የክብር ዶክተር ሀዲስ አለማየሁ የተወዳጁ ፍቅር እስከ መቃብር ልቦለድ ደራሲ ናቸው። ነገር ግን ከፍቅር እስከ መቃብር ድርሰታቸው ባልተናነሰ ፍቅራቸውን እስከ መቃብራቸው ይዘው የዘለቁ እውነተኛ የፍቅር መምህርም ናቸው። ይህ ወር የተወለዱበት ወር ነውና ይህንን መነሻ በማድረግ ታሪካቸውን ወደ ማውሳት እንሻገራለን።
የሀዲስ የትዳር አጋር የነበሩት ወይዘሮ ክበበጸሀይ ያረፉት ገና በተጋቡ በአፍላ እድሜ ላይ ነበር። ይሁንና ያኔ ወጣት የነበሩት ሀዲስ ሀዘናቸውን ውጠው ሌላ ትዳር ሳይመሠርቱ ነበር የኖሩት። በአንድ ወቅት ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ክብር ዶክተር ሀዲስ አለማየሁን እንዲህ አላቸው፦
“ለምን ሌላ ትዳር ሳይመሰርቱ ከ50 ዓመታት በላይ ቆዩ? ልጅም እንኳን አልወለዱም?” እሳቸውም የጣት ቀለበታቸውን አሳዩትና እንዲህ አሉት “ይሔን ቀለበት ያሰረችልኝ ክበበጸሀይ ናት። እኔም አስሬላታለሁ። እሷ የኔን ሣታወልቀው ነው ያረፈችው። እኔም የእሷን አላወልቀውም። ማንም አያወልቀውም። እሷ ነች ያሰረችልኝ” ሲሉ መለሱለት።
ከጻፉት በላይ ሆኖ እንደመገኘት የሚያረካ ነገር ይኖር ይሆን? ጋዜጠኛ ጥበቡ እንዳለው “ፍቅር እስከ መቃብር የሚባለው ታሪክ ከሀዲስ ህይወት ሌላ ምን አለ? ለትዳራቸው እስከ መጨረሻው ድረስ ታማኝ የሆኑ ክስተት ናቸው።”
ለመሆኑ ሀዲስ አለማየሁ ማን ናቸው? ሀዲስ ከአለቃ ዓለማየሁ ሰለሞን እና ከወይዘሮ ደስታ ዓለሙ በ1902 ዓ.ም ጎጃም ውስጥ ተወለዱ። አያታቸው (የእናታቸው አባት) አለቃ ዓለሙ ስዩም በእንዶዳም ኪዳነ ምኅረት ገዳም የዜማ መምህር ስለነበሩ ስድስት ዓመት ሲሞላቸው የግዕዝ ፊደሎችን ማጥናት ጀመሩ። ከእንዶዳም ኪዳነምኅረት በተጨማሪ በደብረ ኤልያስ፣ በደብረ ወርቅና በዲማ ጊዮርጊስ ገዳማት ተዘዋውረው የድጓ፣ የቅኔና የመጻህፍት ቤት (ትርጓሜ) ትምህርቶችን ተማሩ። በትምህርታቸውም ከጓደኞቻቸው ሁሉ የላቁ ነበሩ። በ1918 ዓ.ም ሀዲስና ሌሎች ጓደኞቻቸው ከመምህራቸው መሪጌታ በላይ ጋር በመሆን ወደ አዲስ አበባ አቀኑ።
አዲስ አበባ ደርሰው ጥቂት ጊዜያትን ካሳለፉ በኋላ አቶ አያሌው ንጉሤ ከተባሉና በስዊድን ሚሲዮን ትምህርት ቤት ያስተምሩ ከነበሩ ግለሰብ ጋር ተዋወቁ። አቶ አያሌውም ሀዲስና ጓደኞቻቸው ወደ ስዊድን ሚሲዮን ትምህርት ቤት ገብተው ዘመናዊ ትምህርት እንዲማሩ መከሯቸው። ሀዲስ ትምህርት ቤቱ ሀይማኖቴን ሊያስለውጠኝ ይችላል ብለው በመፍራታቸው ጥቂት አመነቱ። በመጨረሻ ግን ወደ ስዊድን ሚሲዮን ትምህርት ቤት ገብተው ትምህርቱን ጀመሩ። በሂደትም የዘመናዊ ትምህርትን ጥቅም በማወቃቸው የመንግስት ትምህርት ቤት መግባት እንዳለባቸው ወስነው ተፈሪ መኮንን የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤትን ተቀላቀሉ። ከራስ ኃይሉ ተክለሃይማኖት ግምጃ ቤት ባገኙት ወርሃዊ የገንዘብ ድጋፍም ከሶስተኛ እስከ ስድስተኛ ክፍል ድረስ ያለውን ትምህርት በተፈሪ መኮንን የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታተሉ።
በወቅቱ በትምህርት ቤቱ ውስጥ አመጽ ተቀስቅሶ ነበር፤ ‹‹… የአመጹ ጠንሳሾች በእድሜያቸው በሰል ያሉት ተማሪዎች ናቸው … ›› ተብሎ በመታመኑ እድሜያቸው ከ18 ዓመት በላይ የሆኑ ተማሪዎች ማደሪያቸው ከትምህርት ቤቱ ውጭ ሆኖ እንዲማሩ ተወሰነ። ይህ ውሳኔ አዲስ አበባ ውስጥ ቤተሰብና የቅርብ ዘመድ ለሌላቸው የትምህርት ቤቱ ተማሪዎች አስደንጋጭ ነበር። ሀዲስ አዲስ አበባ ውስጥ ቤተሰብም ሆነ የቅርብ ዘመድ ስላልነበራቸው ትምህርቱን ለማቋረጥ ተገደዱ።
በወቅቱ በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ይሰጥ የነበረውን የመምህርነት ስልጠና ወስደውም በስዊድን ሚሲዮን ትምህርት ቤት ማስተማር ጀመሩ። ከዘጠኝ ወራት የመምህርነት ስራ በኋላ ዳንግላ አካባቢ በነበረው የብሪታኒያ ቆንስላ ውስጥ እንዲሰሩ ተመደቡ። ዳንግላ አካባቢ የነበረው የብሪታኒያ ቆንስላ ከተዘጋ በኋላ ሀዲስ በአካባቢው የነበረው ጉምሩክ ተቆጣጣሪ ሆነው መስራት ጀመሩ። በዚህ ስራቸውም ላይ ብዙም አልቆዩም። በወቅቱ በአካባቢው የባሪያ ንግድ ይካሄድ ስለነበር የባሪያ ንግድ እንዲቆም የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት መንግስት ያወጣቸውን ድንጋጌዎችን የማስፈጸምና የመከታተል ኃላፊነት ተሰጥቷቸው ኃላፊነቱን አከናወኑ። ከዚያም በዳንግላም ሆነ በመላው አገው ምድር የመጀመሪያ የሆነውን የዳንግላ ትምህርት ቤትን እንዲያቋቁሙ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ተወጡ። ሀዲስ የትምህርት ቤቱ ዳይሬክተርና መምህር ሆነውም አገልግለዋል።
በ1928 ዓ.ም ወደ ደብረ ማርቆስ ተዘዋውረው በንጉስ ተክለሃይማኖት ትምህርት ቤት የእንግሊዝኛና የሂሳብ መምህር ሆኑ። የወቅቱ የጎጃም ገዢ የነበሩትን የልዑል ራስ እምሩ ኃይለስላሴ ልጆችንም ያስተምሩ ነበር። እስከ ፋሺስት ኢጣሊያ ወረራ ጊዜ ድረስም በዚያው በደብረ ማርቆስ ቆዩ።
ፋሺስት ኢጣሊያ ኢትዮያን በወረረችበት ወቅት ሀዲስ ከመንግስት ሳይጠብቁ ራሳቸው ጠመንጃ ገዝተው፣ የራስ እምሩን ጦር ተቀላቅለው በአርበኝነት መዋጋት ጀመሩ። የህዝቡንና የአርበኛውን ስሜት የሚቀሰቅሱ የኪነ ጥበብ ስራዎችንም እየሰሩ አቀረቡ። በ1929 ዓ.ም ጎጀብ ወንዝ አካባቢ በተደረገ ውጊያ ላይም ተማርከው ፖንዞ እና ሊፓሪ ወደሚባሉና በሳርዲና አካባቢ (ደቡባዊ ኢጣሊያ) ወደሚገኙ የሜዲትራኒያን ደሴቶች ተወስደው ታሰሩ። ከሰባት ዓመታት የእስራት ጊዜ በኋላም አርበኛው ሀዲስ ወደ ኢትዮጵያ ተመለሱ።
ከስደት መልስ ሀዲስ በተለያዩ ዘርፎች ያገለገሉ ሲሆን በተለይም በፖለቲካው ረገድ ሚኒስትር ዴኤታ እና ዲፕሎማት ሆነው አገራቸውን ብዙ አገልግለዋል። ይሁንና ሀዲስ በተለይ ዲፕሎማት ሆነው አዳዲስ ልምዶችን ቀስመው ከመጡ በኋላ ከንጉሰ ነገስቱ ጋር የነበራቸው ግንኙነት ብዙም የሰመረ አልነበረም። በተለይም ለውጥን አስመልክተው ለንጉሱ የጻፉት መልእክት አስከፍቷቸው ነበር። በዚህ መልዕክታቸው በ1953 ዓ.ም የተሞከረው መፈንቅለ መንግሥት መንስዔና ወደፊትም የመንግስት አሰራር ካልተሻሻለ የከፋ ችግር ሊያጋጥም እንደሚችል በመጥቀስ ኋላ ቀር የሆነው የኢትዮጵያ ማኅበረ-ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መዋቅር ሊሻሻል እንደሚገባ ገልጸዋል። ይህ መረር ያለ የሀዲስ ምክረ ሃሳብ ስልጣናቸውንና ክብራቸውን እንደዓይናቸው ብሌን ለሚጠብቁት ንጉሰ ነገስቱ ምቾትን አልሰጠም። በዚህም ንጉሰ ነገስቱ ሀዲስን ቢሯቸው አስጠርተው ‹‹ድፍረት ስለተሞላበት›› ደብደቤያቸው ገሰጿቸው። ሀዲስ ግን በንጉሰ ነገስቱ ሃሳብ ባለመስማማት በመልዕክታቸው ካሰፈሩት ሃሳብ በተጨማሪ ሌሎችንም ምክረ ሃሳቦችን ለንጉሰ ነገስቱ ተናገሩ። መልዕክቱ ለንጉሱ በደረሳቸው በስምንተኛው ቀንም ሀዲስ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ እንዲሆኑ ተደረገ። ንጉሰ ነገስቱ ራሳቸው የትምህርት ሚኒስትር ስለነበሩ ሹመቱ ከፍተኛ ትችት የሰነዘሩባቸውን ደፋሩን፣ በግልፅ ተናጋሪውንና ትሁቱን ሀዲስን ከጎናቸው አድርገው ለመቆጣጠር እንደሆነ ግልጽ ነበር። በኋላ ላይ ሀዲስ በገዛ ፈቃዳቸው ከትምህርት ሚኒስቴርነት ሲነሱ ዲፕሎማት ተደርገው ከአገር ራቅ እንዲሉ ተደረገ ባለቤታቸውም ያረፉት በዚህ ወቅት ነበር።
ሀዲስ በህዝብ ዘንድ በተለይ የታወቁት በደራሲነታቸው ሲሆን በኢትዮጵያ ስነጽሁፍ እንደ ማሳያ ተደርጎ የሚወሰደው ፍቅር እስከ መቃብርን ጨምሮ ሌሎች መጻህፍትንም ጽፈዋል። ከጻፏቸው መጻህፍት መካከል በተረት ብዙ ፍልስፍናዎችን ብዙ ትልልቅ ነገሮችን የተናገሩበትና ያስተማሩበት በ1948 ዓ.ም የጻፉት ተረት ተረት የመሰረት በሚለው መጽሀፋቸው ነው። ከዚያ በመለጠቅ በ1948 ዓ.ም የትምህርትና የተማሪ ቤት ትርጉም በሚል ስለትምህርት የጻፉ የመጀመርያው ሰው ናቸዉ። ሌላው ላለፉት 50 ዓመታት በኢትዮጵያ ስነ ጽሁፍ ውስጥ ትልቅ ማስተማርያ የሆነና የኢትዮጵያን ስነ ጽሁፍ ከፍ ብሎ እንዲታይ ያደረገ መጽሀፋቸው «ፍቅር እስከ መቃብር» የተሰኘው ልብወለድ 1958 ዓ.ም የታተመ ነው። በኢትዮጵያ ስነ ጽሁፍ ውስጥ አዲስ ክስተት አዲስ አስተሳሰብ ያመጣ ትውልድን ያነቃነቀ፤ ለለውጥ በብዙ ፍልስፍናዎች ብዙ ጥያቄዎችን ያነሳሳ መጽሀፍ ነው። ሌላው ኢትዮጵያ ምን ዓይነት አስተዳደር ያስፈልጋታል በሚል በቀዳማዊ ኃይለስላሴ ዘመነ መንግስት ተጽፎ የቆየ ነው። ሀዲስ አለማየሁ ይህንኑ ጽሁፋቸውን ለጃንሆይም አሳይተዋቸው ይታተማል ብለዋቸው ግን እሳቸዉም ያላሳተሙላቸው፤ በኋላም የደርግ አስተዳደር 1966 ዓ.ም ላይ ከመጣ በኋላ ለደርግ ሰጥተውት አይታተምም ተብሎ ያልታተመ መጽሀፋቸው ነው። ሌላው በኢትዮጵያ ስነጽሑፍ ውስጥ እንደዚሁ ተጠቃሽ የሆነው በ1974 ዓ.ም ያሳተሙት ወንጀለኛው ዳኛ የተሰኘው መጽሀፋቸው ነው። የጥንታዊውን የኢትዮጵያ የጋብቻ ሁኔታ ያሳዩበት በ1980 ዓ.ም ያሳተሙት የልምዣት የተሰኘው ትልቁ መጽሀፋቸውም ይጠቀሳል። ወደ መጨረሻ ላይ የጻፉትና የሳቸውንም ሆነ በሳቸው የዕድሜ ዘመንተኛ የሆኑ የሌሎችን ኢትዮጵያውያን የህይወት ታሪክ እና የኢትዮጵያን ታሪክ የዳሰሱበት ትዝታ የተሰኘው መጽሀፋቸው በ1985 ዓ.ም ያሳተሙትና ያስነበቡት ግሩም መጽሀፍም የቀዳሚነት ቦታን የሚይዝ ነው።
ከእለተ ሞታቸው ሁለት ዓመታት ቀደም ብሎ ቃለመጠይቅ ያደረገላቸው ጋዜጠኛ ጥበቡ በለጠ ስለ ፍቅር እስከ መቃብር ያጫወቱትን ጉዳይ በአንድ ወቅት ለጀርመን ድምጽ ራዲዮ እንዲህ ብሎ ተናግሮ ነበር። «ደራሲ ሀዲስ አለማየሁን በ1994 ዓ.ም አዲስ ዜና ለተሰኘው ጋዜጣ ቃለመጠይቅ አድርጌላቸው ነበር። የዚያን ጊዜ እንደነገሩኝ ፍቅር እስከ መቃብር መጽሀፍ እንደታተመ ሰዎች መጽሀፉን ይዘው ለጃንሆይ አሳይዋቸው። ይኸው አዲስ አለማየሁ ከኛ ጋር እየኖረ በኛ ተሹሞ የዚሁ የኛው መንግስት ባለስልጣን ሆኖ እንዲህ ዓይነት መጽሀፍ አዘጋጅቶ መንግስታችንን አዋረደ ብለው ለጃንሆይ ሰጧቸው። ጃንሆይም ተቀብለው መጽሀፉን ሲያዩ ርዕሱ ፍቅር እስከ መቃብር ይላል ከስሩ ልብ ወለድ ታሪክ ይላል እና ወድያው ሳያነቡ መለሱላቸው። ምንድን ነው የምትሉት እናንተ ሰዎች፤ ይሄ ሰው ፍቅር እስከ መቃብር ልብ ወለድ ታሪክ ብሎ ነው የጻፈው፤ ልቡ የወለደውን ነው የጻፈው ምን አድርግ ነው የምትሉት? ብለው ጃንሆይ መለሱት ስለዚህ ያ መጽሀፍ ተጽኖም አልፈጠረብኝም በጃንሆይ በኩል እንደውም ከሚወድዋቸው መጽሀፍት አንዱና ዋናው እሱ ነበር። ምክንያቱም እሳቸው የሚያስቡት እኔ የጻፍኩበትን ስርዓተ ማህበር እሳቸው ካሉበት በፊት የነበረ ብለው ነው ያሰቡት›› ብለዋል።
ሀዲስ በስነ ጽሁፍ ስራዎቻቸውም የቀዳማዊ ኃይለስላሴ የስነጽሁፍ ሽልማትን አሸንፈዋል። አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ የክብር ዶክትሬት ዲግሪ ሰጥቷቸዋል። ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲ ያሰራላቸው ከነኀስ የተቀረጸ ሃውልት በ2009 ዓ.ም በደብረ ማርቆስ ከተማ ቆሞላቸዋል። የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበርም በ2002 ዓ.ም ለክብር ዶክተር ሀዲስ ዓለማየሁ ያዘጋጀው የፖስታ ቴምብር በኢትዮጵያ የፖስታ ድርጅት ታትሞ ተሰራጭቷል። የደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲም ሀዲስ አለማየሁ የባህል ጥናት ተቋም የሚል ተቋም በስማቸው አቋቁሟል።
በኢትዮጵያ የፖለቲካና የስነጽሁፍ ዘርፎች ላይ ገናና ስም የነበራቸው ደራሲ፣ መምህር፣ ፖለቲከኛ፣ አርበኛ፣ ባለቅኔ፣ … የክብር ዶክተር ሀዲስ ዓለማየሁ በ1996 ዓ.ም በ94 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ስርዓተ ቀብራቸውም በአዲስ አበባ፣ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ጥቅምት 13 ቀን 2015 ዓ.ም