የዓለም ዋንጫ ዛሬ በኳታር ዋና መዲና ዶሀ ይጀመራል። ለቀጣይ አንድ ወርም የዓለም አይኖች ወደ መካከለኛው ምስራቋ አገር ይዞራሉ። የዓለም መገናኛ ብዙሃንም ዋና ትኩረታቸውን ወደዚያ ይሆናል። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሀንም እንደዚያው። ስለ ኢትዮጵያ የስፖርት ሚዲያ ስናወራ ደግሞ በምንም መልኩ ሊዘነጋ የማይችለው ሰው ታላቁ ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ ነው። እኛም የዓለም ዋንጫውን አስታከን ይህን ታላቅ ጋዜጠኛ ልንዘክረው ወደድን።
ደምሴ ዳምጤ የተወለደው በ1945 ዓ.ም ሲሆን እድገቱም በምስራቃዊቷ ሞቃታማ ከተማ ድሬዳዋ ነው። ብዙዎች እንደሚናገሩለት ደምሴ ገና ከልጅነቱ ለስፖርት የተሰጠ ነበር። ነገር ግን ለስፖርት ተወዳዳሪነት ሳይሆን ለስፖርት ዘገባ። አፍላው ደምሴ ተሰጥኦውን ፈልጎ ለማግኘት ጊዜ አላባከነም ነበር። የስፖርት ዘጋቢነት ሙያውን የመረጠው ገና በልጅነቱ ነው። በድሬዳዋ ከተማ አሸዋማ ስፍራዎች ላይ ይደረጉ የነበሩ የታዳጊ ህጻናትና የወጣቶች የእግር ኳስ ግጥሚያዎች ደምሴ ወደ ስፖርት ዘጋቢነት ሙያ እንዲገባ ትልቅ ሚና ነበራቸው። ደምሴ የኳስ ፍቅር ነበረው። የኳስ ፍቅሩን በንቁ ተመልካችነት፣ በታዛቢነትና በደጋፊነት ከመግለጽ ባለፈ በተጨዋችነት ታቅፎ የተሳተፈበት የእግር ኳስ ቡድን አልነበረም። የእርሱ ትኩረትና ሕልም መጫወት ላይ አልነበረም፤ መዘገብ ላይ እንጂ።
ተዘራ እሸቴ የተባሉ የደምሴ የቅርብ ወዳጅ ስለደምሴ በጻፉት ጸሑፍ ደምሴ ወደ አማተር የጋዜጠኝነት ስራ የገባበትን አጋጣሚ እንዲህ ይገልጹታል፡-
‹‹ … በወቅቱ የነበሩት የድሬዳዋ ስፖርት ኮሚቴ አባላት የስራና የቤተሰብ ኃላፊነት ጫና የነበረባቸው ሰዎች ነበሩ። በዚህም የተነሳ የስፖርት ዘገባውን አጠናቅሮ ለዜና የማብቃት ድክመት ጎልቶ ይታይባቸው ነበር። በዚህ ክፍተት ነበር ደምሴ የሕይወት ጥሪውን ለማሳካት ብቅ ያለው። ሕልሙን እውን ለማድረግ የነጻ አገልግሎት ለመስጠት ራሱን አቀረበ። አዎንታዊ ምላሽም አገኘ። በሙያው መደበኛ ስልጠና ሳይኖረው ትምህርቱንና የስፖርት ዘጋቢነቱን አጣምሮ ያዘ። በእርሱ የእድሜ ክልል የነበሩት እኩዮቹ ባልሄዱበት ጎዳና ጉዞውን ቀጠለ። ነፃ የስልክ አገልግሎትና ነፃ የስታዲየም መግቢያ ካርድ ተሰጥቶት አገልግሎት መስጠት ጀመረ። በጥረቱም ስኬታማ ሆነ … የድሬዳዋ ስፖርት አፍቃሪዎችንም ቀልብ መግዛት ቻለ። ደምሴን በየመንገዱ እየጠራ አድናቆቱን የሚቸረው የድሬዳዋ ስፖርት አፍቃሪም በረከተ። ስሙ ገነነ። ወደፊት ጎልቶ የሚወጣ የጋዜጠኝነት ሙያ ችሎታ እንዳለውና ለሙያውም የተሰጠ መሆኑንም አሳየ። በጊዜውም ‹‹አማተር ጋዜጠኛ›› ተባለ። በዚህ ወቅት ያጎለበተው ልምድና እውቅና ለኋለኛው የጋዜጠኝነት ዘመኑ የማዕዘን ድንጋይ ሆኖለት አለፈ …›› ብለዋል።
በወቅቱ የደምሴ ዘገባ በእግር ኳስ ተመልካቹ ዘንድ ተወዳጅነትን ቢያተርፍለትም በተጫዋቾች እና አሰልጣኞች ዘንድ ግን አልተወደደለትም ነበር። ምክንያቱም ደምሴ ጨዋታውን ምስል ከሳች ለማድረግ የሚጠቀማቸው ቃላት የተጫዋቾችን ድክመት የሚያሳዩ ስለነበሩ ነው። አጥቂው በረኛውን እንዴት እንዳለፈው ሲናገር አጥቂው ቢደሰትም በረኛው ግን ያኮርፍ ነበር። እንዲህ እንዲህ እያለ በደምሴ ዘገባ በበጎ ያልተነሱ ተጫዋቾች ደምሴን ያኮርፉትና መንገድ ላይ ሲያገኙትም ይተናኮሉት ነበር። ከሁሉም በላይ ግን ዘገባው በድሬደዋው ተመልካች እና አዲስ አበባ ባሉ አንጋፋ ጋዜጠኞች አይን ውስጥ ከተተው።
ደምሴ አማተርነትን ተሻግሮ ዋና/መደበኛ/ ጋዜጠኛ የሆነበት አጋጣሚ ከ10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጋር የተያያዘ ነው። ወቅቱ ኢትዮጵያ 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫን የምታስተናግድበት ጊዜ ነበር። ጋዜጠኛ ሰለሞን ተሰማና ባልደረባው ይንበርበሩ ምትኬ የተወሰኑትን ጨዋታዎች ተከታትለው ለመዘገብ ከአዲስ አበባ ድሬዳዋ ገብተዋል። የአጋጣሚ ነገር ሆነና ደምሴ ከባድ ትኩሳት የተቀላቀለበት ጉንፋን ያመውና ሲጠብቀው ከነበረው ታላቅ ጨዋታ ቀርቶ ቤት ውስጥ ይውላል። ቀልቡን ከሰረቁት እውቅ ጋዜጠኞች ጋርም ሳይታደም ይቀራል። ሰለሞንና ይንበርበሩም ከጨዋታው ፍጻሜ በኋላ የሙያ ባልደረባቸውን ለመጠየቅ አድራሻውን ያጠያይቃሉ። የደምሴንና የተዘራን ቅርበት ከሚያውቁ ሰዎች በተደረገ ጥቆማ ተዘራ እንደሚፈለግ ከስታዲየሙ የድምጽ ማጉያ ሰማ። የደምሴ ጉዳይ እንደሆነ ፈጥኖ የተረዳው ወዳጁ ተዘራ በተባለው ቦታ ፈጥኖ ተገኘ። ከዚያም በቀረበላቸው መኪና ተያይዘው ወደ ደምሴ መኖሪያ ቤት (ወደ ታላቅ እህቱ ቤት) አመሩ። ታላቅ እህቱ ከባለቤቷና ከሦስት ልጆቿ እንዲሁም ከደምሴ ጋር የሚኖሩባት አንዲት ክፍል ቤት ሲደርሱም ሰለሞንና ይንበርበሩ ባዩት ነገር እጅግ ተገረሙ፤ ተደናገጡ። ሰለሞን ‹‹ … እንደዚህ አልጠበኩም ነበር …›› ሲል ይንበርበሩም ፊቱን አቀጭሞ የእርሱም ስሜት ተመሳሳይ መሆኑን ገለፀ። ደምሴ ለብዙ ጊዜያት በነፃ ሲያገለግል የቆየው በአስቸጋሪ ህይወት ውስጥ ሆኖ እንደነበር እነ ሰለሞን ተረዱ።
ወደ መኪናቸው ሲመለሱም ደምሴ የሚኖረው ከማን ጋር እንደሆነ ተዘራን ጠየቁት። ተዘራም ከታላቅ እህቱ ቤተሰብ ጋር እንደሆነ ተናገረ። ደምሴ ራሱን ከሱስ ጠብቆ ከአባቱ ከምትደረግለት ድጎማ ላይ ቆጥቦ፤ አለባበሱን አሳምሮ መታየቱ ጥሩ ገቢ ያላቸው ቤተሰቦች ልጅ እንደሆነ ሳያስጠረጥረው አልቀረም።
እነ ሰለሞንም ባዩት ሁኔታ ውስጣቸው ተረብሾና ግምታቸው ከእውነታው ጋር ተጋጭቶባቸው ወደ አዲስ አበባ ተመለሱ። በዚያን ሰሞን አንድ የስፖርት ጋዜጠኛ ከአገር ወጥቶ አልተመለሰም ነበር። እነ ሰለሞንም አዲስ አበባ እንደተመለሱ የደምሴን ጉዳይ ቅድሚያ ሰጥተው ያዙት። በወቅቱ የነበሩት የስራ ኃላፊም ከአገር ወጥቶ ባልተመለሰው ጋዜጠኛ ቦታ ሌላ አማተር ጋዜጠኛ ለመቅጠር ዝግጅት አጠናቀው ጨርሰዋል። በዚህ ጊዜ ነበር እነኚህ ተደማጭነት የነበራቸው እውቅ ጋዜጠኞች ደምሴ ለዓመታት በነፃ ሲያገለግል በአስቸጋሪ ህይወት ውስጥ ሆኖ እንደነበር አለቃቸውን አስረድተው ያሳመኑትና ሀሳቡንም እንዲቀለብስ የተማፀኑት።
እነ ሰለሞንም ደምሴ በአስቸኳይ ወደ አዲስ አበባ እንዲመጣ ነገሩት። ደምሴም በፍጥነት ወደ አዲስ አበባ ሄደ፤ ከአማተር ጋዜጠኛነት ወደ መደበኛ/ዋና/ ጋዜጠኛነት ተሸጋገረ። ጋዜጠኝነትም ሙያው ሆነ። በርቀት ሲያደንቃቸው ከነበሩት ጋዜጠኞች ጋርም በቅርብ ሆኖ ደመወዝ ተከፍሎት ለመስራት በቃ። እነ ሰለሞንም ፈለጋቸውን ሲከተል የነበረውን ደምሴን እጁን ይዘው ከደረሱበት አደረሱት። ደምሴም በሙያውም አንቱ ተባለበት። ከኢትዮጵያ ሕዝብ በተለይም ከስፖርት አፍቃሪው የኅብረተሰብ ክፍልም አድናቆትንና ተወዳጅነትን አተረፈበት።
በደምሴ የጋዜጠኝነት ታሪክ ተጠቃሹ ቀን ታህሳስ 17 ቀን 1980 ዓ.ም ነው። እለቱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከዙምባቡዌ አቻው ጋር በምስራቅ እና መካከለኛው አፍሪካ ዋንጫ ፍፃሜ የሚጫወትበት ቀን ነበር። ከአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታውን ቀጥታ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ደምሴ ዳምጤ ሲያስተላልፍ የተጠቀማቸው ቃላት አይረሴ ናቸው። በተለይ የዙምባቡዌ ብሔራዊ ቡድን 1ለ0 እየመራ ሳለ ያደረጋቸው ገለጻዎች ደምሴ ለአገሩ እና ለእግር ኳስ ያለው ፍቅር ፍንትው ብሎ የታየበት ነበር። እስኪ ከዚያ ዘገባ የተወሰነውን እናስታውስ..
“… አማኑኤል አሁን … አማኑኤል ለሙሉዓለም … ሙሉዓለም ለመንግሥቱ ሁሴን … መንግሥቱ ሁሴን ለአማኑኤል … አሻማ … ሙሉዓለም አሁን አሻማ … አሻ … አሻማ … ሙሉዓለም አሻማ … በጭንቅላት ወይኔ … ወይኔ … ወይኔ ገብሬ … ገብሬ የመታውን … የዙምባቡዌው 2 ቁጥር… በራሱ ግብ ላይ … በራሱ ግብ ላይ ከመረብ አሳረፈ … በራሱ ግብ ላይ ከመረብ አሳረፈ … ፤ … አሁን 1ለ1 ካለቀ ሠላሳ ደቂቃ ይጨመራል፤ ሰዓቱ አልቆ ነበር”
በተጨማሪው 30 ደቂቃ የውጤት ለውጥ ባለመኖሩ አሸናፊውን ለመለየት ሁለቱ ቡድኖች ወደመለያ ምት አመሩ። ደምሴ ዳምጤ ሲቃ እየተናነቀው አስራ ሁለቱን መለያ ምቶች እንዲህ እያለ ማስተላለፍ ቀጠለ፦
፩. “… ሰባት ቁጥሩ ነው የሚመታው … የታወቀው የክንፍ አጥቂያቸው …. አሁን ሰባት ቁጥሩ ሄዷል … ተካበ ቦታውን ይዟል … ሰባት ቁጥሩ ኳሷን አስቀምጦ የዳኛ ውሳኔ በመጠበቅ ላይ ነው … ምታ ብለውታል … መታ … ተካበ አዳነ …ተካበ የመጀመሪያውን አድኗል …
ተካበ የመጀመሪያውን አድኗል … ግሩም ነው! ተካበ የመጀመሪያውን አድኗል … ግን ቁርጡ በዚህ አይታወቅም … ገና … ነው”
“ነጋሽ አስቀምጧል … ነጋሽ ሊመታ ነው … ነጋሽ መታ … ቀረቀባት … ቀረቀባት ነጋሽ … ግሩም ግብ … ጠረቀማት … ገብቷል የእኛ … ጠረቀመው … ጥሩ ምት ነው! የመታው ነጋሽ ጠረቀመው … አሁን ተመትቶ እስካላለቀ ቁርጡ አይታወቅም።”
፪. “…የሚመታው 15 ቁጥሩ ነው … ሁለተኛው ነው ለዙምባቡዌ … መታ … ተካበ አዳነ … ተካበ አሁንም አዳነ … ጉድ ነው … ጉድ ነው … ጉድ ነው፤ ተካበ አሁንም አዳነ … የሚገርም ነው፤ ሜዳው ተደበላለቀ…”
“… አሁን አማኑኤል ሊመታ ነው … አማኑኤል ሊመታ ነው … አማኑኤል … ሰጠሰጠው … ሰጠሰጠው … ሰጠሰጠው … ምን ዓይነት ግብ ነው … ምን ዓይነት ግብ ነው … ምን ዓይነት ግብ ነው … አሁን 2ለ0 እየመራን ነው …”
፫. “… ዙምባቡዌ አሁን ሦስተኛውን ሊመታ ነው … 14 ቁጥሩ ሊመታ ነው … ጉድ ነው … መታ … ገባ”
“… ገብረመድህን ሊመታ ነው … ምታ አሉት … መታ … ወይኔ … ወይኔ … ወይኔ … ግሩም ግብ ገብሬ..”
፬. 10 ቁጥሩ ሊመታ ነው … 10 ቁጥሩ ሊመታ ነው አሁን … መታ … ኸረ … አስገባ …ምቱ ይቀጥላል”
“…አሁን በቀለ ካገባ ያልቃል … በቀለ ካገባ … በቀለ ካገባ ያልቃል … ካገባ … ምታ አሉት … በቄ መታ … ወይኔ ውጪ ሰደዳት … ተነቃንቋል ግብ ጠባቂው … ተነቃንቋል … ተነቃንቋል አሉ ግብ ጠባቂው … ሊደገም ነው … ውጪ ወጥቶ ነበር … ግብ ጠባቂው መነቃነቁ በጀን እንጂ … “
“አይዞህ በቄ … በቄ አሁን ሊመታ ነው … መታ … ውይ … መለሳት ግብ ጠባቂው … መለሳት … መለሳት … መለሳት … መለሳት …”
፭. “8 አሁን ሊመታ ነው … ምታ አሉት … አልመታም … መታ … ገባ … ገባ …”
“…አሁን መንግሥቱ ሁሴን ሊመታ ነው … መንጌ አሁን ገላግለን … መንጌ መታ … መታ … ወይኔ ወይኔ … ግብ ጠባቂው መለሰ …”
፮. “…3 ቁጥሩ ሊመታ ነው … 3 ቁጥሩ ሊመታ ነው … ውጪ … ውጪ … ውጪ … ውጪ … (ደምሴ እንዲህ ይበል እንጂ ተጫዋቹ ገና አልመታም) … ውጪ … ውጪ ሰደዳት …”
“… አሁን ዳኛቸው ነው የሚመታው … ዳኙ ሊመታ ነው … ሰው ዝም ቢል ይሻላል ይጨነቃል … አሁን ግብ ጠባቂው ቦታውን … ቦታውን … አሁን ይገላግለናል … ካገባ ትገላገላለች … አሁን ዳኙ ሊመታ ነው … በዙምባብዌ ላይ … ዳኙ … ወይኔ ወይኔ … ጨፈረ ደነሰበት … ደንሶ አገባ ዳኙ … ደንሶ አገባ … በጣም አስደናቂ ግብ ነው ዳኙ …
… ዳኙ አሁን ደንሶ ጨፍሮ አገባ … አታለለው ቀኙን አሳይቶ ግራውን … ግራውን አሳይቶ በቀኙ … አሁን ተጫዋቾቻችን ደስታቸውን እየገለፁ ነው … ወደሜዳ ህዝቡ ገባ … በጣም የሚያስደንቅ ነው አሁን … ዳኙ … ተመልካቹ እንደተመኘኋት አገኘኋት ይላል …”
ከ40 ዓመታት በላይ ያለድካም በቅንነትና በትጋት ያገለገለው አንጋፋው ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ፣ ባደረበት ሕመም ምክንያት ሕክምናውን በአገር ውስጥና በውጭ አገር ሲከታተል ቆይቶ በ60 ዓመቱ፣ ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም. አርፏል። ሥርዓተ ቀብሩም ወዳጅ ዘመዶቹ፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለስልጣናት፣ የስፖርት ቤተሰቦችና አድናቂዎቹ በተገኙበት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ተፈጽሟል። ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ ባለትዳርና የሦስት ልጆች አባት ነበር።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ኅዳር 11/ 2015 ዓ.ም