የሰላም ድምጽ ከሰማን እነሆ አንድ ሳምንት አለፈን ! በሰሜን ኢትዮጵያ በኩል ለሁለት ዓመታት ያህል ስንሰማውና ስናየው የቆየነው አሰቃቂና አውዳሚ ጦርነት እልባት አግኝቶ ልክ በሁለተኛው ዓመት ዋዜማ ከወደ ደቡብ አፍሪካ አስደሳች ዜና ሰምተናል፡፡ ተፋላሚ የነበሩ ወገኖች እጅ ለእጅ ተጨባብጠው ማየት ሰላም ፈላጊ የሆነን ወገን ሁሉ የሚያስደስት ክስተት ነበር፡፡
እነሆ ከዚያች ቀን ጀምሮ የአገራችን አጀንዳ ሰላም
ሆኗል፡፡ ታዲያ ይህ የሰላም ዜና ሲሰማ እና ያ አውዳሚ ጦርነት ሊቆም ስምምነት ሲደረግ ለፌዴራሉ መንግሥት እና ለሕወሓት መልዕክት አለኝ፤ ምንም እንኳን ፈተናዎች ቢበዙበትም የሰላም ድምጾችን ብቻ ስሙ የሚል!።
ይህ የሰላም አየር የተገኘው በፌዴራሉ መንግሥት እና በሕወሓት ቆራጥነት ነውና ሊመሰገኑ ይገባል፡፡ ጦርነቱ በሕዝብ ላይ ያደረሰውን እና ሊያደርስ የሚችለውን ጥፋት ይብቃ ብለው ለሰላም የመደራደሪያ ነጥቦችን አስቀምጠው መፈራረማቸው የውጭ ጠላቶቻችንን አንገት የሚያስደፋ ሆኗል፡፡
በአንድ አገር ውስጥ ሁለት የታጠቀ ኃይል መኖር የለበትም በሚለው ፤ ከሀገር ሉዓላዊነት ጋር የተያያዘውን መርህ አምኖ፣ ከቀደመ ስህተቱ ተምሮ፣ ሕወሓት ትጥቅ ሊፈታ መስማማቱ ያስመሰግነዋል፡፡ እውነተኛ ሰላም ፈላጊ መሆን ማለት እንዲህ ነው!፡፡
አሁን ከፌዴራሉ መንግሥትም ሆነ ከሕወሓት የሚጠበቀው በደረሱበት የሰላም ስምምነት መሰረት ለስምምነቱ ፍጹም ተገዥ የመሆናቸው እውነታ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በሀገሪቱ ታሪክ ወስጥ ስፍራ የሚያስገኝላቸው ሲሆን የአዲስ ታሪክ ጀማሪ በመሆንም እንዲዘከሩ እድል የሚሰጣቸው ነው።
ሀገርን ወደ እንደ ሀገር አስተማማኝ ወደ ሆነ ሰላም ከመውሰድ ባለፈ ፤ ለጀመርነው ልማት አቅም በመፍጠር ብልጽግና እውን እንዲሆን የሚያስችል እድል መፍጠር ይችላሉ። ኢትዮጵያን የብልጽግና ከፍታ ላይ ይሰቅላሉ፡፡ በጀመረቻቸው ትልልቅ ፕሮጀክቶች፣ አጀንዳዎች እና የከፍታ ጉዞዎች ታሪካዊ አሻራ ያስቀምጣሉ፡፡ ተፈፃሚ ሳያደርጉት ቢቀሩ ግን የታሪክ ተወቃሽ ይሆናሉ፡፡
የፌዴራሉ መንግሥት ሆነ ሕወሓት ቀደም ሲል የተስማሙባቸውን ጉዳዮች ተፈጻሚ ማድረግ ፤ በራሱ አልጋ በአልጋ ነው ተብሎ አይገመትም ፤ ጦርነቱ በሀገርና በሕዝብ ላይ ያስከተለው ሁለንተናዊ ጥፋት መረዳት የማይችሉ፤ ጦርነት ለችግሮች አልፋና ኦሜጋ ነው ብለው የሚያምኑ፤ ከዛም በላይ ከጦርነቱ አትራፊ የሆኑ ሃይሎች ለተፈጻሚነቱ ተግዳሮት መሆናቸው አይቀርም። ይህንን ተግዳሮት ሰብሮ/አሸንፎ ለመውጣት ቆራጥነት ያስፈልጋል፡፡ ይህ ቆራጥነት የሚመነጨው ደግሞ የሰላም ድምጾችን ብቻ በመስማት ነው፡፡
ባለፈው ሰኞ ምሽት በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን የተላለፈ ዜና ላይ አንዳንድ በውጭ አገራት የሚኖሩ የትግራይ ተወላጅ የዲያስፖራ አባላት ሰላምን የማይደግፍ ነገር ሲያስተላልፉ እንደነበር ለማየት ችያለሁ፡፡ በእነዚሁ የትግራይ ተወላጅ ዲያስፖራ የማህበራዊ ገጾችም ልክ ያልሆኑ ነገሮችን ስናይ ቆይተናል ፤ ዛሬም እያየን ነው፡፡
እነዚህ ወገኖቻችን እየሄዱበት ያለው የተሳሳተ የጥፋት መንገድ ከጦርነት የሚገኝ ትሩፋት ይኖራል ብሎ ከማመን ፤ የጦርነቱን ሰብአዊና ቁሳዊ ውድመት ካለመረዳት የመነጨ ሳይሆን፤ ከጦርነቱ ሩቅ በሆኑ ሀገሮች ከመኖራቸው ጋር በተያያዘ የተፈጠረ ደንታ ቢስነት እንደሆነ ለማሰብ አይከብድም።
ሕወሓት ለእነዚህ ሃይሎች ሃላፊነት ለጎደለው ጮኸት ጆሮውን ሊሰጥ አይገባም። በጦርነቱ ግንባር ገፈት ቀማሽ ለሆነው የትግራይ ሕዝብ ሰላም ሲል የገባውን ቃል እና የተፈራረመውን ስምምነት ተፈጻሚ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ለዚህም የሰላም ስምምነቱን ተከትሎ በሕዝቡ ውስጥ የተፈጠረውን ስሜት በአግባቡ ሊያጤነው ይገባል።
ዶ ቸ ቬለ (DW) ሕዝቡ የሰላም ድርድር በመጀመሩ የተሰማውን ደስታ አስመልክቶ የሰራው ዘገባም የሕዝቡን ስሜት ምን እንደሚመስል አንዱ ማሳያ እንደሆነ ለመገንዘብ የሚከብድ አይደለም።
በተመሳሳይ የፌዴራሉ መንግሥትም የገባውን ቃል እና የተፈራረመውን ስምምነት ተፈፃሚ እንዲያደርግ ቆራጥነት ሊኖረው ይገባል፡፡ 120 ሚሊዮን ሕዝብ አንድ አይነት ድምጽ ይኖረዋል ተብሎ አይጠበቅም፤ መንግሥት ለአገር ይጠቅማል ብሎ ያሰበውን ነገር ያደርጋል፡፡ ሰላም ማስፈን የአንድ መንግሥት ተቀዳሚ ተግባር ነውና የሰላም አማራጭ የማይፈልጉ ኃይሎች ካሉ ቁርጣቸውን ሊነገራቸው ይገባል፡፡
በፌዴራሉ መንግሥት እና በሕወሓት መካከል የተደረገው የሰላም ድርድር እና የተደረሰበት ስምምነት የምርም የኢትዮጵያን አሸናፊነት ያሳየ ነው፡፡ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓትን ማስፈን ፤ የሀገር ሉዓላዊነትን ማስከበር ያስቻለ ነው ። ኢትዮጵያ አሸንፋለች የሚባለውም ለዚህ ነው።
ከዚህም ባለፈ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መሥራችና መቀመጫ መሆኗ ፤ የአፍሪካ ሕብረት ደግሞ ‹‹ለአፍሪካዊ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሔ›› የሚል መሪ ሃሳብ ይዞ የሚንቀሳቀሱ መሆኑ ስምምነቱ የሕብረቱን መሪ ሃሳብ ተግባራዊ በማድረግ አዲስ አህጉራዊ እውነታ መፍጠር ያስቻለ ነው፡፡
ኢትዮጵያ የራሷን ችግር በራሷ መፍታት እንደምትችል በተጨባጭ ለዓለም ማሳየት የቻለ ፤ ያለማንም ጣልቃ ገብነትና ወሳኝነት ጦርነት አያስፈልገንም ብለው ሕገመንግሥታዊና ሉዓላዊነትን መሰረት ባደረገ መርህ መስማማት መቻላቸው፡ ፡ ኢትዮጵያ የራሷን ችግሮች በራሷ ትፈታለች ብሎ በሙሉ አፍ መናገር ያስቻለ አዲስ ክስተት ነው፡፡
ከዚህ በፊት በሰላም አስከባሪነት የምትታወቀው ኢትዮጵያ ‹‹ምነው ምን ነካት!›› ሲሉ የነበሩ የአፍሪካ አገራት ሁሉ ‹‹ዋው! ኢትዮጵያ እውነትም ትልቅ አገር ናት›› እንዲሉ አስቻሏል፡ ፡ በቀጣይ ሁለቱ አካላት ስምምነታቸውን አክብረው ተግባራዊ ካደረጉ የትልቅ አገር ታሪካዊ ተወዳሽ ይሆናሉ፡፡
አዎ! የምንመኘው ይህንኑ ነው፡፡ ከተፋላሚ ኃይልነት ወደ ተደጋጋፊ ኃይልነት መምጣት፣ በሁሉም መስክ የተጀመረውን የከፍታ ጉዞ አብሮ ማስቀጠል፣ ለዓለም የሚበቃውን የኢትዮጵያ እምቅ ሀብት በጋራ እና በፍቅር መጠቀም፣ ከአውዳሚነት ወደ አልሚነት መሸጋገር፣ ለጦርነት የሚሰማሩ ወጣቶችን ለልማት ማሰማራት፡፡
ለምሽግ ይውል የነበረውን ቦታ ለስንዴ እና ለመናፈሻ ማዋል፣ ለጥይት መግዣ ይውል የነበረውን ገንዘብ ለማዳበሪያ መግዣ ማድረግ፣ ይዘራረፍ የነበረ ተፋላሚ እንድጎራረስ ማድረግ፣ ታንክ የሄደባቸውን ሜዳዎች ትራክተርና ኮምባይነር እንድሄድባቸው ማድረግ… ይህ ነው የአንድ አገር ወዳድ መንግሥት ወይም ድርጅት መገለጫ፡፡
ከዚህ ውጪ ሀገርን ዳግም ወደ ጦርነት ለመውሰድ የሚደረግ የጥኛውም የእምቢተኝነት ተግባር ለሀገርና ለሕዝብ ተቆርቋሪ ነኝ የሚል አካል መገለጫ ሊሆን አይችልም ፤በየትበኛውም
መመዘኛ ። በሕዝብ ዘንድ የሚጠላ እና ሲወቀስ የሚኖር ነው፡፡ በጎረቤት አገራትም ሆነ በውጭ አገራት ኢትዮጵያ የነበራትን ገናና ስም እና ሰላም አፍቃሪነት የሚያጎድፍ ነው::
ለምትወዷት አገራችሁ፣ ለምትመሩት ሕዝባችሁ ትክክለኛው መስመር አሁን የያዛችሁት ነው፡፡ የሰላምና እርቅ መንገድ። ፍቅር ካለ፣ መተሳሰብና ቅንነት ካለ የኢትዮጵያ ሀብት ለማንም እንደሚበቃ የአደባባይ ሀቅ ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የሰላም ድርድሩ ብሥራት በተሰማበት ማግስት በአርባ ምንጭ የተናገሩትም ይህንኑ ነበር፤ በሰላም የተገኘውን ድል በልማት ማስቀጠል፡፡ ያኔ ኢትዮጵያ ለሁላችንም ምቹ ትሆናለች፡፡
ለመሆኑ ልብ ብለን አስተውለነው እናውቃለን? እስኪ የብዙ ችግሮቻችንን ምክንያቶች ልብ እንበል! አብሮ ባለመሥራትና በመገፋፋት የተከሰቱ ናቸው፡፡ ፍቅር፣ አንድነትና ሰላም ቢኖር እነዚህ የሚታዩ ችግሮቻችን ሁሉ አይኖሩም፡፡
ለስምምነቱ ተፈጻሚነት ከፌዴራሉ መንግሥት እና ከሕወሓት አመራሮች ብቻ ሳይሆን ከእኛ ከተራ ዜጎችም ብዙ የሚጠበቅ ነገር አለ፡፡ ይሄውም የጀመሩትን የሰላም መንገድ ማጠናከርና ከጎናቸው መቆም፡፡ በጦርነቱ ወቅት ‹‹ሕዝብ ነው የሚጎዳ›› ስንል ቆይተናል፡፡ ስለዚህ አሁን ለሕዝብ ተብሎ የሰላም መንገድ ሲጀመር አመስጋኝና አበረታች መሆን አለብን፡፡
የትናንት ነገር ትናንት አልፏል፡፡ ዛሬ ሌላ ነው፤ ዛሬ የሚሰራው ለነገ ነው፡፡ አንድን ነገር እንደ አዲስ ስንጀምር ካለፈው ስህተት በመማር እንጂ ያለፈው ላይ ችክ ማለት ግትርነት
ነው፡፡ ኢትዮጵያም ሆነች ሌላው ዓለም በየሥርዓቱ አንዳንድ መጥፎ ክስተቶች ያጋጥሟቸዋል፡፡ የሚያስመሰግናቸው ችግሩን የፈቱበት መንገድ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ዓውድ ብቻ እንኳን ካየነው፤ በዘመነ ኢህአዴግም፣ በደርግም፣ በቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴም…. በየሥርዓቱ ችግሮች ነበሩ፡፡ ከአንዱ ሥርዓት ወደ አንዱ ሥርዓት ለውጥ የሚደረገው በኃይል ነበር፡፡ ከኢህአዴግ ወደ ብልጽግና የተደረገው የሥርዓት ለውጥ ግን ያለምንም ጦርነት በኢትዮጵያም ሆነ በአፍሪካ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ የዴሞክራሲ ጅማሮ ነበር፤ በመሃል የተፈጠረው ተፈጠረ፡፡
አሁን ወደ ሰላም እየተጓዝን ነው። እየሄድንበት ያለው የሰላም መንገድ በአገራችን ታሪክ አዲስ የዴሞክራሲ ምዕራፍ የሚከፍት ነው፡፡ ለአፍሪካ ብቻ ሳይሆን ለዓለም ምሳሌ የሚሆን ነው፡፡ ይጠፋፋሉ ሲባል ሁለት ተፋላሚ ኃይሎች አንድ ሆነው አገራቸውን ወደ ከፍታ ሲወስዱ ማየት የማንንም ቀልብ የሚስብ ነው፡፡
ሚሊዮን ሺበሺ
አዲስ ዘመን ኅዳር 3/ 2015 ዓ.ም