በቅርቡ ከዚህ አለም በሞት የተለየው ማዲንጎ አፈወርቅ ለመጨረሻ ጊዜ ባወጣው አልበሙ ውስጥ ከተጫወታቸው ሙዚቃዎች መካከል አንዱ የሆነው ‹‹እባክሽ ታረቂኝ›› የሚለው ሙዚቃ በአድማጩ ዘንድ እጅግ ተወዳጅ ሆኖለት ነበር ።ማዲንጎ ይህን ሙዚቃ በድንቅ ሁኔታ ይጫወተው እንጂ ሙዚቃው ግን ንብረትነቱ የአንጋፋው ድምጻዊ ካሳ ተሰማ ነበር። የጠቀስነውን ሙዚቃ ጨምሮ ‹‹ፋኖ ፋኖ›› በተባለውና በሌሎች ተወዳጅ ሙዚቃዎቹ የሚታወቀው ስመ ጥሩ የክራር ተጨዋች ድምጻዊ ካሣ ተሰማ ያረፈው ከዛሬ 49 ዓመታት በፊት ጥቅምት 1 ቀን 1966 ዓም ነበር ።እኛም ወቅቱን አስታውሰን የዚህን ታላቅ ድምጻዊ ታሪክ በአጭሩ ልናስታውሰው ወደድን ።
ካሳ የካቲት 6 ቀን 1919 ዓም በሸዋ ክፍለ ሀገር መናገሻ አውራጃ ተወለደ ።ስለ አስተዳደጉ ብዙም ባይታወቅም ለአቅመ አዳም ሲደርስ ግን አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ተምሮ ተግባረ እድ ትምህርት ቤትን ተቀላቅሏል ።ካሣ ተግባረ እድ ትምህርት ቤት በ1934 ዓም የቧንቧ እና የኤሌክትሪክ ስራ ተምሮ በማጠናቀቅ የክብር ዘበኛ ሰራዊትን ተቀላቀለ ።በክብር ዘበኛ ሰራዊት ውስጥ የቧንቧ ጥገና ባለሙያ የነበረው የክራሩ ጌታ ካሣ ተሰማ፤ የቃኘው ሻለቃ ጦር ወደ ኮሪያ በዘመተ ጊዜ የምህንድስና ክፍል አባል ሆኖ አብሮ ሁለት ጊዜ ዘምቷል ።ከዚህ ዘመቻ ጋር የሚጠቀስም ታሪክ አለው ።ዘማቹ ሁሉ ወደ ጂቡቲ የሚያደርሰውን ባቡር ሞልቶ ጉዞ ሲጀምር ካሳ ክራሩን አንስቶ ዜማውንም ግጥሙንም እዚያው በመፍጠር ‹‹እልም አለ ባቡሩ፣ እልም አለ ባቡሩ፤ ወጣት ይዞ በሙሉ…›› እያለ ተጓዡን አዝናንቷል። በሙዚቃው በኩል በኮሪያ ልሳነ ምድር ላሳየው ጀግንነት የቀዳማዊ ኃይለስላሴ የብሄራዊ አገልግሎት የወርቅ ሜዳሊያ ነሀሴ 19 ቀን 1948 ዓም ተሸልሟል ።በአንድ ወቅት በተማረበት የቧንቧ ስራ በቤተ መንግስት ውስጥ ተቀጥሮ በመስራት ላይ ሳለ የእጅ ሰአቱ ተሰበረ፤ ይህንን የተመለከቱት ልዑል አልጋ ወራሽ አስፋ ወሰን የራሳቸዉን የእጅ ሰዓት አውልቀዉ ሰጥተውታል ይባላል ።
በ1949ዓም ካሳ ከክቡር ዘበኛ የምህንድስና ክፍል ወደ ሙዚቃ ቡድኑ ተቀላቅሏል ።በወቅቱ ከጦሩ የተለያዩ ክፍሎች ከካሳ በተጨማሪ ተዘራ ኋይለ ሚካኤል፣ አየለ ማሞ፣ ተፈራ ካሳ እና ሌሎችም ተሰባሰቡ ።ከሲቪሉ ደግሞ እነ ጥላሁን ገሰሰ እና ብዙነሽ በቀለ ገቡ ።ይህ ወቅትም የኢትዮጵያ ሙዚቃ ታሪካዊ የሆነ እመርታ ያሳየበት ወቅት ሆነ ።የክብር ዘበኛ የሙዚቃ ቡድን አባል የነበሩት አቶ ዘውገ ገብረ መድህን በአንድ ወቅት የሙዚቃ ሰዎች እና ስራዎቻቸው በተሰኘ ኢትዮጵያ ሬድዮ ፕሮግራም ላይ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ “በወፍራም ድምጽ ካሳ ተሰማን ማንም አያክለውም” ብለዋል ።አክለውም ”ሙዚቃ ላይ ባሪቶን የሚባል የድምጽ አይነት አለ ።በጣም ወፍራም ድምጽ ነው ።የአንበሳ ድምጽ ነው ።የካሳ ድምጽ እሱ ነው። በዚህ ወፍራም ድምጽ ሲጫወት ተዓምር ነው” በማለት የድምጹን ነጎድጓዳዊ ውበት አድንቀዋል ።ከካሳ ጋር አብረው የሰሩት አንጋፋው አርቲስት ተስፋዬ ሳህሉ ደግሞ የካሳ ድምጽ አዘፋፈን “ውስጥን ይነካል ይቀሰቅሳል” ይላሉ ።
ካሳ ከነበሩት አስገራሚ ባህሪዎቹ ውስጥ መድረክ ላይ ሙዚቃ ተጫዉቶ ሲያበቃ የተጫወተበትን ክራር የመስበሩ ነገር ነበር ።በዚህም ባህሪዉ የተነሳ ኢትዮጵያዊው ጂሚ ሄንድሪክስ የሚል ቅጽል አግኝቶ ነበር ።ጂሚ ሄንድሪክስ እዉቅ የሮክ የሙዚቃ ስልት ተጫዋች ሲሆን መድረክ ላይ ሙዚቃ ተጫዉቶ ሲያበቃ የተጫወተበትን ጊታር በመሰባበር ይታወቃል ።
ሁሉንም ግጥሞቹን እና ዜማዎቹን ራሱ የጻፈው ድምጻዊ ካሳ በወፍራም ድምጹ ካንጎራጎራቸው ሙዚቃዎቹ መካከል ‹‹ብርቱካኔ››፣ ‹‹እባክሽ ታረቂኝ››፣ ‹‹ሸግዬ›› … የሚሉት ይጠቀሳሉ ።በነጎድጓዳዊ ድምጹ ለስላሳ እና ጣፋጭ ነገር ግን ልብን ሰርሳሪ ሙዚቃዎችን የተጫወተው ካሳ በሙዚቃው ብዙዎችን አሸንፎ ነበር ። እንዲያውም የክብር ዘበኛ ሰራዊት ዋና አዛዥ እንዲሁም የ1953ዓም የመንግስት ግልበጣ ሙከራ መሪ የነበሩት ብርጋዴር ጀኔራል መንግስቱ ነዋይ ሁልጊዜም ማታ ማታ የካሳን የክራር እንጉርጉሮ ካልሰሙ እንቅልፍ እንደማይወስዳችው በቅርብ የሚያውቋችው ሰዎች ተናግረዋል ።ሰዎች ለእሱ ሙዚቃ እንደዛ ይሁኑ እንጂ ካሳ ሙዚቀኛ እሆናለሁ ብሎ አያምንም ነበር ።በ1963 ዓም ባደረገው ቃለ መጠይቅ “በወቅቱ ሰዎች ያ እኮ ነው እልም አለ ባቡሩ ብሎ የዘፈነው አዝማሪ እያሉ ሲያነሳሱኝ እኔ ግን ራሴን እንደ ወታደር እንጂ እንደ ሙዚቀኛ ስለማላይ ምንም አይመስለኝም ነበር” ብሎ ነበር ።
የሚያውቁት ካሳ የዋህ ነው ይላሉ ።ከዚህም ባለፈ በሴቶች ዘንድ ተወዳጅ ነበር ።ከብዙ ሴቶች ጋር በተያያዘም ስሙ ይነሳ ስለነበር ጉም ጉም የሚል ሙዚቃ ተጫውቷል ።መዝናናትን ፤ ውስኪን እና ላቭ ስትራይክ የተባለ ሲጋራን ይወድ ነበር የሚባለው ካሳ መዝናናትን ይውደድ እንጂ በስራው ላይ ግን ቆፍጣና ነበርም ይላሉ። በባህሪው ደግ እና ሩህሩህ የነበረው ካሳ፤ እጅግ በጣም የሚወዳቸው ወላጅ እናቱ ሲሞቱ በድንጋጤ ለአንድ ወር ያህል አማኑኤል ሆስፒታል ገብቶ ነበር ።ከ2 ጊዜ ትዳር 8 ልጅ የወለደው ካሳ ከዚህ ዓለም በሞት ሲለይ እድሜው 47 ዓመት ነበር ።
ታዋቂው ደራሲ እና ጋዜጠኛ ብርሀኑ ዘሪሁን ከካሳ ሞት በኋላ ጥቅምት 9 ቀን 1966 ዓ.ም የከርታታ ነፍሴ ምሳሌ በሚል ርእስ ባሰፈረው ጽሁፍ ስለ ካሳ ፤ ስለ ክራሩ እና ስለ ሙዚቃው የሚከተለውን ብሏል ።የካሳ እንጉርጉሮ ደስታ ለደስታ በደስታ ያለመሆኑ ባህርይ ከዚያ ላይ ይመስለኛል ። “ ካሳ በክራሩ ቅኝት በወጣትነት ያለምነውን የተስፋ የፍቅር የምኞት መሟላት አለም ፍለጋ ነፍሱን ይልካታል ።ትሄዳለች ተንከራታ ወደዚህ ሸካራ ዓለም ትመለሳለች ።ቅኝቱ ሲቆም ነፍሱና እርሱ የወደቀ ፍቅር የተሰበረ ተስፋ የተሰናከለ ዓለምና ምኞት በሰፈነበት ግዙፍ ዓለም ውስጥ ናቸው። ነፍሱ ትቅበጠበጣለች ።ተበሳጭቶ ክራሩን ይሰብረዋል። ተገንዝበን እንደሆነ የካሳን ክራር እንጉርጉሮ ስንሰማ ደስታና ፈንጠዝያ የማይሰማን በዚህ ምክንያት ይመስለኛል ።ዘብረቅረቅ ያለ ዘፈን ሰምተን ጨፍረን ደንሰን እንደምንረካው አይነት አይደለም ። የካሳ ክራር ስሜት የትካዜና የመጽናናት መካከል መመሰጥ ነው ። ”ብሏል ።
ድምጻዊ ካሳ ተሰማ፤
ደራሲው ፍቅሩ ኪዳኔ
ታዋቂው የስፖርት ጋዜጠኛ እና የስፖርት ሰው ፍቅሩ ኪዳኔ በዚህ ሳምንት አርፈዋል ።ስርአተ ቀብራቸውም በዛሬው ዕለት በኖሩባት ፈረንሳይ እንደሚከናወን ተነግሯል ።ፍቅሩ በስፖርቱ ረገድ በጣም ታዋቂ ሰው የነበሩ ቢሆንም ከስፖርቱ ጎን ለጎን ደራሲም ናቸው ።ሁለት መጻህፍትን ደርሰዋል ።አንደኛው ከስፖርት ጋር በተያያዘ የጻፉት “የስፖርት ጨዋነት ምንጮች” የተሰኘ መጽሀፍ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ዝናን ያተረፈላቸው “የፒያሳ ልጅ” የተሰኘው መጽሀፋቸው ነው ።በዚህ መጽሀፍ ፍቅሩ በዘመናቸው የነበረችውን ፒያሳ እና አዲስ አበባ አስቃኝተውናል ።ዛሬም በዚህ ጽሁፍ ከዚህ መጽሀፍ ላይ የተወሰኑ ገጾችን አብረን እናነብባለን ።
የፒያሳ ልጅ ከፍቅሩ ኪዳኔ ዘብሄረ ጉለሌ – ፒያሳ – አዲስ አበባ – ሸዋ – ኢትዮጵያ – አፍሪካ – ዓለም ።
ጉለሌ … በኛ ዘመን ማዘጋጃ ቤት የቀየሰልን ቀበሌ ስላልነበር ከአቡነ ጴጥሮስ አንስቶ በአዲስ አበባ ከተማ በቅድሚያ የተሰራውን አስፋልቱን ጎዳና ተከትሎ እስከ ገፈርሳ ያለውን ጉለሌ ነበር የምንለው ።አስፋልቱ የሚያቆመው አዲስ ዓለም ሆለታ መናገሻ ይሆናል ተብሎ የታሰበው የአጼ ምኒልክ ቤተ መንግስት የተሰራበት ድረስ ነው ።አልፎ አልፎም የመስፍን ሀረር መንገድንና አርበኞች መንገድን በማገጣጠም የወይዘሮ አሰለፈች ሰፈር፣ ገዳም ሰፈር፣ ጣልያን ሰፈር፣ አባኮራን ሰፈር በማቀላቀል የጉለሌን ግዛት አስፍተነዋል ።የጉለሌ ዋና ምልክት ጣልያኖች የሰሩት የራስ ደስታ ዳምጠው ሆስፒታል ሀኪም ቦራ ነበር ።
በኢትዮጵያ ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ በአሳንሰር ወይም ሊፍት የተሳፈርን የጉለሌ ልጆች ነን ።ምክንያቱም ዘመናዊ አሳንሰር በሀገሪቱ ውስጥ የነበረው ራስ ደስታ ሆስፒታል እኛው ሰፈር ብቻ ስለነበር ነው ።በዚሀም የተነሳ በ7 ወይም 12 ሰዓት ላይ ልክ በሽተኛ እንደሚጠይቅ ሰው ዘው ብለን ሆስፒታል ገብተን ሁለት ወይ ሶሰት ጊዜ አንዷን ፎቅ ወጣ ወረድ ብለን ዞር ማለት ነው ። የሆስፒታሉ ሽታ ደስ ስለማይል ነው እንጂ በቆየን ነበር ።ትልልቆቹ ደፍረው ስለማይሳፈሩት በሊፍቱ የምንጠቀመው እኛና በሽተኞቹ ብቻ ሳንሆን አንቀርም ።ፈረንጅ የሰራው ትልቅ ፎቅ ቤት ውስጥም የገባነው እዚሁ ሆስፒታሉ ሰለነበር ያላየነው ጉድ የለም ።
በሚሽከረክርና ከፍ ዝቅ የሚል አልጋ የብርድ ልብሱ ዓይነት የመጸዳጃ እቃዎች ሁሉም ነገር ለእኛ ብርቅ ነው ።የተወለድኩት ፍልውሀ ሆስፒታል ቢሆንም ለመጀመሪያ ጊዜ ሀኪም ያየሁት ፤ ያውም የፈረንጅ ሀኪም ፤ ውሻ ነክሶኝ ለመታከም ሄጄ ነው ።ጠባሳዬም እስካሁን አለች። ሁለተኛውም ለፈንጣጣ ክትባት ነው። አሁን ግን የማላየው የሀኪም አይነት የለም ።ራስ ደስታ ሆስፒታል አጠገብ ጣልያኖች ሊሰሩት ጀምረው የነበረው የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ቦታ የጨርቅ ኳስ መጫወቻችን ነበር። ልክ ከጀርባው የአባቴ ወዳጆች የአቶ ተፈራ ፈይሳ እና ወይዘሮ አሸነፈች ሀብተሚካኤል ፤ የክርስትና አባቴ የአቶ ታደሰ ሀብተሚካኤል ፤ ወይዘሮ ሰናይት ዋቅሊቶ እና የአቶ ከበደ ሩፋኤል ቤተሰቦች ኖረዋል ።አሁን ቤተ ክርስቲያኑ ተሰርቶ ለሰይፉ ግርማ ሰጥቶታል ።
ሁለተኛ መጫወቻ ሜዳችን ከሆስፒታሉ ፊት ለፊት ከሚገኘው የአፈ ንጉስ ቅጣው ይታጠቁ የሳንጆርጅ ተጫዋች የነበረው አብሮ አደጌ ያየህይራድ አባት ቦታ ላይ ነው ።ከሆስፒታሉ ግራና ቀኝ አርበኞች እና የስዊድን ሚሽን ትምህርት ቤቶች ሲገኙ ከጠላት በፊት የጣልያን ኮንሶላቶ ትምህርት ቤት እዚያው ጉለሌ ነበር ።ከካቶሎክ ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊት የግሪክ ክለብ ፤ ኦሎምፒያኮስ የቅርጫት ኳስ እና የእግር ኳስ መጫወቻዎች ነበሩ። የክለቡ ዘበኛ አንዳንዴም ኳስ እንድንጫወት የሚፈቅዱልን የድምጻዊ አርቲስት የመሀሙድ አህመድ አባት ናቸው። የግሪክ ባስኬት ቦል እና ፉትቦል ውድድር አልፎ አልፎም የትግል ውድድር ሲዘጋጅ አያመልጠንም።
ትንሽ ፈቀቅ ብሎ የመምህራን ማሰልጠኛ እና የፖሊስ አባዲና አካዳሚ ትምህርት ቤቶች ነበሩ ።ትንሽ ራቅ ብሎም የባላባት ብሎም በኋላ መድሀኒዓለም ቀጥሎም ጄነራል ዊንጌት ትምህርት ቤቶች ስለነበሩ ወጣት ተማሪ የሞላበት ሰፈር ስለመሆኑ እንዳይረሳ ።ድሮ ጣልያኖች የሰሩት የዶክተር ላምቢ ግቢ ዝነኛ የሆነው ለፈረንሳይ ኢንስቲትዩት ፓስተር የበሽጻ ኒክሮቦች አጥኚ እና ምርምር ድርጅት ተሰጥቶ ከሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤት የተመለመሉ የላብራቶር ቴክኒሻን ሰልጥነውበታል። እንደዚሁም የአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት የጂኦሜትሪዎች ትምህርት ቤት አቋቁሞ የእኛ ጓደኞች አሰፋ ተሰማ እና ወርቅነህ ገብሬ ተመርቀውበታል ።
ጋሽ ፍቅሩ በዚህ መጽሀፋቸው በወቅቱ የነበረችውን አዲስ አበባ እንዲህ እንዲህ እያሉ እያስቃኙን የሚቀጥሉ ሲሆን አጻጻፋቸው ምስል ከሳች እና አዝናኝ በመሆኑ እንድታነቡት እንጋብዛለን ።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ጥቅምት 6 ቀን 2015 ዓ.ም