ብሔራዊ ፈተናን በተመለከተ ከቅርብ ዓመታት ጀምሮ ስናነሳ ኩረጃና ስርቆት የሚሉት ነገሮች ቀድመው ትዝ ይሉናል። ስርቆቱ ደግሞ ተማሪው አካባቢ ሲደርስ ነው የሚሰማው። እናም በጥረቱ ዩኒቨርሲቲ የሚገባው ከጊዜ ወደጊዜ እየቀነሰ መጥቷል። እንደውም ጎበዙ ተስፋ ቆራጭ ሰነፉ ደግሞ አነፍናፊ ሆኖ ዓመቱን ይዘልቃል። ‹‹ከዓመት ልፋት የአንድ ቀን የዓይን ጥራት›› የሚሉም ቀላል አልነበሩም። እናም ዓመቱን ሙሉ የለፋው በቤቱ ቀርቶ በተሰረቀው ፈተናና በተኮረጀው ውጤት ዩኒቨርሲቲዎችን ተቀላቅሎ ለመምህራንም ለራሱም ፈተና የሆነውን ቤት ይቁጠረው። ግን ዛሬ ይህ ሁሉ ማክተም እንዳለበት በማሰብ እንደ አገር አንድ ፕሮጀክት ተነድፎ የመጀመሪያው ዙር ተግባራዊ ሆኗል። ለውጡም ብዙዎችን ያስደሰተ ነው።
ከዚህ ጉዳይ ጋር በተያያዘ አገር አቀፍ ትምህርት ምዘና እና ትምህርት ሚኒስቴር በተደጋጋሚ መግለጫ ሰጥተዋል። መገናኛ ብዙኃኑም ግንዛቤ ሲፈጥሩ ቆይተዋል። እኛም እንደ አዲስ ዘመን በየጊዜው መረጃዎችን ስናደርስ እንደነበር ይታወሳል። ለመሆኑ ፕሮጀክቱ ምን ነበር፤ አተገባበሩስ እንዴት ነበር፤ ውጤቱስ ካልን በተደጋጋሚ ከተነገሩት ሀሳቦችና ከዚህ ቀደም ይዘናቸው ከወጣናቸው መረጃዎች በመነሳት ያለውን እውነት እናስታውሳችሁ።
በዚህ ዓመት ማለትም በ2015 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል የ2014 ዓ.ም ተፈታኞች ፈተናቸውን ይወስዳሉ። በቁጥር ከ900 መቶ ሺህ በላይ ተማሪዎች ናቸው። ይህ ቁጥር ደግሞ አምና በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ያልተፈተኑትን የሚጨምር ነው። ይሁን እንጂ ለውጤታቸው ማሽቆልቆል መሠረታዊ ነገሩ የፈተናው ተሰርቆ መውጣት እንደሆነ በተደጋጋሚ ስናነሳው ነበር። ፈተናው ብዙ ውዝግቦች ያስተናገደ እንደነበርም በደንብ አይተነዋል። በትምህርታቸው ተስፋ የተጣለባቸውን ሳይቀር ቤት ያስቀረና ተስፋቢስ ያደረገ እንደነበርም የምንዘነጋው አይመስለኝም። ግን እንደ ትምህርት ሚኒስቴር መፍትሄ ተበጅቶ ወደ ሥራ ተገብቷል። የመጀመሪያው ተማሪዎችን በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ አስገብቶ መፈተን ሲሆን፤ ጥብቅ ቁጥጥር የተደረገበትም ነው። አዲስ ፕሮጀክትም እንደሆነ ሁሉም ልብ ይለዋል። ታዲያ ይህ መሆኑ ምን አስገኘ፤ በመጀመሪያው ዙር ፈተና ምን ይመስል ነበር ? ካልን አሁንም ትምህርት ሚኒስቴር የሰጠውን ጋዜጣዊ መግለጫ አብነት አድርገን ማንሳት እንችላለን።
ዘንድሮ ለማይሠራ ተማሪም ሆነ ዩኒቨርሲቲ በሩጫ እገባለሁ ለሚለው ምንም ምቹ ሁኔታ የተፈጠረ አይመስልም። ምክንያቱም ፈተናውም ሆነ ተፈታኙ እንዲሁም ፈታኙ ከዩኒቨርሲቲው ሳይወጡ የሚከናወኑ ናቸው። ከፍተኛ ቁጥጥርም ይደረግበታል። ይህ ደግሞ በራሱ ጥረት ለማለፍ የገባውን ያሰበው ላይ እንደሚያደርሰው ምንም ጥርጥር የለውም። አዲስ የሚፈተኑትን ተማሪዎች ሳይቀር ከረብሻ የሚታደግ ነው። ምክንያቱም እንደተማሪ ረጅም ዓመት የተለፋበት ነገር የመጨረሻ ፍሬው የሚታወቀው በ12ኛ ክፍል ፈተና ሆኖ ሳለ ተሰርቆ ጎበዙ ተማሪ መና ሲቀር ያማል። ስለሆነም ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲ መፈተናቸው በብዙ መልኩ ከችግሮች የሚድኑበት እንደሆነ ይታመናል።
ፈተናውን ለምን በዩኒቨርሲቲ
የአገር አቀፍ ትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር እሸቱ ከበደ እንደሚሉት፤ ፈተናው በዩኒቨርሲቲ ውስጥ መሰጠት ያስፈለገበት ምክንያት ተማሪዎቹ ነገ ተፈትነው ሲያልፉ የሚገቡበትን ዩኒቨርሲቲ በተወሰነ ደረጃ እንዲያውቁ ይረዳል፤ ዩኒቨርሲቲዎች ደግሞ ነገ ስለምንልክላቸው ተማሪዎች እንዲያውቁ ያግዛል። እንዲሁም መንግሥት ልጆቹ ሳይረበሹ እንዲፈተኑ ጥበቃ እንዲያደርግ ይረዳዋል።
ቀደም ሲል ፈተናዎች ከሚሰጡበት ሦስት ሺህ የፈተና ጣቢያዎች ወደ 133 ዝቅ ማለታቸውን ያነሱት ኃላፊው፤ ይህ መሆኑ ፈተናዎች «አንዳንድ ሰዎች ኃላፊነትን ከመወጣት አንጻር በሚፈጥሩት ክፍተት» የነበሩ ስርቆቶችን በመቀነስ «ለፖለቲካ ፍጆታ» እንዳይውል ያግዛል። በተጨማሪም ፈተናዎች ሾልከው በመውጣታቸው የተነሳ የተሰረቁ ፈተናዎችን ጥያቄዎችና መልሶችን በስፋት ማሰራጨት እንዳይቻል የኢንተርኔት አገልግሎት እንዲሁም የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮች በፈተና ሰሞን እንዲዘጉ ይደረግ ነበር። አሁን ግን ይህ አጋጣሚ እንዳይኖር ዕድሉን ይሰጣል። የፈተና ጥያቄዎች ተሰርቀው ወጥተዋል የሚሉ መረጃዎች ወጥተው በተፈታኞች ላይ ጫና እንዳያሳርፉም ይረዳል።
ቁጥጥሩ ምን ይመስል ነበር?
የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እንዳሉት፤ ፈተናው ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ድረስ ተማሪዎች ከትምህርት ተቋማቱ መውጣት አይፈቀድላቸውም። በቦታ ውስንነት ምክንያት የማኅበራዊ እና የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪዎች በተለያዩ ጊዜያት እንደሚፈተኑም ይደረጋል። በዚህም በፈተናው ወቅት ተማሪዎች ተንቀሳቃሽ ስልኮችን ይዘው በፈተና ማዕከል ውስጥ መገኘት አይችሉም። ይህንን ተላልፈው የተገኙ ተፈታኞች ከፈተናው ይታገዳሉ። የሁለተኛ ደረጃ መልቀቂያ ፈተናን ለመውሰድ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚቆዩ ከመሆናቸው በተጨማሪ፣ ፈተናውን የሚያስፈጽሙ ፈታኞችም ከትውልድ አካባቢያቸው ውጪ ባሉ ስፍራዎች ይፈትናሉ።
በፈተና መስጫ ቦታዎችም የሚኖረው ጥበቃ በክልል ወይም በአካባቢ የፀጥታ አካላት ሳይሆን፣ ሙሉ ለሙሉ በፌዴራል ፖሊስ አማካይነት ነው። የተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ባለ የፀጥታ ችግር ምክንያት 56 ሺህ የሚጠጉ ተማሪዎች ፈተናውን በሌላ ጊዜ እንደሚወስዱ ይደረጋል። ይህ ደግሞ የተማሪውን ቁጥር ስለሚቀንሰው ለቁጥጥሩ አመቺ እንደሚሆን የጠቀሱት ፕሮፌሰር ብርሃኑ፣ ከዚህ ውጪ ባሉ ምክንያቶች ፈተናውን መውሰድ ላልቻሉ ተማሪዎች ደግሞ ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ ይሰጣል።
ፈተናና የመጀመሪያ ዙር ውጤት
ትምህርት ሚኒስቴር በሰጠው መግለጫ እንዳስቀመጠው፤ የ2014 ዓ.ም የመጀመሪያው ዙር ፈተና በታለመለት መንገድ ተከናውኖ የታለመለትን ዓላማ እንዲያሳካ ዘርፈ ብዙ አካላትን በማሳተፍ ተከናውኗል። በመጀመሪያው ዙር ተፈታኝ የሆኑት የማኅበራዊ ሳይንስ ተማሪዎች ሲሆኑ፤ ከሚጠበቁት 595ሺህ700 ተማሪዎች ውስጥ 586ሺህ541 ተማሪዎች በ133 ማዕከላት ለፈተና ቀርበዋል። ከክልሎች፣ ከተማ አስተዳደሮችና ከዩኒቨርሲቲዎች ለፈተና አስተዳደር ድጋፍ ሥራዎች የተሰማራውን የሰው ኃይል ሳይጨምር በአስፈፃሚነት እና በፀጥታ ሥራ 32ሺህ973 በየማዕከላቱ ተሰማርተዋል።
በጥቅሉ ሲታይ ፈተናው ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ በአብዛኞች የመፈተኛ ጣቢያዎች መልካም የሚባል ሂደትን አልፎ እንደተጠናቀቀ የሚያስረዳው መግለጫው፤ ተሞክሮው የመጀመሪያ እንደመሆኑ መጠን ብዙ የፈተና ሥርዓትና ደንብ ተግዳሮቶች ሊያጋጥሙ እንደሚችሉ ቢገመትም ሁለት ያልተገመቱ ክስተቶች ማጋጠማቸውን ያነሳል። በመጀመሪያው ቀን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከዋና ግቢ ወደ ቴክኖሎጂ ግቢ ያለው የመተላለፊያ ድልድይ ወድቆ በ451 ተማሪዎች ላይ የደረሰው አስደንጋጭ አደጋ ሲሆን፤ በአደጋውም 232ቀላል ጉዳት፤ 201 መካከለኛ ጉዳት፤ 13 ከፍተኛ ጉዳት፤ አምስት በጣም ከፍተኛ ጉዳት እና የአንድ ተማሪ ሕይወት ማለፍ ነው። በዚህ ድንገተኛ አደጋ ምክንያት በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ መፈተን የሚጠበቅባቸው 14ሺህ415 ተፈታኞች የመጀመሪያው ቀን ሁለት ፈተናዎች እንደዚሁም የቴክኖሎጂ ግቢ 7ሺህ350 ተፈታኞች የመጀመሪያ ቀን የጠዋት ፈተና መውሰድ አልቻሉም። እናም የመጀመሪያው ቀን ፈተና ቢስተጓጎልም በክልሉና በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር አመራሮች፤ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ አመራሮች፤ በፀጥታ አመራሮች፤ በፈተና አስፈፃሚዎችና መላው የትምህርት ማህበረሰብ እንዲሁም የከተማው ነዋሪዎች ባደረጉት ልዩ ርብርብ ተማሪዎች ከሁለተኛው ቀን ጀምሮ ያሉትን ፈተናዎች በተረጋጋ ሁኔታ እንዲወስዱ ሆነዋል። በአደጋው ምክንያት ያልተፈተኗቸውን ትምህርቶች በ2ኛው ዙር እንደሚፈተኑም አስረድቷል።
ሌላውና ሁለተኛ ብሎ ያነሳው ያልተጠ በቀው ክስተት ለፈተና ወደ ዩኒቨርሲቲ የገቡ ተማሪዎች ከትምህርት ሥርዓትባፈነገጠ መንገድ ፈተናውን እንፈተንም ብለው በገዛ ፈቃዳቸው ዩኒቨርሲቲውን ለቀው የወጡት ተማሪዎች ጉዳይ ሲሆን፤ በድርጊታቸው ብዙዎችን እንዳሳዘኑ ያስረዳበት ነው። የቤተሰቦቻቸውን ድካም ከንቱ ያስቀሩና የራሳቸውን መፃኢ ዕድል ከማምክን አልፈው በጥረታቸው ተፈትነው ውጤት ለማስመዝገብ የሚፈልጉ ተማሪዎች እንዳይፈተኑ የረበሹበት ተግባር መሆኑንም በመግለጫው አብራርቷል።
እስካሁን ባለን መረጃ መሠረት በእንደዚህ ዓይነት ተግባር ተሰማርተው ከፈተና ተገቢ ባልሆነ መንገድ ራሳቸውን ያገለሉ ተማሪዎችን በተመለከተ መቅደላ አምባ ዩኒቨርሲቲ፤ መካነሰላም ካምፓስ 1ሺህ700፤ ከደብረማርቆስ ዩኒቨርሲቲ 1ሺህ226፤ ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ 2ሺህ711፤ ከደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ 7ሺህ150 በጠቅላላው 12ሺህ787 ተማሪዎች ፈተና ሙሉ በሙሉ ወይም ውስን ፈተናዎችን በመውሰድ ጥለው ውጥተዋል። በተለይም በደብረታቦር ዩኒቨርሲቲ ተፈታኞች ኃይል በተቀላቀለበት መልኩ ሁከት በመፍጠራቸው የአንድ ተማሪ ሕይወት ሲያልፍ በፈተና አስፈጻሚዎችና በፀጥታ ኃይሎች ላይ ጉዳት መድረሱንም አስታውቋል።
ሚኒስትሩ በመግለጫው እንዳስረዳው፤ ፈተናውን ጥለው የወጡ ተማሪዎች ፈተና መፈተን እንደማይፈልጉ አሳውቀው ግቢ ለቀው የወጡ በመሆኑ በቀጣይ መፈተን አይችሉም። ሆኖም ግን ግቢውን ጥለው ባለመውጣት ቀጣይ ፈተናዎችን የወሰዱና በመሃል ከፍላጎታቸው ውጪ በሆነ መንገድ አንድ ፈተና ሳይፈተኑ የቀሩ ተማሪዎች በሚቀጥለው ዙር ፈተና የሚፈተኑ ይሆናል።
ሌሎች ያጋጠሙ ችግሮች እንደነበሩም የሚያነሳው መግለጫው፤ ከተሳተፈው ሰው ብዛት፣ ከተፈታኙ ብዛትና በዚህ መልኩ ፈተናው ሲሰጥ የመጀመሪያችን ከመሆኑ አንጻር የሚጠቅም ቢሆንም ያጋጠሙ ቁልፍ ችግሮችተብለው የሚነሱም አሉ። ከእነዚህ መካከል የመጀመሪያ የሚሆነው በቂ ኦረንቴሽን ባለማግኘት ወይም በማወቅም ጭምር የተከለከሉ ቁሶች ይዘው የመጡና ይዘው የተገኙ ተፈታኞች መኖራቸው፤ ነብሰ ጡርና እመጫት ተፈታኞች በሌላ ዙር እንደሚፈተኑ አስቀድሞ ቢገለፅም በዚህኛው ዙር ለፈተና መምጣታቸው ነው።
ሌላውና በሁለተኛ ደረጃ ሊነሳ የሚችለው ችግር በፈተና አዳራሽ ውስጥ በጋራ ካልሠራን ብለው ከፈተና አስፈጻሚዎች ጋር ግብ ግብ የፈጠሩ ተፈታኞች ማጋጠማቸው ነው። ከተሰጣቸው መመሪያና ከፈታኝ የማይጠበቅ ተግባር ላይ የተሳተፉ የፈተና አስፈፃሚዎች መኖራቸው፤ በትራንስፖርት እጥረት ምክንያት ዘግይተውና አምሽተው በዩኒቨርሲቲዎች የደረሱ አካላት መኖራቸው፤ ተማሪዎች ስልክ እንደሌላቸውና ፈተና ቢወጣ እንኳ እንደማያገኙ እየታወቀ ፈተና እንለጥፋለን የሚሉ የቴሌግራም ገፆች ማጋጠማቸውና ፈተና ካለቀ ወይም በመሰጠት ላይእያለ አንድም ሁለትም ገፅ መለጠፋቸው ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውንም ያብራራል።
እንደ መግለጫው ከሆነ፤ የተከለከሉ ነገሮችን ደብቀው ለማስገባት የሞከሩ ተማሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለው ከፈተናየተሰናበቱ ሲሆን፤ ያልተገባ ተግባር ሲፈጽሙ እጅ ከፍንጅ የተያዙ ፈታኞችም በሕግ ቁጥጥርሥር ውለው ጉዳያቸው እየታየ ይገኛል። በተጨማሪም በመፈተኛ ክፍል ውስጥ በቡድን ወይምበግል የፈተና ደንብን የተላለፉ እንዳሉ ሪፖርት የደረሰ ሲሆን፤ በሚቀርበው መረጃና ማስረጃመሠረት ፈተና እስከ መሠረዝ የሚደርሱ እርምጃዎች እንደሚኖሩም ተጠቁሟል።
በአጠቃላይ የ12ኛ ክፍል የ2014 ዓ.ም የመጀመሪያ ዙር የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪዎች ፈተና ከ586 ሺህ በላይ ተማሪዎች በ133 ማዕከላት ውስጥ እንዲፈተኑ አድርጓል። እነዚህን ችግሮችና አሠራሮች በሚገባ ማየቱ ለቀጣይ ፈተና የተሻሉ ዕድሎችን እንደሚያጎናጽፉም መግለጫው ያመላክታል። እኛም መልካም ጅማሮ መልካም ነገሮችን ያመጣልና ለተፈታኞች የላባቸውን ውጤት የሚያገኙበት እንዲሆንላቸው በመመኘት ጽሑፋችንን እንቋጭ። ሰላም!!
ጽጌረዳ ጫንያለው
አዲስ ዘመን ጥቅምት 7 ቀን 2015 ዓ.ም