የጥላሁን ገሰሰን የዘንባባ ማር ነሽ፣ አምሳሉ፣ የሕይወቴ ሕይወት፣ የምግብ አይነቶች፣ ከመሞት አልድንም፤ የመሀሙድ አህመድን አላወቅሽልኝም፣ እንዴት ይረሳል፤ የብዙነሽ በቀለን ወጣት ሳለሁ፣ የፍቅር መጠኑ የተሰኙ ሙዚቃዎች ስንሰማ አንድ ጥያቄ መሰንዘራችን አይቀርም። ‹‹ማን ይሆን የነዚህ ጣፋጭ ዜማዎች የፈጠራ አባት?›› መልሱ ሻለቃ ግርማይ ሀድጉ ናቸው።
ከ1950ዎቹ ጀምሮ እስከ 1970ዎቹ መጀመሪያ ያለው ጊዜ ለኢትዮጵያ ሙዚቃ ወርቃማ ዘመን እንደነበር ይነገራል። ለዚህ ወርቃማ ዘመን የሙዚቃ እድገት አስተዋጽኦ ካደረጉት መካከል ደግሞ ወታደራዊ ባንዶች ቀዳሚውን ስፍራ ይይዛሉ። እንዳለመታደል ሆኖ ስለዚህ ዘመን ሙዚቃ ሲነሳ በአብዛኛው ስማቸው የሚነሳው ድምጻውያኑ ብቻ ናቸው። ግጥም ደራሲዎቹ፣ ዜማ ቀማሪዎቹ፣ የሙዚቃ መሳሪያ ተጫዋቾቹ፣ አቀናባሪዎቹ ወዘተ…ካደረጉት የጎላ አስተዋጽኦ አንጻር የሰጠናቸው ቦታ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም። ዛሬም ብዙም ካላሞገስናቸው ነገር ግን የሙዚቃ ጠቢባን መካከል አንዱ የሆኑትን ሻለቃ ግርማይ ሀድጉን በአጭሩ እናስታውሳለን።
ሻለቃ ግርማይ ሀድጉ ተወልዶ ያደገው በኤርትራዋ ከተማ አስመራ ልዩ ስሙ ግዛ ከንሻ ከሚባል ስፍራ ነው። ወቅቱም በፈረንጆቹ ኅዳር 8 ቀን 1928 ነው። እናትና አባቱ የአስመራ ወንጌላዊያን ሚሲዮን ተማሪዎች ነበሩ። በጊዜው በጣልያን ቅኝ ግዛት ስር በነበረቸው ኤርትራ የተወለደው ግርማይ በልጅነቱ ጥቂት የግእዝ ትምህርት ተምሮ ነው እድሜው 7 አመት ሲደርስ ወደ አንደኛ ትምህርት ያቀናው። በወቅቱ ጣልያኖቹ ለኤርትራውያኑ ይሰጡት የነበረው ትምህርት የቅኝ ግዛታቸውን ለማጠናከር የሚረዳም ነበር። ህጻናቱ በየቀኑ መንግስታቸው ጣልያን ንጉሳቸው ደግሞ ቪክቶር ኢማኑኤል እንደሆነ ይነገራቸው ነበር። በኋላም ጣልያን ኢትዮጵያን ወርራ ከኤርትራ ጋር በመጠቅለል አፍሪካ ኦሪየንታል ኢታሊያና ስትል የምስራቅ አፍሪካ ግዛቷን አወጀች።
ከልጅነቱ ጀምሮ የቅኝ ግዛትን ገፈት የቀመሰው ወጣቱ ግርማይም የኢትዮጵያና የኤርትራን መዋሀድ የሚያቀነቅነው የሀገር ፍቅር ማህበር ሲቋቋም የማህበሩን አላማ ደግፈው ከተቀላቀሉ የኤርትራ ተወላጆች መካከል አንዱ ነበር። ያኔ ወደ ፖለቲካ ሲገባ ገና እድሜው 19 ገደማ ሲሆን፤ በዚህ ማህበር ውስጥ የግርማይ ሀድጉ እንቅስቃሴ ጠንካራ ነበር። ግርማይ “አንድ ኢትዮጵያ” የሚለውን መፈክር አንግቦ የተለያዩ የፕሮፓጋንዳ ስራዎችን ከመስራትም ባሻገር ሰልፎችን በማስተባበር በራሪ ወረቀቶችን በመበተንና ጋዜጦች ላይ ጽሁፎችን በመጻፍ የአንድነት አቀንቃኝነቱን በግልጽ አስመስክሯል።
ታዲያ ይህ የግርማይ እንቅስቃሴ ሕይወቱንም ሊያስከፍል የሚችል አደጋን ያስከተለ ነበር። ገና የ19 አመት ወጣት ሳለ የሁለቱን አገራት ውህደት ይቃወሙ በነበሩ አካላት የግድያ ሙከራ የተደረገበት ግርማይ ቤተሰቦቹን አስመራ ጥሎ ከሶሰት ቀናት አድካሚ ጉዞ በኋላ ሸሽቶ የወንድሙን ማንዶሊን ይዞ አዲስ አበባ ገባ። በወቅቱ እንዴት ወደ አዲስ አበባ እንደገባ ሲናገርም “አንድ ግሪካዊ ነበር ጨው ነጋዴ። እሱ ጨው ጭኖ ወደ አዲስ አበባ ሲሄድ በመኪናው ላይ ተጭነን እንዳንወድቅ አንድ እጃችን ታስሮ ወደ አዲሰ አበባ መጣን” በማለት ከሶስት ቀናት ጉዞ በኋላ አዲስ አበባ መግባቱን ይገልጻል። በወቅቱ ከተማዋን በፎቶ ብቻ የሚያውቃት ግርማይ አዲስ አበባ ደርሶ አራት ኪሎ መሀል ላይ ሰዎች ሽንታቸውን ሲሸኑ ሲያይ ‘’ይቺማ አዲስ አበባ አይደለችም ከመኪናም አልወርድም’’ ብሎ አስቸግሮ ነበር።
አዲስ አበባ ግርማይ አክስቱ ልጅ ቤት ጥቂት ከተቀመጠ በኋላ የመጀመሪያ ሙከራ ያደረገው ደብረ ዘይት ወደሚገኘው የአየር ኃይል ለመቀላቀል ነበር። ወደ ደብረ ዘይት አካሄዱም ታሪካዊ ነው። ከመሀል ፒያሳ ተነስተው በቸርችል ጎዳና፤ ለገሀር አድርገው ያኔ ጫካ የነበረው ነፋስ ስልክ ሲደርሱ አንድ ሰው ደብረ ዘይት ሩቅ እንደሆነ እና በመኪና ካልሆነ በእግር ሩቅ እንደሆነ ነግሯቸው የተመለሱበት እና ለሶስት ቀናት የታመመበት ታሪክ አስቂኝ ነበር። የደብረ ዘይቱ ነገር ሳይሳካለት ሲቀር ደግሞ ስዊድኖች ያስተዳድሩት በነበረው የመካነ ኢየሱስ ወንጌላውያን ቤተ ክርስቲያን በወር ሶስት ብር ክፍያ በአዳሪነት ተመዘገበ። በዚህም ከሁለት ወራት በላይ መቆየት አልቻለም። በሰው ጥቆማ በ1942 ዓ.ም የካዴት ኮርስ ስልጠና ምልመላ መኖሩን ከጎረቤት የሰማው ግርማይ የክቡር ዘበኛን ተቀላቀለ። ይህም ታሪኩ
አስገራሚ ነበር። እዚያው ያረፉበት ቤት አጠገብ የሚኖር አንድን ልጅ ግርማይ እንግሊዝኛ ቋንቋ ያስተምረው ነበር። ልጁም ግርማይን አማርኛ ያስተምረው ነበር። ከዚያም ያ ልጅ አንድ ቀን ለግርማይ መልክእት ይልክለታል ”አንተ ባስተማርከኝ የእንግሊዝኛ ትምህርት የተነሳ የትምህርት እድል አግኝቼ እየተማርኩ ነውና መጥተህ ጎብኘኝ” የሚል መልእክት ደረሰው። ግርማይ ቤላ ወደሚገኘው የመኮንኖች ማሰልጠኛ በመሄድ ልጁን ይጎበኝና ሲጫወቱ ይውላሉ። አመሻሽ ላይ ሰዓት ደርሶ ግርማይ ወደቤቱ ሊሄድ ሲነሳ ግን ጥበቃው ሰዓት አልፏል መውጣት አይቻልም ይለዋል። ይህች አጋጣሚም ግርማይ ወደ ውትድርናው ዓለም እንዲቀላቀል በር ከፈተለት።
ግርማይ የክብር ዘበኛን በተቀላቀለ ሰሞን የኮሪያ ልሳነ ምድር በጦርነት ይናጥ ጀመር። ይህን ጦርነት ከደቡብ ኮሪያ ጎን ተሰልፎ ኮሚኒስት ሰሜን ኮሪያን ለመዋጋት በተባበሩት መንግስታት በኩል ከተሰለፈው ሀይል መካከል አንዱ የኢትዮጵያው ቃኘው ሻለቃ ነበር። የመጀመሪያው የቃኘው ሻለቃ ቡድን ንጉሰ ነገስቱ በተገኙበት በጃንሜዳ የሞቀ ሽኝት ሲደረግለትና ከጃንሆይ እጅ የአደራ ሰንደቅ አላማ ሲቀበልም ግርማይ ከዘማች ወታደሮቹ መካከል
አንዱ ነበር። ሊያውም ከነማንዶሊኑ። ከ21 ቀናት ጉዞ በኋላም በጄነራል አማን አምዶም መሪነት ግርማይ እና ጓዶቹ ደቡብ ኮሪያ ደረሱ።
በኮሪያ የሰራዊቱን ናፍቆት በማስታገስ በኩል ግርማይ እና ማንዶሊኑ ትልቅ ድርሻ ነበራቸው። በኮሪያ የአንድ አመት ከመንፈቅ ቆይታውን በእረፍት ጊዜው ማንዶሊኑን እየተጫወተ ነበር ያሳለፈው። ማንዶሊኗ በእርግጥ መጀመሪያ የግርማይ ሳትሆን የወንድማቸው ነበረች። የጣልያኖች ትምህርት ቤት ተማሪ የነበረው ወንድሙ በትምህርቱ ጎበዝ ስለነበር በሽልማት መልክ ከጣልያኗ ኔፕልስ መጥቶ የተበረከተለት ስጦታም ነበር። ነገር ግን ወንድምየው በስራ ምክንያት ማንዶሊኗን ብዙ ስለማይጠቀማት በማንዶሊኗ የመጫወት እድል የግርማይ ሆነ። ጎበዝ ተጫዋችም ሆነ። የግርማይ የሙዚቃ ሕይወት ጅማሬም ከዚህ የሚመነጭ ነው። በኮሪያ ዘመቻው ጊዜ በወታደሩ ዘንድ ተወዳጅ የነበረችው በሽንብራ ዱቤ የተሰኘች ሙዚቃ የሚጫወቱት በዚህች መሳሪያ ነበር። ግርማይ በማንዶሊን ሙዚቃን ይጀምር እንጂ በራሱ ጥረት ፒያኖ እና ሌሎችን መሳሪያዎችንም መጫወትን ተማረ። ይህም የሙዚቃ ግንዛቤው ከጊዜ ወደ ጊዜ ከፍ እንዲል ረድቶታል።
ከኮሪያ መልስ ለግርማይ የተሰጠው ስራ የወታደሩን ክበብ መምራት ነበር። ግርማይ ግን የሙዚቃ ችሎታውን የሚሳድግበትን መንገድ እየፈለለገ ስለነበር በተሰጠው ሀላፊነት ደስተኛ አልነበረም። ግርማይ ሀላፊነቱን በአግባቡ ባለመወጣቱ በተፈጠረ የንብረት ብክነት ምክንያት ክበቡ በመክሰሩ በብዙ ሺ ብር እዳ ተከስሶ ቢታሰርም እስሩ ለእርሱ በረከተ መርገም ነበር የሆነለት። ምክንያቱም የሙዚቃ ችሎታውን እንደ ልቡ የሚያዳብርት ጊዜ አገኘ። ከመኮንኖች ክበብ ቤተ መጻህፍት የሙዚቃ መጻህፍትን ተውሶ ማጥናት እና ዜማ ማዘጋጀትም ያዘ። የተለያዩ ዜማዎችንም እስር ቤት ሳለ መድረስ ችሎ ነበር። ከወራት እስር በኋላ ለክብር ዘበኛም ራሱ እንግዳ የነበረው እና ግርማ ያዘጋጀውን ባለ ኖታ የሙዚቃ ድርሰት ለሙዚቃ ክፍል ሀላፊዎች አቀረበ።
የሙዚቃ ችሎታው ያስደመማቸው የክቡር ዘበኛ ባንድ ሰዎች ግርማይ ቀን ቀን አብሯቸው እንዲሰራ ማታ ማታም ወደ እስር ቤቱ እንዲመለስ ፈቀዱለት። በክቡር ዘበኛ ባንድ ውስጥ እነ ኮሎኔል ሳህሌ ደጋጎን የመሰሉ የሙዚቃ ሊቃውንትን ያገኘው ግርማይ የሙዚቃ እውቀቱን የበለጠ እንዲዳብርም በር ከፈተለት። ከዚህም በላይ ግን ይህ አጋጣሚ ግርማይ አንድም ከፊል ነጻነትን እንዲያገኝ ሲያደርግ በሌላ በኩል ደግሞ የ7 ልጆች እናት የሆነችለትን ባለቤቱን ወይዘሮ ጥሩነሽ ይመርን አገኘ።
ግርማይ ከእስር ቤት ወደ ክብር ዘበኛ እየተመላለሰ የሰራበት ያ አጋጣሚ በግሉ ትዳሩን እንዲያገኝ ከማድረጉም በላይ አጋጣሚው ግርማይ በኢትዮጵያ ወርቃማ የሙዚቃ ዘመን ውስጥ አንዱ ወርቅ መሆኑን ያስመሰከረባቸውን ግሩም ስራዎች እንዲያመነጭ አድርጎታል። ወቅቱ እነ ግርማይ እና ኮሎኔል ሳህሌ ደጋጎ የኢትዮጵያን ሙዚቃ ወደ ዘመናዊ ሙዚቃ ያሻገሩበት ነበር። የግርማይ አሻራ ካለፈባቸው ስራዎች መሀከል የጥላሁን ገሰሰ አቋቋምሽማ፣ ኧረ ምን ይሻለኛል፣ ብሞትም አትርሺኝ፣ እኔ ያላንቺ አልኖርም፣ ፍሬው ያማረ ዘር፣ ከመሞት አልድንም፣ ኡኡታ አያስከፋም፣ ትዝ ትዝ እያለኝ፣ የዘንባባ ማር ነሽ እና ሌሎችም። ከብዙነሽ በቀለም ወጣት ሳለሁ፣ የፍቅር መጠኑ፣ የመሀሙድ አህመድን አላወቅሽልኝም፣ እንዴት ይረሳል፣ አቅምን አውቆ መኖር ጥሩ ነው ተጠቃሽ ናቸው።
ያልተሳካው የታኅሳስ 1953 ዓ.ም መፈንቅለ መንግስት ሙከራ የክብር ዘበኛን ክብር እና ሞገስ በአንዴ እንዲጠፋ አረገው። ብዙ የክብር ዘበኛ አባላት ለእስር እና ለእንግልት ሲዳረጉ ግርማይን ጨምሮ ለደህንነታቸው የሰጉ ብዙዎች ደግሞ ህቡእ ገቡ። ግርማይ በህመም ምክንያት በ1960ዎቹ አጋማሽ የክብር ዘበኛ በይፋ ከተሰናበተ በኋላ በደርግ የስልጣን ዘመን ለተወሰኑ አመታት በሀገር ፍቅር እና ብሄራዊ ቴአትር ሰርቷል። በዚህ ወቅትም ከሰራቸው ስራዎች መካከል የመልካሙ ተበጀን የልቤን አዳራሽ ሙዚቃ ዜማ ደርሷል። የደርግን መምጣት ተከትሎ ግርማይ ሙዚቃውን ትቶ መንፈሳዊ ኑሮው ላይ አተኮረ። እዚያም ግን በርካታ መንፈሳዊ ዝማሬዎችን ከማበርከት አልሰነፈም ነበር። ከብዙ ዘመናት በኋላ ወደ ኤርትራ ለእናቱ ቀብር ከተመለሰ በኋላም የተወሰኑ አመታትን በኤርትራ የቆየው ግርማይ ኤርትራ አገር ስትሆን የመጀመሪያውን ብሄራዊ ኦርኬስትራ በማቋቋምም አግዟል። ከዚያ ወዲያም በ2010 በ90 አመት እድሜ ሕይወቱ እስኪያርፍ ድረስ ለሶስት አስርት አመታት ገደማ ወደኖረባት አሜሪካ አገር ተሰደደ። ግርማይ የወርቃማው የኢትዮጵያ ዘመን ወርቃማ ከያኒ ነበር።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን መስከረመ 29/2015