ይህ ዘመን የቴክኖሎጂ እንደመሆኑ ዘመኑን የሚዋጅ ቴክኖሎጂን መጠቀምን የግድ ይላል። ዘመኑን የሚመጥን ቴክኖሎጂ መረጃን በመለዋወጥ ሥራን በቀላሉና በተቀላጠፈ መንገድ ማከናወን፣ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ፣ ሉዓላዊነትን ማስጠበቅ. ወዘተ ከማስቻሉም በላይ ለተወዳዳሪነት ወሳኙ መሣሪያ ነው። ቴክኖሎጂው የሚያመጣቸውን እድሎችና መልካም አጋጣሚዎችን መጠቀም ለአንድ ሀገር እድገት ወሳኝ መሆኑም ይታመናል።
ከቴክኖሎጂዎቹ መካከል አንዱ የበይነ መረብ/ኢንተርኔት/ ቴክኖሎጂ ነው፤ ዓለም አንድ መንደር መሆን ለቻለችበት ምክንያት አንዱ ምስጢርም ይሄው የበይነ መረብ ቴክኖሎጂ ነው። ያደጉትን ሀገሮች እድገት እያፋጠኑ ከሚገኙት መካከል አንዱ ይሄው ቴክኖሎጂ ሆኗል። ሌሎች በማደግና ላይ ያሉ ያላደጉ ሀገሮችም ይህን ቴክኖሎጂ በስፋት ለመጠቀም እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ። እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ታዳጊ ሀገራት ልማትን በማፋጠን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች ተርታ ለመሰለፍ የሚያደርጉትን ጥረት ለማሳካት በፍጥነት ቴክኖሎጂውን በመቀላቀል በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፍ የራሳቸውን እድገት ማፋጠን ይጠበቅባቸዋል።
በተለይ ዓለምን በእጅጉ እያስተሳሰረ ያለውን የበይነ መረብ (ኢንተርኔት) ቴክኖሎጂን በመጠቀም ልማትን፣ የንግድ እንቅስቃሴዎችን፣ ማኅበራዊ ጉዳዮችንና የሀገር ገጽታ ግንባታን በማቀላጠፍና ውጤታማ ማድረግ ለሀገር እድገት የላቀ አስተዋፅዖ ያበረክታል።
ኢትዮጵያም ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሰነቀችውን ራዕይ እውን የማድረግ ሩጫዋን ለሚያፋጥንላት ለሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ትኩረት ሰጥታ እየሠራች ትገኛለች። መንግሥት የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው የአስር ዓመት መሪ እቅድ የኢኮኖሚው አምስት ምሰሶዎች ብሎ ከያዛቸው መካከልም ይሄው የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ አንዱ ተደርጓል። ሀገሪቱ በሀገር ደረጃ ዲጂታል ኢኮኖሚን መገንባት የሚያስችል እንዲሁም የቴክኖሎጂ ምህዳሩን ሊያፋጥን የሚያስችል የሕግና የአሠራር ማዕቀፎችን በመዘርጋት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂንም እየተገበረች ትገኛለች።
የዲጂታል ዘርፉ በሀገራችን እያደገ መምጣቱ፣ የተለያዩ የዲጂታል ሥርዓቶች እየተገነቡ መሆናቸው፣ የዘርፉን ደህንነት ለማስጠበቅ ደግሞ በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ ያሉበት ሁኔታም ይህንኑ ያመለክታሉ። በተለይ መንግሥት ለተቋማት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ወደ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለመቀየር በርካታ ሥራዎችን እያከናወነ ስለመሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ።
ሀገሪቱ ባለፈው ሳምንት ላስተናገደችው ዓለም አቀፉ የበይነ መረብ /ኢንተርኔት/ አስተዳደር ጉባኤ እንድትመረጥ ካስቻሏት ምክንያቶች መካከል ይሄው በዘርፉ እያካሄደች የምትገኘው ተግባር ነው። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ ዓሊም ይህንኑ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በሳይንስና ቴክኖሎጂው ዘርፍ እያሳየች ያለችው ቁርጠኝነትና ለውጥ 17ኛውን ዓለም አቀፍ የበይነ መረብ አስተዳደር ጉባኤ እንድታዘጋጅ ለመመረጥ አብቅቷታል ሲሉ ሚኒስትሯ አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ ይህን ታላቅ መድረክ ነው እንግዲህ ባለፈው ሳምንት ለቀናት አካሂዳ በስኬት ያጠናቀቀችው። ኢትዮጵያ ይህንን ዕድል ልታገኝ የቻለችው በቴክኖሎጂ እያሳየች ያለችው እድገት እና የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ፀድቆ ወደ ሥራ መግባቱ፣ የቴሌኮም ዘርፉን በዓለም ተወዳዳሪ እንዲሆን ክፍት ማድረጓ፤ ይህም ለቴክኖሎጂ እድገት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑ ታምኖበት ነው።
ጉባኤው ታላቅ መድረክ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። ጉባኤው በዓለም አቀፍ ደረጃ ከአስራ ስድስት ዓመት በፊት እ.ኤ.አ በ2005 ነው የተጀመረው። ባለቤት የሌለውን በይነ መረብ ለማስተዳደር ሀሳብ ለማፍለቅ የሚያስችል በየዓመቱ በአዘጋጅነት በተመረጡ ሀገራት የሚካሄድ ሲሆን፣ የበይነ መረብ አስተዳደር ጉባኤ የበይነ መረብ ተጠቃሚነትን ተከትሎ የሚመጡ መልካም እድሎችና ተግዳሮቶችን በተመለከተ ተወያይቶ ምላሽ የሚሰጥ አካል ያስፈልገዋል በሚል ስምምነት እ.ኤ.አ በ2006 የመጀመሪያው ጉባኤም በግሪክ አቴንስ ተካሂዷል። የዚህ ጉባኤ ዓላማ በዚህ ዘርፍ የተሠማሩ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ስለበይነ መረብ አስተዳደር ያሉ መልካም አጋጣሚዎች እና እድሎች እንዲሁም ፈተናዎችን በተመለከተ ሀሳብ የሚያንሸራሽሩበት እና የጋራ ግንዛቤ የሚፈጠሩበት ነው።
ይህ ጉባኤ አስገዳጅ ውሳኔዎች የሚወሰኑበት አይደለም፤ ውሳኔ አመንጪና ሰጪ የሆኑት የግሉን ዘርፍና መንግሥትን በጉዳዮቹ ላይ የመረጃና የፖሊሲ መነሻ ሀሳብ በመስጠት ጉዳዮች በሕግና በሌሎች ማዕቀፎች የሚፈቱበት አግባብ የሚመላከትበት ነው።
17ኛው ዓለም አቀፍ የበይነ መረብ ጉባኤም በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስተባባሪነት ከኅዳር 19 ጀምሮ እስከ 23 ቀን 2015 ዓ.ም ለአምስት ተከታታይ ቀናት በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የጉባኤ አዳራሽ ተካሂዷል። በጉባኤው የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ተጠባባቂ ዋና ጸሐፊ አንቴኒዮ ፔድሮ ፣ የግል ማኅበራትን ጨምሮ ከሦስት ሺ በላይ ተሳታፊዎችና የዘርፉ ምሑራን ተገኝተዋል። በጉባኤው ላይም የኢትዮጵያና የአፍሪካ የኢንተርኔት ተጠቃሚነትን የተመለከቱ ጉዳዮች ጎላ ብለው ቀርበዋል።
በጉባኤው ላይ በይነ መረብ ለዓለም፣ ለአፍሪካና ለሀገሮች ቁልፍ ጉዳይ መሆኑ የተጠቀሰ ሲሆን፣ ይህ ቁልፍ የልማት፣ የደህንነት፣ ወዘተ መሣሪያ ተደራሽ አለመሆኑ እንዲሁም በአስተዳደር በኩል በሚታዩ ክፍተቶች ለተለያዩ ችግሮች እየተጋለጠ ያለበት ሁኔታ ሰፊ መነጋገሪያ አጀንዳ ሆነዋል። አካታችነትና የበይነ መረብ ደህንነት መወያያ ሆነዋል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በጉባኤው ላይ በዙም ባስተላለፉት መልዕክት በዓለም አቀፍ ደረጃ በበይነ መረብ ተደራሽነት ላይ በስፋት መሥራት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፤ አስተማማኝና አካታች የዲጂታል ደህንነት አንደሚያስፈልግም ነው ያስገነዘቡት።
ዋና ጸሐፊው፤ በዓለም 2 ነጥብ 7 ቢሊዮን ሕዝብ አሁንም ድረስ ከኢንተርኔት መገናኘት እንዳልቻለ ጠቅሰው፣ ከእዚህም ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የምትይዘው አፍሪካ መሆኗን አመልክተዋል። ‹‹እንደ አውሮፓ ባሉ አህጉራት ከ89 በመቶ በላይ ሕዝባቸውን የኢንተርኔት ተጠቃሚ አድርገዋል›› ያሉት ዋና ጸሐፊው፣ ‹‹ይህንን ስናስተውል አፍሪካና የአፍሪካ ሕዝቦች ወደኋላ የመውደቅ አደጋ ላይ ናቸው ማለት ነው›› ሲሉ ብለዋል።
እንደ ዋና ፀሐፊው ገለጻ፤ ለአፍሪካ ዘላቂ እድገት ኢንተርኔት ጉልህ ሚና ይጫወታል ። ስለዚህ ለአፍሪካ የወደፊት ዲጂታል ጉዞ እውን መሆን ከጉባኤው ብዙ ይጠበቃል።
በርግጥ ኢትዮጵያን ጨምሮ በርካታ የአፍሪካ አገራት ዲጂታል ቴክኖሎጂ የመጣው እድል ለመጠቀም እየሠሩ ናቸው። ዜጎቻቸውን በቴክኖሎጂ አካታች ለማድረግ ጥረቶች ያደርጋሉ። ኢንተርኔት ለዜጎች ለማዳረስ ጥረት ያደርጋሉ። ያም ሆኖ ግን በአፍሪካ ኢንተርኔት የሚጠቀመው ከሦስት ሰው አንዱ ነው። ይህ ማለት ወደ 871 ሚሊዮን ዜጎች ከበይነ መረብ ግንኙነት ውጭ ናቸው ማለት ነው። ይህም አስተማማኝ የበይነ መረብ ዝርጋታን በዓለም ላይ ለማዳረስ ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባ ያመለክታል። ይህን ሕዝብ ተጠቃሚ ማድረግ የቤት ሥራ ሊሆን ይገባል።
ደህንነቱ የተረጋገጠ፣ የበይነ መረብ ግንኙነት ለሁሉም እንደሚያስፈልግ ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አስገንዝበዋል። አስተማማኝ የበይነ መረብ ዝርጋታን በዓለም ላይ ለማዳረስ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባ አመልክተው፤ በተለይ ለአፍሪካ አስተማማኝና አካታች የዲጂታል ደህንነት መተግበር እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል። ሦስት ቢሊዮን የዓለም ሕዝብን የቴክኖሎጂው ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።
ሁሉን አቀፍ አህጉራዊ ብልጽግናንና ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በትብብር መሥራት እንደሚገባም ነው ዋና ጸሐፊው ያመለከቱት። ሁሉን አቀፍ ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን ለማሳካት መረባረብ እንደሚገባ አስታውቀዋል።
የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ጉዳዮች ምክትል ዋና ጸሐፊ ሊ ጁንሁዋ እንደገለጹት፤ ቀጣይነት ያለውና አስተማማኝ የበይነ መረብ ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ኢንቨስትመንትን፣ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን በማሳደግ ትስስር ሊፈጥር ይገባል። በተለይም እንደ አፍሪካ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት በዘርፉ በትኩረት መሥራት ይኖርባቸዋል።
የበይነ መረብ ተደራሽነትን ለማስፋት ዘርፉ በፖሊሲ መደገፍ አለበት ያሉት ሊ ጁንሁዋ ፣ መንግሥታት ለዘርፉ የሚሰጡት ትኩረት፣ ዘርፉን በረጅም ጊዜ ኢንቨስትመንት መደገፍና የዲጂታል ዘርፉ ክህሎትን ማሳደግ የበይነ መረብ ተደራሽነትን ለማስፋት ወሳኝ ጉዳዮች በመሆናቸው ትኩረት ሊደረግባቸው እንደሚገባ ገልጸዋል።
የዲጂታል አብዮት እየተጀመረ ያለባት አፍሪካ ግልጽና አካታች ስትራቴጂን በመንደፍ ልትሠራ እንደሚገባትም አስገንዝበዋል። መንግሥታት ለዘርፉ የሚሰጡት ትኩረት፣ ዘርፉን በረጅም ጊዜ ኢንቨስትመንት መደገፍና የዲጂታል ዘርፉ ክህሎትን ማሳደግ የበይነ መረብ ተደራሽነትን ለማስፋት ወሳኝ ጉዳዮች መሆናቸውን አንስተዋል፡፡
በመድረኩ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የበይነ መረብ ተደራሽነትን በማስፋፋትና የሳይበር ደህንነትን በማስጠበቅ ረገድ በርካታ ሥራዎችን እየሠራች ትገኛለች። በዚህ ሂደት ላይም ዘርፉ ለብልጽግና ጉዞዋ የሚፈጥርላትን መልካም ዕድል እንደ አዳጊ ሀገር እውቅና ትሰጣለች።
ኢትዮጵያ በዲጂታል ቴክኖሎጂና ኢንፎርሜሽን ዘርፍ ፈጣን ለውጥ እያመጣች መሆኑን ጠቅሰው፤ የበይነ መረብ አገልግሎት የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተያዘውን የአሥር ዓመት እቅድ ተግባራዊ ለማድረግ የሚኖረውን ፋይዳም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስታውቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2017 የነበረው 19 ሚሊዮን የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር በ2022 ወደ 30 ሚሊዮን ከፍ ብሏል፤ የ4ጂ ኔትወርክ ሕዝብ በሚበዛባቸው ከተሞች እና 5ጂ ኔትወርክን በትላልቅ ከተሞች መዘርጋቱ ግንኙነቱን እያፋጠነ ይገኛል። በመላ ሀገሪቱ 2 ሺህ300 ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የኢንተርኔት አገልግሎት አላቸው።
‹‹በዘመነ ዲጂታል የበይነ መረብ ጠቀሜታ ዘርፈ ብዙ ነው›› ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህም በትራንስፖርት፣ በግብርና እንዲሁም በጤና እድገት ላይ ዘርፉ ያለውን አወንታዊ ድጋፍም አመላክተዋል። ኢትዮጵያ በኮቪድና በሌሎች ሰው ሠራሽ ችግሮች በተፈተነችበት ወቅት ሥራን በበይነመረብ ማካሄድ መቻሏን አዳዲስ ፈጠራዎች እንዲበረታቱ ማድረጉንም በመልካም ጎኑ አንስተውታል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩም አፍሪካ ደህንነቱ የተጠበቀ የበይነመረብ አስተዳደር ሊኖራት ይገባል ሲሉ አስገንዝበዋል። የበይነ መረብ አስተዳደር በጠንካራ ፖሊሲ መደገፍ እንደሚገባውም ነው የጠቆሙት። ያለፉት አራት ዓመታት ለኢትዮጵያ የፈተናም የዕድልም ዓመታት ነበሩ ሲሉ ጠቅሰዋል። በይነ መረብ በርካታ በጎ ነገሮች ቢኖሩትም የተዛባ የመረጃ ስርጭትን በማስፋፋት ረገድም አሉታዊ አስተዋፅኦ አለው ብለዋል። ዘርፉ የተሳሳቱ መረጃዎችን በማሰራጨት ሀገሪቷን ሲጎዳ መክረሙንም በአብነት ጠቅሰዋል።
ከሁለት ዓመት በፊት ኢትዮጵያ ወደ አካታች ዲጂታል ኢኮኖሚ በምታደርገው ጉዞ አንድ ወጥ የሆነ ራዕይ ያስቀመጠ ብሔራዊ ዲጂታል ስትራቴጂ በሥራ ላይ ማዋሏን የጠቆሙት ዶክተር ዐቢይ፣ ስትራቴጂው መሠረተ ልማትን ማጎልበት፣ ሥርዓቶችን ማስቻል፣ ዲጂታል መድረኮችን እና የዲጂታል ሥነ-ምሕዳርን በመገንባት ላይ ያተኩራል ብለዋል።
ለዚህም ደህንነትን እና ተጠያቂነትን ለማስፈን በሚደረገው ጥረት መንግሥት ብሔራዊ የሳይበር ደህንነት ተቋማትን ለማጠናከር የተለያዩ እርምጃዎችን ወስዷል። እነዚህ ተቋማት የአገሪቱን የሳይበር ምሕዳር ከመጠበቅ በተጨማሪ በተዛማጅ ጉዳዮች ላይ የዜጎችን ግንዛቤ የማሳደግ ሥራ በመሥራት ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡
በጉባኤው መጠናቀቂያ ላይ የተገኙት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በጉባኤው የተነሱ ነጥቦች በበይነ መረብ አስተዳደር የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር የሚያስችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በበይነ መረብ አጠቃቀም ዙሪያ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት ዓለም አቀፍ የበይነ መረብ አስተዳደር ሊኖር እንደሚገባም ጉባኤው ማመላከቱን ጠቅሰዋል። የተነሱት ሀሳቦች ለሁሉም ሀገሮች ጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ሁሪያ ዓሊ በጉባኤው ከ170 በላይ አገሮች መሳተፋቸውን ጠቅሰው፣ በተለይም ያልተቆራረጠ የኢንተርኔት ተደራሽነት እንዲኖር በርካታ ሀሳቦች መንሸራሸራቸውን ገልጸዋል። ከ2ነጥብ 7 ቢሊዮን በላይ ከኢንተርኔት ውጭ የሆነውን ሕዝብ ተጠቃሚ ለማድረግ መሥራት እንደሚገባ የቤት ሥራ የተሰጠበት ነው ሲሉ አስገንዝበዋል።
የኢንተርኔት አባት በመባል የሚታወቁት ቬንት ሰርፍ ኢትዮጵያ ጉባኤውን በሚገባ ማስተናገዷን አስታውቀዋል፡፡በመድረኩ የተገኙት ሀሳቦች በኢንተርኔት አስተዳደርና አጠቃቀም ላይ ለሚሠሩ ሥራዎች ትልቅ ግብዓት የተገኘበት ሲሉም ጉባኤውን ገልጸውታል።
ወርቅነሽ ደምሰው
አዲስ ዘመን ኅዳር 27/ 2015 ዓ.ም