይመስለንም ሃሳብን መሰንዘር ከሳይንሳዊ ጥናት ጋር እንደማያኳርፍ ተስፋ እናደርጋለን። ቀደም ሲል ያማናቸው የዓለም መሪዎች እንዲህ መሰሉን በግለት የታጀበ የእግር ኳስ አድናቂዎች ጩኸት ለዓለማችን የሙቀት መጨመር አስተዋፅዖ ይኖረው አይኑረው ተወያይተውበት ስለመሆኑ እርግጠኞች አይደለንም። ሳይንቲስቶቻችን ቢያጠኑት ግን የሚከፋ አይመስለንም።
በዚህ የዓለም ዋንጫ ፍልሚያ ላይ ተደጋግሞ ባስገረመ አንድ ክስተት ላይ ብቻ ትኩረት እናድርግ። ቡድኖቹ በሚያደርጓቸው ተጋድሎዎች ላይ ጎል አግብተውና አሸንፈው ጨዋታዎቹ ሲጠናቀቁ በጎል ብልጫ ያሸነፈው ተሸንፏል ሲባል፤ የተሸነፈው ቡድን ደግሞ ቀደም ሲል በሰበሰበው የጎል ወይንም የነጥብ ልዩነት ማሸነፉ ሲገለጽ ብዙዎችን ግራ እንዳጋባ ይታወሳል።
በተለይም “ጸሐፊውን ለመሰሉ የዋህ” የእግረ መንገድ የእግር ኳስ ተመልካቾች ጉዳዩ ግር ማሰኘቱ አልቀረም። ቁጭ ብድግ እያስደረገ ያሸነፈው ቡድን የመጨረሻው ፊሽካ ሲነፋ ማልቀስ፣ ጎሉ ተደፍሮበት ተደጋግሞ ግብ የተቆጠረበት ቡድንም እንዲሁ መጨረሻ ላይ አሸናፊ ሆኖ ሲጨበጨብለት ተደጋግሞ ተስተውሏል። የአሸናፊ ሽንፈት፤ የተሸናፊ አሸናፊነት ገኖ የተደመጠበት መሰል የዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ውድድር ከአሁን ቀደም እንዳሁኑ በርከት ብሎ ተስተውሎ ከሆነ የሚያውቁ ቢያሳውቁን ለትምህርት ይሆነናል።
ምዕራፍ ሦስት፤
የኳታሩ ዓለም አቀፍ የኳስ ሜዳ ክስተት ከሀገራዊና ነባራዊ ጉዳዮቻችን ጋር በስሱም ቢሆን የሚቀራረብ ስለመሰለን አንዳንድ እንቆቅልሾቻችንን እያነሳሳን እንደተለመደው በእህህታ እንቆዝም። ከመቼውም ዘመን ይልቅ ዛሬ ግፈኛ የደም ጥማተኞች በሚፈጽሙት የጭካኔ ተግባራት የሀገራችን አየር በጩኸትና በእግዚኦታ የተጋጋለበት ደረጃ ላይ የደረሰ ይመስለናል። በኋለኛው ታሪኩም ሆነ በዛሬው የግፍ ድርጊቱ ታሪኩ በዜሮ የሚባዛውና በንጹሐን ደም የጨቀየው “ሸኔ ይሉት” የአሸባሪዎች ቡድን በሀገሪቱ በርካታ አካባቢዎች እየፈጸመ ያለው የንጹሐን ዜጎች ጭፍጨፋ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻችንን “ኤሎሄ! ኤሎሄ!” እያሰኘ ወደ ጸባዖት በማስቃተት በእምባቸው ግለት አየራችን ሊከብድ ግድ ሆኗል። ደመናችንም በደመኞች ደም ዳምኗል።
“ሸኔ” የአሸናፊነት ስሜት እየተሰማው የሚፈጽማቸው ግድያዎችና የንብረት ውድመቶች የተሸናፊነቱ ማረጋገጫ ካልሆነ በስተቀር በአንዳንድ አለሁህ ባዮች እየተጨበጨበለት ቢሆንም፤ ለአሸናፊነቱ ውጤት ማረጋገጫ ሊሆን ግን ከቶውንም አይችልም። በተለይም በመንግሥት ኃላፊነት ላይ ተቀምጠው ይህንን እኩይ ቡድን በደጀንነት “ልክ እንደ ኳስ ሜዳ ትርዒት” በለሆሳስና ድምጻቸውን ከፍ አድርገው የሚረዱትና የሚደግፉት፤ ሲበረታም “ግፋ በለው” እያሉ ከኋላው የሚዘፍኑለትና የሚያቅራሩለት አንዳንድ ኃይላት ከገዳዮቹ እኩል እጃቸው በደም እየጨቀየ መሆኑ የሚጠፋቸው አይመስለንም።
ሞት ረክሶባቸዋል ከሚባሉት ሀገራት መካከል ምናልባትም የእኛን ያህል እምባ እየፈሰሰባቸው ያሉ ሌሎች ሀገራት ስለመኖራቸው እርግጠኛ ለመሆን ያዳግታል። “ሰው እየገደሉ ጭፈራና የፎሌ ረገዳ” የአሸናፊነት ስሜት የሚንጸባረቅበት ሳይሆን የሙት ኅሊና ቀብር ማሳወቂያና የተሸናፊነት የመጨረሻ ማሳረጊያ ጭምር ነው።
በተለይም በወለጋ ውስጥና በአንዳንድ የሀገራችን አካባቢዎች “ሸኔ” በሚሰኘው አሸባሪ ቡድን እየተፈጸሙ ያሉት የግፍ ድርጊቶች ዛሬ እንደ ዋዛ የእብሪተኞች የጀብድ ድርጊትና የጀግንነት ውሎ መገለጫ ተደርጎ ቢቆጠርም ውሎ አድሮ ግን በምድራዊው ሕግ ብቻ ሳይሆን በሰማያዊ ፈራጅ ፊትም ለዘለዓለሙ የሲዖል ኑሮ የሚዳርግ መሆኑ አልገባቸውም፤ ወይንም በትዕቢት ሞራ የተደፈነው ልባቸው ይህንን እውነታ እንዳያስታውሱ አዚም ጥሎባቸዋል። ንጹሐንን በመግደልና ንብረት በማውደም ድል አይገኝም፣ አያስጨበጭብም፣ “ሃሌ ሉያ!” አያሰኘም አያዘምርም።
አንድ ጥያቄ መዘን እንወያይበት? የሸኔ እብሪተኞች እንደፈለጉ ሲፋንኑ ሃይ! እያሉ የሚገስጹና የሚቀጡ የክልል ሹማምንት፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት መሪዎች፣ አባ ገዳዎችና ሀደ ስንቄዎች እንዴት አስችሏቸው ዝም ሊሉ ቻሉ? በአካባቢውስ ጭርሱኑ የሉም ማለት ነው? ለመሆኑ “በሕያውነቴ እምላለሁ ይላል ልዑል እግዚአብሔር… እነሆ ነፍስ ሁሉ የእኔ ናት፤ የአባት ነፍስ የእኔ እንደሆነች ሁሉ የልጅም ነፍስ የእኔ ናት። ግፍን የምትፈጽም ነፍስ እርሷ ትሞታለች። … የሰውን ደም በከንቱ የሚያፈስ ሁሉ ደሙ በከንቱ እንደሚፈስስ” የቅዱስ መጻሕፍት መምህራን አላስተማሯቸውም?
“የወንድምህ ደም ከምድር ወደ እኔ ይጮኻል። ስለዚህም የተረገምህ ነው። የወንድምህን ደም ከእጅህ ለመቀበል አፏን ከከፈተችው መሬት ተሰደህ ተቅበዝባዥ ትሆናለህ። ብታርሳትም ፍሬዋን አትለግስህም። በምድር ላይ ኮብላይና ተንከራታች ትሆናለህ” የሚለው የሕያው አምላክ ፍርድ ተፈጻሚ እንደሚሆንስ አልገባቸውም ይሆን?
ይህ ሀገራዊ እንቆቅልሻችን ጊዜ ይፍጅ እንጂ ምላሹ በዝርዝርና በግላጭ ፍች ማግኘቱ አይቀርም። ዛሬ በኢትዮጵያ ምድር የፖለቲካ ውድድሩን መቋቋም የተሳናቸው “የከንቱ ከንቱ” የሚሰኙ ቡድኖች እዚህም እዚያም ደም እያፈሰሱ ጀብደኛነታቸውን ለመግለጽ እድል ያገኙ ይምሰል እንጂ ውሎ አድሮ በሕዝብና በፀሐይ ፊት ለፍርድ ቀርበው የእጃቸውን እንደሚያገኙ አንጠራጠርም።
የኢትዮጵያን ደመናና የአየር ንብረት እያጋለ ያለው በሸኔ ቡድን የሚፈጸመው ግፍና እልቂት ብቻም አይደለም። ይህንን የግፍ ድርጊት እንደ ጀግንነት ቆጥረው በየማኅበራዊ ሚዲያው ሳይቀር የሚፎክሩና የሚያስፎክሩት የጥፋት ልጆች ድርጊትም ከገዳዮቹ የሚለይ አይደለም።
ለራሳቸው ክብር የሌላቸው የክፋት ኃይላት ደም በማፍሰስ ንጹሐንን ጭዳ በማድረግ የሕዝብ ተቆርቋሪ ነን ብለው ማምታታታቸው ለጊዜው ካልሆነ በስተቀር ውሎ አድሮ እውነታው መገለጡ አይቀርም። ማንነታቸው በድርጊታቸው እየተረጋገጠ ይፋ መሆን ሲጀምርም እኔን ብቻ ካላያችሁኝና ካልሰማችሁኝ በማለት እንዳልፋነኑ ሁሉ ምድር አፏን ከፍታ እንድትውጣቸው መመኘታቸው የሚቀር አይሆንም።
የኢትዮጵያ ፖለቲካ የአየር ንብረት ለጊዜው ግለት የጨመረ ይመስላል። ሙሰኞችን የማጋለጥ ሂደቱ ብዙዎችን አርበድብዶ ትኩሳቱን አግሎታል። የሸኔ ቡድን ግባ መሬት ሊፈጸም ጫፍ ላይ መድረሱ ያሳሰባቸው አንዳንድ “የበግ ቆዳ የደረቡ ተኩላ” የመንግሥት ሹመኞች ሰላም እንዳይሰፍን በሕዝቡ ውስጥ ሠርገው በመግባት የማሸበር ተልዕኳቸውን እየተወጡ መሆኑ እየተደመጠ ነው። “የመንግሥት ያለህ!” የሚሉ ኡኡታዎችም ሰማያዊውን ሰማይ አጥቁረውታል።
“የሕወሓት መጨረሻ ምን ሊሆን ይችላል? መንግሥትና ቡድኑ የገቧቸው ግዴታዎች አተገባበርስ እንደምን ለፍሬ ይበቃል?” ወዘተ. የሚሉ ጥያቄዎችና ጉምጉምታዎችም በስፋት አየራችንን ተቆጣጥረው ሙቀቱን አጋግለውታል።
የወቅታዊው የሀገራችን ምህዳር እውነታው ይህንን ይመሰል እንጂ ኢትዮጵያ ከሁሉም ተግዳሮቶቿ አሸናፊ ሆና መውጣቷ ግን ይዘገይ ካልሆነ በስተቀር በፍጹም የሚቀር አይደለም። ይህቺ ታላቅ ሀገር ተፋልማ ማሸነፍንም ታውቅበታለች፣ ተሳልማ ፈጣሪዋን መለመንንም በሚገባ ተለማምዳለች። ስለዚህም ነው ስታሸንፍ ቀረርቶ አብዝታ የማትፎክረው፤ የተሸነፈች ለሚመስላቸውም ከማስተባበያ ተቆጥባ አሸናፊነቷን በተግባር የምታረጋግጠው። ይኸው ነው። ሰ ላም ይሁን።
አዲስ ዘመን ህዳር 29 ቀን 2015 ዓ.ም