በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ1985 / በእኛ አቆጣጠር 1977 ዓም አካባቢ ይመስለኛል/ ኢትዮጵያ ውስጥ በተከሰተ ከፍተኛ ድርቅ አያሌ ኢትዮጵያውያን ለረሃብ አደጋ ተጋልጠው ነበር፡፡ ህብረተሰቡን ድርቁ ሊያስከትል ከሚችለው ረሃብና የመሳሰሉት አደጋዎች ለመታደግ ታዲያ አንድ ግዙፍ የተባለ አለም አቀፍ የእርዳታ ማሰባሰብ ኮንሰርት በተዋቂው አይርላንዳዊ አርቲስት ሰር ቦብ ጌልዶፍ አስተባባሪነት ተካሄደ፡፡ በአዚህም ዝግጅት በርካታ የአለም ሀገሮችና ቁጥር ስፍር የሌላቸው/ ካውንትለስ ይላቸዋል መረጃው/ ለጋሾች እንደተሳተፉበትም ዘገባዎች ያመለክታሉ፡፡ በእርዳታ ማሰባሰቡም 100 ሚሊየን ዩሮ ወይም 136 ቢሊየን ዶላር ተገኝቷል፡፡
በፈረንጆቹ ሜይ 11 ቀን 2010 በወጣ የጀርመኑ መገናኛ ብዙሃን ጆቼወሌ ዘገባ ላይ እንደተጠቆመው፤ አሸበሪው ትህነግ ይህን ገንዘብ በወቅቱ የትግራይ እርዳታ ድርጅት በሚል ይጠራ ለነበረውና የቡድኑ አንድ ክንፍ ለሆነው ማረት ለተባለ ድርጅት ባልተገባ መንገድ ገቢ እንዲሆን ያደርጋል፤ ቡድኑ ከዚህ ገንዘብ የተወሰነውን ለጦር መሳሪያ መግዣ እንዳወለውም በስደት በውጭ ሀገሮች ይኖሩ የነበሩ የቀድሞ የትህነግ አባላት አጋልጠዋል፡፡ በእርዳታ የተለገሰው ስንዴ እንዴት ተደርጎ እንደተሸጠ ጭምር እነዚህ የፓርቲው የቀድሞ አባላት ማጋለጣቸውን መረጃው ይጠቁማል፡፡
ይህን መረጃም አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን በስፋት ተቀባብለውታል፤ ሲአይኤ ጭምር ህወሓት የምእራባውያኑን የእርዳታ ገንዘብ ላልተገባ ተግባር አውሎታል በሚል ሪፓርት አቅርቦበትም አንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
አሸበሪው ትህነግ በወቅቱ ከደርግ ጋር ይዋጋ ነበርና እርዳታውን ለተራበው የትግራይ ህዝብ በቀጥታ ከማድረስ ይልቅ ያደረገው የተወሰነውን ገንዘብ ለጦር መሳሪያ መግዣ አዋለው፤ ትልቅ ቅሌት፡፡ አሁንም ማስ ማስ ፣ ገለጥ ገለጥ ላደረገ የቡድኑ ቅሌት ከዚያም ቀደም ብሎ ሊጀመር እንደሚችል መገመት አያዳግትም፤ የቡድኑ ነውር በረሃብ ለተጠቁ ኢትዮጵያውያን አለም የለገሰውን እርዳታ ለጦር መሳሪያ መግዣ ካወለበት ከዚህ አሳፋሪ ተግባሩ እንደሚጀምር ይዘን ስለማንነቱ መግለጽ ይቻላል፡፡
እወክልሃለሁ ያሉትን ህዝብ ህይወት ለረሃብ አጋልጦ በእርዳታ በተሰበሰበ ገንዘብ ሌላ የሞት ድግስ ለማውጣት የጦር መሳሪያ ከመግዛት በላይ ወንጀል የለም፡፡ የስንቱን የትግራይ ህዝብ ህይወት ከሞት አፋፍ ሊመልስ የሚችል እርዳታ ነው ሀገርን ለመውጊያ የሚውል መሳሪያ መግዣ የዋለው፡፡
የመንግስት ምንአልባትም የአለም አቀፉ ማህበረሰብ የሰብአዊ እርዳታና በእዚህ ላይ ያለ አመለካከት ትርጉም ጤነኛ ነው፡፡ ቃሉ እንደሚገልጸው ማለት ነው፡፡ የአሸባሪው በድን የሰብአዊ እርዳታና በእዚህ ላይ ያለው አመለካከት ትርጉም ግን ከዚህም ይዘላል፡፡
አሸበሪው ትህነግ በትግራይ ህዝብ ዘንድ ከዘራቸው አሜኬላዎች አንዱ ‹‹እርዳታ›› እና እሱ ላይ የተመሰረተው አመለካከት ነው፡፡ ይህ የጦርነት አባዜ የተጠናነው ቡድን ጦርነቱን ሁሉ ከእርዳታ ጋር ያስተሳሰረ ነው፡፡ የጦርነቱ ሀብት የሚገኘው በሰብአዊ እርዳታ ስም ከሚሰበሰበው ገንዘብና አጋሮች ጋር ይያያዛል፡፡
ቡድኑ ከእያንዳንዱ እርዳታ ጀርባ የራሱ ስውር ተልእኮ አለው፡፡ ከእያንዳንዱ የእርዳታ እንቅስቃሴ ብዙ የሚዘርፈው ያለው በመሆኑ ረሃብ መስራትን፣ ጦርነት መስራትን/ ራሱም ጦርነት መስራት እንችላለን ይላል/ እርዳታ ማሰባሰብን እንደ ህልውናው መሰረት አድርጎ ይቆጥራል፡፡ ከእነዚህ እንቅስቃሴዎች ውጪ ህልውና አለኝ ብሎ አይመለከትም፡፡
እርዳታ ለመሰብሰብ ምክንያት አያጣም፡፡ የረሃብ ስጋት በሌለበት የረሃብ ስጋት ይሰራል፡፡ ግጭት በሌለበት ግጭት ይፈበርካል፤ ጦርነት በሌለበት ጦርነት ይሰራል፡፡ እነዚህ አደጋዎች ደግሞ ንጹኃን ይገድላሉ፤ ያፈነቅላሉ፡፡ ለእዚህ ደግሞ እርዳታ ይጠየቅበታል፡፡ ሌላ የእርዳታ ማሳ ተዘጋጀ ማለት ነው፡፡
እርዳታ እሱ በትግራይ የዘራው አሜኬላ ነው ፤ አሁንም መዝራቱን ቀጥሎበታል፡፡ በኢትዮጵያ አድራጊ ፈጣሪ በነበረበት የ27 አመት የስልጣን ዘመኑም ወደ ሁለት ሚሊየን የሚጠጋ የትግራይ ህዝብ በሴፍቲኔት መርሀ ግብር በኩል ተረጂ ነበር፡፡ ልብ በሉ እንግዲህ ቡድኑ በልማት ድርጅቱ በኩል አያሌ ኢንዱስትሪዎችንና የንግድ ተቋማትን እያንቀሳቀሰም፣ የሀገሪቱን ሀብት ሙጥጥ አርጎ ወደ ውጭ እያጋዘም፤ በአጠቃላይ ባለጸጋም ሆኖ ነው እንግዲህ ህዝቡ እርዳታ ጠባቂ ሆኖ እንዲቆይ ያደረገው፡፡ ይህ የሆነው በምክንያት ነው፡፡ ከእርዳታና ከእርዳታ በስተጀርባ የሚያገኘው ጥቅም እንዲቀጥል ብቻ አይደለም አንዲጠናከር ጽኑ ፍላጎት ስላለው ነው፡፡
በሚከፍታቸው ጦርነቶች ሁሉ የትግራይን ህዝብ እንደ ሰብአዊ ጋሻ ይጠቀማል፤ ለጦርነቱ ይማግዳቸዋል፤ አንዱን አስልጥኖ አንዱን ደግሞ መናጆ አርጎ ወደ ጦር ግንባር ይልካቸዋል፡፡በእዚህ ሳቢያ አርሶ አደሩ እና ልጆቹን የግብርና ስራቸውን ማከናወን አይችሉም፤ ህዝቡን እርዳታ እየለመነ ማኖሩን መደበኛ ስራ አርጎታል፡፡
ሰሞኑን ባነበብኩት መረጃ ደግሞ እጃቸውን ለጥምር ሀይሉ የሰጡ የቡድኑ ምርኮኞች እርዳታ አይተው እንደማያውቁ ጠቁመዋል፤ አገኘን ያሉትም ከወራት በፊት ያገኙ ናቸው፡፡ እርዳታው በከባድ መኪና ተግተልትሎ ወደ ክልሉ ሲገባ የተመለከተ የዋህ እንግዲያው ወዴት ገባ ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ እርዳታ ቢትረፈረፍም ቡድኑ ሁሌም ስለረሀብ እንዲወራ ስለሚፈልግ፣ የእርዳታ አጀንዳ ጨርሶ ከቡድኑ አይወርድም፡፡
መንግስት በትግራይ ክልል በተካሄደው የህግ ማስከበር ዘመቻ ወቅት አርሶ አደሩ የመኸር እርሻውን በሚገባ አንዲያከናውን የትግራይ ህዝብም ራሱን ቆም ብሎ አንዲመለከት በሚል መከላከያን ከትግራይ ሲያስወጣ የሆነውም ይሄው ነው፡፡
ያ ወቅት ለመኽር ወቅት እርሻ ዝግጅት የሚካሄድበት ነበር፡፡ የክልሉ ግብርና ቢሮ ለግብርና ስራው ተገቢው ማደበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ ካልቀረበ ቀጣዮቹ አመታት ለትግራይ ህዝብ አሰከፊ ይሆናሉ ማለቱን ተከትሎ መንግስት በክልሉ ከተጠየቀው በላይ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር አቅርቦ ነበር፡፡ ቡድኑ ለትግራይ ህዝብ የሚቆረቆርና፣ በእርዳታ መኖር ትክክለኛው የህይወት መስመር አለመሆኑን ቢገነዘብ ኖሮ፣ ይህን ግብአት ይዞ አርሶ አደሩ ተግቶ አንዲሰራ ማድረግ ነበረበት፡፡ እሱ ግን አርሶ አደሩንና ልጆቹን በጦርነቱ በማሰለፍ የአማራ እና አፋር ክልሎችን ወረረ፡፡
በመሰረቱ ቡድኑ የትግራይ ክልል አርሶ አደር ምርታማ እንዲሆን አይፈልግም፡፡ አርሶ አደሩ አመረተ ማለት ቡድኑ ለተለያየ አላማ የሚፈልገው እርዳታ ቀረበት ወይም ቀነሰበት ማለት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ በእርዳታ ብዙ ለተጠቀመ፣ እርዳታ ሁሉ ነገሩ ለሆነው አሸባሪው ትህነግ ፈጽሞ አይዋጥም፡፡
የትግራይ ህዝብ በዚህ ከይሲ ታግቷል፤ በእርግጥም እርዳታ ያስፈልገዋል፤ አሁንም ነገም ሰብአዊ እርዳታ ይድረስለት፡፡ አሸበሪው ትህነግ ግን ነገሮችን በእዚህ ልክ አይመለከትም፡፡ እርዳታ ጨርሶ አንዲቆም አይፈልግም፡፡ ያ ሁሉ ከባድ መኪና እርዳታ ጭኖ እየተግተለተለ ወደ መቀሌ ሲጓዝ፣ በዚያ ሁሉ የአውሮፕላን በረራ ሰብአዊ እርዳታ ወደ መቀለ ሲጓጓዝ ከሰፊው እርሻው አዝመራ እንደሰበሰበ አርጎ ሳይቆጥር አይቀርም፡፡
ከእያንዳንዱ እርዳታ ጀርባ ትልቅ የጥፋት ፕሮጀክት አለው፡፡ ልጆቹን ለጦርነት ያላሰለፈ የትግራይ ቤተሰብ እርዳታ አይሰጠውም፤ ለህብረተሰቡ መድረስ ያለበት እርዳታ የቡድኑ ታጣቂዎች ምሽግ እንዲሁም ምርኮኞቹ እጅ ተገኝቷል፤ የተማረኩ አዋጊዎቹ ኪስ ሳይቀር የእርዳታ ብስኩት ተገኝቷል፤ የቡድኑ መሪዎች ጓዳ ጎድጓዳም ቢፈተሸ ይሄው ሊሆን እንደሚችል መጠርጠር ስህተት አይሆንም፡፡ ሰብአዊ እርዳታን ለታጣቂዎች መመልመያ መሳሪያና ለታጣቂና ጀሌዎቹ ስንቅ ያውላል፤ ከዚህም ከሰብአዊ እርዳታ ጀርባ ብዙ የጥፋት ተልእኮዎች ያሉት መሆኑን መረዳት አያዳግትም፡፡
ይህ ብቻም አይደለም፤ እርዳታ ለማጓጓዝ ወደ ትግራይ የገቡ ከባድ መኪኖች ታጣቂ፣ ስንቅና ትጥቅ ወደ ጦር ሜዳ ያጓጉዛሉ፤ ይሄ አምና ሆኗል፤ እርዳታ ይዘው መቀሌ ከገቡ ከባድ መኪኖች በርካታ የሚሆኑት ዘንድሮም አልተመለሱም ሲባል ዘንድሮም እንደ አምናው ተደርጓል ማለት ነው፡፡ በዚህ ላይ ዘንድሮ ደግሞ ለሰብአዊ አገልግሎት የተከማቸን የአለም ምግብ ፕሮግራም ነዳጅ ዘረፏል፡፡
እርዳታ በእዚህ መልኩ የሚጠቀም ቡድን እርዳታ እንዲያበቃ ስንዝር አይደለም የጋት ያህልም አይንቀሳቀስም፤ የእርዳታ አመለካከትም ከውስጡ ሊጠፋ አይችልም፤ ይልቁንም የበለጠ ስትራቴጂያዊ ለሆነ የጥፋት መንገድ እንዲውል ማሴሩን ይቀጥላል እንጂ፡፡
በጤነኛ መንገድ ለሚሰራ አካል ያ ሁሉ እርዳታ እየተግተለተለ በከባድ መኪና ወደ ትግራይ ክልል ሲገባ፣ በበርካታ የአውሮፕላን ምልልስ እርዳታ ሲጓጓዝ መመልከትም ሆነ ሁኔታው እንዲቀጥል ምክንያት መሆን ያሳፍራል፡፡ አምናም ዘንድሮም ይሄ ሲሆን በእርግጥም ሊያሳፍር በተገባ ነበር፡፡ ከዚህ አይነቱ ህይወት ለመውጣት ርብርብ ማድረግ እንጂ ይህን ሁኔታ የሚያባብስ ተግባር ውስጥ መዘፈቅ በሽታኛነት ነው፡፡
ቡድኑ በትግራይ በረሃብ ስም ከአለም እየተሰበሰበ ያለው እርዳታ የትግራይን ልጆች እስትንፋስ ለማቆየት ሳይሆን የሚያውለው ሲጥ ለማድረግ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ የሰራዊቱ ስንቅ ከየት ይገኛል ተብሎ ሲታሰብ መቼም ከአርሶ አደሩ ማሳ ወይም ከአለም አቀፍ ገበያ ተሸምቶ አይባልም፡፡ በታጣቂዎቹ ምሽግና በየታጣቂው ኪስ እየተገኘ ያለው የእርዳታ ምግብ የሚያስተላልፈው መልእክትም ይህን አይደለም፤ ከእርዳታ ነው፡፡
ይህች ሀገርና ይህ ህዝብ ክፉኛ እየተወጋ ያለው እርዳታን ተገን ባደረገ ቡድን ነው፡፡ የአሸበሪው ትህነግ ጉዳይ የጊዜ ጉዳይ ይሆናል እንጂ በአንድም ይሆን በሌላ መንገድ መፍትሄ ያገኛል፡፡ መንግስት ከዚያ ቀጥሎ ቡድኑ በትግራይ ምድር የተከላቸውን እርዳታና የእርዳታ አመለካከቶች መንቀል ትልቁ ስራው ይሆናል፤ የእርዳታ ጠባቂነት ፋይል መዘጋት ይኖርበታል፡፡
ዘካርያስ ዶቢ
አዲስ ዘመን መስከረም 6/2015 ዓ.ም