እውነት ለመናገር ከጦርነቱ ሀንጎቨርና ድባብ መውጣት ፈታኝ ሆኖ ነው ያገኘሁት። በአስፕሪን ወይም በ«እንደ ወረደ ቡና» በቀላሉ የሚፈወስ አይደለም። እንደ ግለሰብ ሽግግሩ እንዲህ የከበደኝ፤ እንደ አገርና ሕዝብ ምን ያህል ሊከብድ እንደሚችል አስቡት። ስለሆነም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በ«አዲስ ወግ»ም ሆነ በሌላ አገራዊ መድረክ፤ በእነ ዶ/ር ምህረት ደበበና ሌሎች የዘርፉ ልሒቃን ላለፉት ሁለት አመታት ከመጣንበት የጦርነት የልቦና ውቅር ወደ የሰላም የልቦና ውቅር የሚያሸጋግር «የመላ ድልድይ» ሊዘረጉልን ያሻል። «አዲስ ወግ» ን የመረጥሁት ካሉን አጀንዳ ማቀበያ መድረኮች የተሻለ ሆኖ ስላገኘሁት ነው።
ለእኔ ሰሜን ዕዝ የተጠቃም ጊዜ፤ ደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ ላይ የሰላም ስምምነቱ ተፈጸመ የተባለ ዕለትም እኩል ደንግጫለሁ። የዚያን ጊዜም ዛሬም ወደ ራሴ ለመመለስ ተቸግሬያለሁ። እዚህ ላይ ልብ እንዲባልልኝ የምፈልገው ስለዘላቂ ሰላምና እርቅ አይደለም እያነሳሁ ያለሁት። ስለተፈጠረብን ጊዜያዊ የስሜት መዘበራረቅ እንጂ።
ወደ ዛሬ መጣጥፌ ስመለስ፤ ጦርነት ምን ያህል አስከፊና ዘግናኝ እንደሆነ በዓይኔ በብረቱ ያየሁት በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት (ሚያዝያ 1990- 1992ዓ.ም) ነው። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ባልደረባ እያለሁ ለተወሰኑ ወራት በዚያን ጊዜዋ የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ዋና ከተማ አሳይታ ተመድቤ ሳገለግል ነው፤ እንግዲህ በፊልምና በዜና ብቻ ከማውቀው ጦርነት ጋር ፊት ለፊት የተፋጠጥሁት፤ በወቅቱ ከነበሩ ግንባሮች አንዱ ከሎጊያ ከተማ በቅርብ ርቀት የሚገኘው የቡሬ(አሰብ መስመር) ግንባር ነው።
ሎጊያ ከክልሉ አዲሷ መዲና ሰመራ በቅርብ ርቀት የምትገኝ በዋናው የጅቡቲ መስመር የተከተመች ሞቅ ደመቅ ያለች ከተማ ናት። በጦርነቱ ወቅት የወገን ቁስለኛም ሙትም ገለል ከሚደረግባቸው ከተሞች አንዷ ነበረች። በዚች ከተማ አንድ የቁስለኞች ማገገሚያ በመቶዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች እጃቸውን፣ እግራቸውን፣ ዓይናቸውን አጥተው፤ አንዳንዶችም
ለማየት የሚዘገንን ጉዳት ደርሶባቸው ስመለክትና ስለቀሪው ዘመናቸው ሳስብ የጦርነት አስከፊነት ግዘፍ ይነሳብኛል። ወጣቶች ከማሰልጠኛ እንደወጡ ቀጥታ ወደ ግንባር መላካቸውና ሌሎች እዚህ ላይ መግለጽ የማልፈልጋቸው ችግሮች ተጨምረው ከፍተኛ ጉዳት ደርሶባቸዋል ።
ቁስለኞችን ማከም ይቅርና እህል ውሃ መስጠትና ማገላበጥ ባለመቻሉ ከአሳይታ የተለያዩ ቢሮዎች ሠራተኞች በፈረቃ ሎጊያ እየመጡ እገዛ ያደርጉ ነበር። ብዙዎች የሚያዩት ነገር ከአቅማቸው በላይ ስለሆነ እርዳታ ማድረግ ይቅርና ጉልበታቸው ሲከዳቸው ተመልክቻለሁ። በዚህ ጊዜያዊ የቁስለኞች ማገገሚያ የሰማሁት የህመምና ስቃይ ድምጽ ዛሬ ድረስ በእዝነ ህሊናዬ ያቃጭላል። እነዚያ ቆስለው ያየኋቸው ወጣት ጀግኖች ምንጊዜም ከዓይነ ህሊናዬ አይጠፉም።
ተገደን በገባንበት በዚህ ዘግናኝ ጦርነት የሆነው ደግሞ የከፋና ዘግናኝ ነው። በኢትዮ- ኤርትራ ጦርነት ከሁለቱ ወገን 70ሺህ ሲሞት፤ ከዚህ የማይተናነሰው ደግሞ ቁስለኛና አካል ጎዳተኛ ሆኗል። በምዕራባውያኑ ሳይቀሩ ከ2ኛ የዓለም ጦርነት በኋላ ከተካሄደው ዘግናኝ ጦርነቶች አንዱ ተብሏል። በጦርነቱ በብዙ ቢሊዮኖች የሚገመት የአገር ጥሪትና ሀብት ፈሷል። ወድሟል። ጦርነቱ ከተጠናቀቀ በኋላም በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል እርቅ ባለመውረዱና የዘ ሔጉ ገለልተኛ ፍርድ ቤት ውሳኔ ባለመፈጸሙ በአገራቱ ድንበር ለ18 አመታት በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮች በምሽጋቸው ተፋጠው ስለኖሩ ፤ የዲፕሎማሲው ግንኙነትም ባለመታደሱ በቀጣናው ውጥረት ነግሶ ኖሯል።
ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ኃላፊነት እንደመጡ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ለኤርትራ ሕዝብና መንግሥት የሰላም ጥሪ በማድረጋቸው በሁለቱ አገራት ሰላም ማውረድ ቻሉ። የሁለቱ አገር መሪዎች ተገናኙ። የሰላም ስምምነት ተፈራረሙ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ወደ አስመራ ሲያቀኑ ለማመን የሚከብድ አቀባበል ተደረገላቸው። ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡም ተመሳሳይ አቀባበል ተደረገ። ወዲያው ድንበሮች ተከፈቱ። በረራ ተጀመረ። ተለያይተው የነበሩ ቤተሰቦች እንባ እየተራጩ ተገናኙ። ይሄን ተስፋና ደስታ አጣጥመን ሳንጨርስ እክል ገጠመው። ብዙም ሳይቆይ ተከፍተው የነበሩ ድንበሮች መልሰው ተዘጉ።
ጥቅምት 24 ቀን ፣ 2013 ዓ.ም በሰሜን ዕዝ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ስንሸሸው ወደኖርነው ጦርነት ገባን። በአገሪቱ ታሪክ ተሰምቶም ታይቶም የማይታወቅ አሰቃቂ ጦርነት ተካሄደ። በጦርነቱ ከ500ሺህ በላይ አምራች ኃይል ተቀጠፈ። ቆሰለ። በሚሊዮኖች ተፈናቀሉ። ንጹሐን ተጨፈጨፉ። አስገድዶ መድፈር ተፈጸመ ። በመቶ ቢሊዮኖች የሚገመት ሀብት ወደመ። ተዘረፈ። የሰማናቸው ያየናቸው ሰቆቃዎች ከባድ ናቸው፤ ለዚህም ነው የሽግግር ጊዜ ያስፈልገናል የምለው።
ስለ እውነትና እርቅ በተወሳ ቁጥር ከልዑል ፈጣሪ ለጥቆ መቼም ወደ ዓይነ ፣ እዝነ ህሊናችን ግዘፍ ነስቶ የሚመጣው ፣ በግርማ ጮሆ የሚሰማን ኔልሰን ማንዴላ (ማዲባ) ነው። የአፍሪካ ናሽናል ኮንግረስ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ አፓርታይድ፣ ኤፍ ደብሊው ዴክለርክ፣ …፤ ከዚያ ይከተላሉ። ስለ እርቅ ሲነሳ ማዲባ አብሮ ስሙ ይወሳል። ማዲባ ሲወሳ እርቅ አብሮ ይነሳል። የእርቅ ምልክት ነው። በገዘፈው ሰብዕናው ገልጦ በተግባር አሳይቶናል። ኖሮታል። መስክሮታል።
እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1998 የእውነትና እርቅ ኮሚሽን ያጠናቀረውን ሪፖርት ማዲባ ከሊቀ መንበሩ ቀሲስ ዴዝሞንድ ቱቱ ከተረከበ በኋላ ባስተላለፈው መልዕክት፤ «በሕገ መንግሥታችን የተደነገገውን ዴሞክራሲና ሰብዓዊነት ለመጠበቅ እርቅ ያስፈልገናል።» ብሎ ነበር። አዎ ! ተቀራርቦ መነጋገር፣ እርቅና መግባባት ከሌለ ሰላም ሊሰፍን አይችልም። ሰላም ከሌለ አይደለም ሰብዓዊነት፣ ዴሞክራሲ፤ የአገር ህልውና ላይ አደጋ መደቀኑ አይቀርም። እንደኛ በውጥረት፣ ውሉ በጠፋ ትብታብ እና ፅንፍ በረገጠ አቋም ላይ ለምትገኝ አገር ተቀራርቦ መነጋገር፣ መግባባትና መታረቅ የግድ ነው። ለመሆኑ ፖለቲካዊ እርቅ Political Reconcilation ሲባል ምን ማለት ነው?
“NESS MODEL OF RECONCILIATION “ በሚል ርዕስ ለንባብ ባበቃው ጽሑፉ ፤ «ፖለቲካዊ እርቅን የተሰበረ ግንኙነት የመጠገን ሂደት ነው።» በታሪክ ምርኮኝነት፣ ሆን ተብሎ ለፖለቲካዊ ጥቅም ሲባል በተነዛ የፈጠራ ትርክት ፣ በማንነት ላይ በተዋቀረው ፖለቲካ፣ በግራ ዘመም አይዲዮሎጂ እና በሕዝበኝነት populism በተካረረ ልዩነት፣ ቁጭት መፍጠር እንደማታገያ ስልት በመወሰዱ፣ በሴራ ኀልዮት በተጎነቆለ ጥላቻ፣ ስልጣን ላይ ለመቆየት ሲባል በሕዝቦች መካከል በተዘራ ልዩነት፣ አንድን ሕዝብና ሃይማኖት በመለየት እንደጠላት መፈረጅ፤ ወዘተረፈ. የፈጠረው የፖለቲካዊ ልዩነት እንዲሽር ከአንገት ሳይሆን ከልብ የመነጨ ፖለቲካዊ ዕርቅ ያስፈልጋል።
ኮሊን ፖለቲካዊ እርቅ ሦስት ንጣፎች layers እንዳሉት ያትታል። የላይኛው የፖለቲካ ፓርቲዎች ግንኙነት እንዲበላሽ ያደረጉ መግፍኤዎችን መለየት፤
እነዚህን ምክንያቶች ከፍ ብዬ ለማሳየት የሞከርሁ ሲሆን፣ የአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ግን ይበልጥ ዘርዝሮ ሊተነትናቸው ይችላል። መካከለኛው በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ከሚፈጠር እርቅ የሚጠበቀውን ግብ ለይቶ ማስቀመጥ ነው። የተቀመጠው ግብ ውስን ሊሆን ይገባል።
እንደ ብሔራዊ እርቅ ያሉ ጉዳዮች ግን ከፓርቲዎች አልፈው አገራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩና ተዋናዮቹም በርካታ ስለሆኑ በዚህ የእርቅ ሒደት የሚካተቱ አይደሉም። የታችኛው ንጣፍ እርቁ የሚሳካበትን ስልት መንደፍ ነው። ከፍ ሲል የተነሱትን ሁለቱ የፖለቲካዊ እርቅ ንጣፎችን በጥንቃቄ መተግበር የእርቅ ሂደቱን ውጤታማ ያደርገዋል ተብሎ ይታመናል።
ኮሊን መርፊ በማስከተል፤ «ፖለቲካዊ እርቅ የሕግ የበላይነትን በስምምነት በጋራ የማረጋገጥ እንጂ ይቅር የመባባል ጉዳይ ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም። በእርቅ ሂደቱ ምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ መቀመጥ የለበትም ። …» በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ሊካሂድ የታሰበው እርቅ ከምንም ዓይነት ቅድመ ሁኔታ ጋር ሊያያዝ አይገባም ።
የዴስቲኒ ኢትዮጵያ አባላት የሄዱበት መንገድ ለዚህ ጥሩ አብነት ነው። በብልፅግና ፣ በኢዜማ ፣ በአብን፣ በኦፌኮ፤ በኦነግ ፣ …፤ በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ፖለቲካዊ እርቅ ሲወርድ በተዘዋዋሪም ሆነ በቀጥታ የሕግ የበላይነትን ማክበር ላይ መግባባት ላይ ይደረሳል ማለት ነው። ደጋፊዎቻቸውም ይህን ፈለግ ይከተላሉ ተብሎ ይታመናል። ከዚህ ባሻገር በቀጣይ ለሚታሰበው ብሔራዊ እርቅ ጥሩ መደላድል ይፈጥራል ተብሎ ይታመናል።
ሆኖም ስለ ሰላምና ስለ ይቅርታ መነጋገር የራሱ የሆነ ሂደትና ቅደም ተከተል እንዳለው አበክሮ ማጤን ያሻል። እዚህ ላይ የሰላም፣ የእርቅ፣ የሽምግልና ዓለምአቀፍ ረቡኒው እና በአሜሪካ በሀሪሰንበርግ በሚገኘው ኢስተርን መኖናይት ዩኒቨርሲቲ የዓለምአቀፍ ግልግልና ዕርቅ ፕሮፌሰር የሆኑት፤ እንዲሁም የእርቀ ሰላም ኮሚሽን አባል የነበሩት ሕዝቅያስ አሰፋ ፤ « የሰላምና እርቅ ትርጉምና መንገዶች ፤ » በሚለው መፅሐፋቸው ፤ ያነሷቸውን ቁም ነገሮች ፤ ሰላም ፣ ዕርቅ የራሱ መንገድ እና አካሄድ እንዳለው ያሳያሉ።
«…ሰላም ለግጭቶች መነሻ የሆኑትን ልዩነቶች በሚገባ ከለየና ከመረመረ በኋላ ልዩነቶችን ለፈጠሩት ችግሮች ሁሉ ወገኖች የሚበጁ መፍትሔዎች መፈለግ ማለት ነው። …፤ » ገፅ 26 _ 33 ፤ ሲሉ ሰላምን ይበይኑታል። ሰላም ግጭትን ማስወገድ አይደለም። በቀዳማይ ኢህአዴግ እንደሆነው በደህንነት፣ በፀጥታ ኃይሉና በካንጋሮ ፍርድ ቤቶች ግጭትን ማስወገድ ይቻል ይሆናል እውነተኛውን ሰላም ግን አያረጋግጥም።
«የአስቸኳይ ጊዜ አውጆ ግጭትን ተቃውሞን ፀጥ ለጥ ማድረግ ይቻል ይሆናል ዘላቂ ሰላምን ግን ማስፈን አይቻልም ። ለዚህ ነው ፕሮፌሰር ሰላም ለግጭቶች መነሻ የሆኑትን መርምሮ ለሁሉም ወገኖች የሚበጅ መፍትሔ መፈለግ ነው ያሉት»።
አሁን በአገራችን የሚከሰቱ ግጭቶች ከዚህ አንጻር ማየትን ይጠይቃል። ፕሮፌሰር ከላይ በጠቀስሁት መፅሐፋቸው የሰላም ሥራ የራሱ እሴቶችና መርሆዎች እንዳሉት ያመላክታሉ።
ሀ . መሠረታዊ የግጭት መንስኤዎችን መርምሮ የአመለካከት አድማስን ማስፋት፤
ለ . ፍትሕ፦ ዘላቂ ሰላም ያለፍትሕ ሊገኝ አይችልም። ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካው ፍትሕ ባልተረጋገጠበት ሰላምን ማምጣት አይቻልም። ለዚህ ነው የለውጥ ኃይሉ ተቋማት ላይ እየሠራ ያለው።
ሐ . መግባባት፦ ፕሮፌሰር መግባባትን ሲበይኑት፤ አንዱ ሌላው ውስጥ ሲገባና ሌላውም መጀመሪያው ውስጥ ሲገባ ነው ይላሉ፤ ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ መግባባትን መፍጠር የማዕዘን ድንጋይ ነው። በግጭቶች ተሳታፊ በሆኑ ኃይላት መካከል መግባባትን ለመፍጠር ደግሞ፤ መጀመሪያ የግጭቱ አካላት፣ የሚጋጩባቸው ምክንያቶች እና መፍትሔዎች ላይ መግባባት ይጠይቃል።
መ . የሕይወት መተሳሰር፡ – mutuality
ዘላቂ ሰላም እንዲፈጠር የሰዎች ሕይወት የተሳሰረ መሆኑን በጥልቀት መገንዘብ፣ መረዳት ይጠይቃል። የሰው ልጆች መሠረታዊ ፍላጎቶች ተመሳሳይ፣ ተቀራራቢ መሆናቸውን መገንዘብ ማለት ነው ። ሰው መከበርን ፣ መወደድን፣ መደመጥን፣ ከፍ ከፍ ማለትን እንደሚሻ ሁሉ በተቃራኒው ውርደትን፣ መገፋትን፣ መጠላትን ፣ መናቅን፣ መቆርቆዝን፣ …፤ ማስወገድ ነው ። ፕሮፌሰር ሕዝቅያስ በዚሁ መፅሐፋቸው ስለ እርቅ ምንነትና መሠረታዊ አላባውያን fundamental elements እንደሚከተለው ይተነትናሉ ።
«እርቅ ማለት በከባድ ጠብና ይህም ባስከተለው መጎዳዳት፣ ጥላቻና መፈራራት ምክንያት ተለያይተው፣ ተራርቀው፣ ተቆራርጠው የነበሩ ሰዎች የወደመውን የጋራ ኑሮአቸውን እንደገና ለመገንባት የሚጓዙበት ሂደት ነው። እርቅ ጥልቅ የሰላም ግንባታ ዘዴና አላማ ነው። የእርቅ ሂደት የሚከተሉትን እርምጃዎች ያካትታል ። »
1ኛ. በግጭቱ ተካፋይ የነበሩ ወገኖች በሌላው ላይ የፈፀሙትን በደልና ጉዳት በሀቀኝነት ማመን፤
2ኛ. በተፈፀመው በደል እውነተኛ ፀፀትን መግለፅ፤
3ኛ. የተበደለውን አካል ከልብ ይቅርታ መጠየቅ፤
4ኛ. የተበደለው አካል ከልብ ይቅርታውን በመቀበል ይቅር ማለት፤
5ኛ. ተበዳዩን ጉዳት ከመድረሱ በፊት ወደ ነበረበት ሁኔታ መመለስ ፤
6ኛ. በደሉ እንደገና እንደማይፈፀም አስተማማኝ የሆነ ማረጋገጫ መስጠት ፤
7ኛ. ከግጭቱና ካስከተለው ጉዳት በመማር የሁለቱንም ወገኖች ጥልቅ ፍላጎትና ጥቅም የሚያራምድ፣ የሚያጎላምስና የሚያስተሳስር አዳዲስ ግንኙነቶችን መመስረትና ዕቅዶችን መንደፍ፤ የሚሉት ይገኙባቸዋል።
ፈጣሪ አገራችንን በቃሽ ብሎ ዘላቂ ሰላም ያስፍንልን !!!
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼዲያን)
አዲስ ዘመን ኀዳር 1/ 2015 ዓ.ም