ብዙዎች ከናዚ ጀርመን ጋር ያመሳስሉታል። አንዳንዶቹ ከካንቦዲያው አማጺ ኬምሩዥ ጋር ይወግኑታል። ከቦኮሃራምና ከአልሻባብ ጋርም የሚያነጻጽሩት አሉ። ያም ሆነ ይህ ግን አሸባሪው ትህነግ የለየለት አረመኔ መሆኑን ሁሉም በአንድ ድምጽ ይስማማሉ። ለዚህ አንዱ ማሳያ ደግሞ ከቅርቡ እንጀምር ብንል እንኳን ሰሞኑን የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ሪፖርተሮች በአካል በመገኘት ያረጋገጡት የሽብር ቡድኑ የጭካኔ ተግባር አንዱ ነው።
እማሆይ ማይጠምቱ ገብረ እግዚአብሔር ለኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት እጃቸውን ከሰጡ አንዱ ናቸው። ጨካኙ አሸባሪው ትህነግ የ75 አመት አዛውንቷን ለጦርነት መልምሎ አሰልፏል። መነኩሴዋ ለጦርነት ሲመለመሉና ለግዳጅ ሲላኩም እንደማንኛውም መነኩሴ የጸሎት ማድረሻ መቁጠሪያ አድርገዋል፤ የምንኩስና ቆብም ደፍተዋል።
እማሆይ ማይጠምቱ በእዚህ ዕድሜያቸው ቤተክርስቲያን ሄደው ለራሳቸውም፤ ለአገራቸውም ጸሎት ከማድረግ ይልቅ በጦር ሜዳ ተገኝተው ቦምብ እንዲወረውሩ በቡድኑ ተፈርዶባቸዋል። ተነግሮ የማያልቀው አሸባሪው ትህነግ የጭካኔ ተግባራት በእማሆይ ማይጠምቱ ብቻ የሚያበቃ አይደለም። አይነስውራንን ጭምር በጦር ሜዳ በማሰለፍ ነውረኛ መሆኑን በተጨባጭ አሳይቷል። ለዚህ ሌላው አብነት የሚሆኑት በሕፃናት እየተመሩ ቦምብ ታጥቀው በጦር ሜዳ የተገኙትና እጃቸውን ለመከላከያ ሰራዊት የሰጡት የ72 አመቱ አይነስውር አረጋዊ አቶ ተክለኃይማኖት ተስፋዩ ናቸው።
የሽብር ቡድኑ የጭካኔ ተግባራት ዘመን ተሻጋሪና ከቡድኑ አፈጣጠር ጀምሮ የነበረ ነው። በወቅቱ የነበረውን መንግሥት ለመቃወም ወደ ትግል ሜዳ ከወጡት መሃል የትግራይ ነፃነት ግንባር የሚባል ድርጅት አንዱ ነበር። ማንም ተቀናቃኝ ከጎናቸው እንዲኖር የማይፈልጉት የቡድኑ አባላት እንመካከር በሚል ሽፋን የትግራይ ነፃነት ግንባር አባላትን በአንድ ቦታ በመሰብሰብ በተኙበት ለወሬ ነጋሪ ሳይቀሩ ሁሉንም ጨርሰዋቸው አድረዋል። በ17 አመታቱ ጦርነትም የቡድኑን አካሄድ የተቃወሙ በርካታ የትግራይ ንጹሃን ልጆች በጠራራ ፀሐይና በጠፍ ጨረቃ በሽብር ቡድኑ ተረሽነዋል።
አንዳንዶችንም ቡድኑ ለማሰቃያ አላማ ባዘጋጀውና ባዶ ስድስት በሚባለው እስር ቤት ለአመታት እንዲማቅቁ በማድረግ ለአካልና ለሥነልቦና ጉዳት ዳርገዋቸዋል። በየበረሃው ባቋቋማቸው ከምድር በታች እስርቤቶችም በርካቶችን በመግረፍና በማሰቃየት የጭካኔ ጥሙን ሲወጣ ቆይቷል።
የአሸባሪ ቡድኑ አባላት ወደ ስልጣን ከመጡ በኋላም ስልጣናቸውን የሚገዳደሩ ሰዎችን እራሳቸው ባቋቋሟቸው ድበቅ እስር ቤቶች በማሰቃየት የማፍያ ሥራ ሲሠሩ ኖረዋል። በማዕከላዊ እስር ቤትም በርካታ ንጹሃን ዜጎችን በማጎርና በማሰቃየት ትውልድ ይቅር የማይለው ግፍ ፈጽመዋል።
በወንዶች ብልት ላይ የሃይላንድ ውሃ በማንጠልጠልና በማኮላሸት፤ በሴቶች ላይም ከኢትዮጵያዊ ሥነምግባር ውጪ የሆኑ ጸያፍ ተግባራትን ሲፈጽሙ ኖረዋል። ስልጣናችንን ይገዳደረናል የሚሉትን ግለሰብ ሳይቀር ሽብርተኛ የሚል ተቀጽላ በመለጠፍ የፊጥኝ አስረው አካላዊና ስነልቦናዊ ጉዳት ሲያደርሱ ኖረዋል። አማራውን ግንቦት ሰባት፤ ኦሮሞውን ኦነግ በሚል ዜጎች በአገራቸው ላይ በነፃነት ሃሳባቸውን እንዳይገልጹና በብሔራቸው ተሸማቀው እንዲኖሩ አበክረው ሰርተዋል።
በስልጣን ማብቂያቸው ዘመን አካባቢ በኦሮሚያና በአማራ ክልሎች የተነሳውን የሕዝብ ተቃውሞ በኃይል ለማፈን ሲባል በርካታ ወጣቶች እንደቅጠል እንዲረግፉ ተደርጓል። በወለጋ አካባቢ አንዲት እናት ልጇን ገድለው በሬሳው ላይ እንድትቀመጥ ያደረጉበት አጋጣሚ እስካሁንም ከሕዝብ ህሊና የሚፋቅ አይደለም።
የስልጣን ዘመናቸው አብቅቶ መቀሌ ከመሸጉ በኋላም ለ20 አመታት ያህል ሲጠብቃቸው የቆየውን የሰሜን ዕዝን ከጀርባው በመውጋት ወራዳ ተግባር ፈጽመዋል። ቀን የአርሶ አደሩን ሰብል ከአንበጣ ሲከላከሉ የዋሉትን የመከላከያ ሰራዊት አባላት ሌሊት በተኙበት በማረድ የሽብር ቡድን አረመኔነቱን አሳይቷል። ሴት የመከላከያ ሰራዊት አባላትን ጡት በመቁረጥ የጭካኔያቸውን ጥግ ገልጸዋል። የሞቱ የሰራዊቱን አባላት ልብስ አውልቀው በፀሐይ በማንቃቃት በሬሳ ፊት ከበሮ ደልቀዋል።
በትግራይ ብልጽግና ፓርቲን ትደግፋላችሁ በሚል ብዙዎችን በገፍ ገድለዋል። ከዚያም አልፎ ሬሳቸውን ከጉድጓድ በማውጣት ለጅብ አስበልተዋል። እርጉዝ ሴቶችን በሳንጃ በመውጋት አረመኔነታቸውን በአደባባይ አሳይተዋል። የመከላከያ ሰራዊት ከመቀሌ ከወጣ በኋላም በአማራና በአፋር ክልል ወረራ በማድረግም በሕዝቦች ላይ መጠነ ሰፊ ግፍ ፈጽመዋል። ሕፃናትና የ80 አመት መነኩሴን ጭምር በመድፈር ነውረኛነታቸውን አሳይተዋል። ከሰዎች አልፈው እንስሳትን ጭምር በጥይት ደብድበው በመግደል የጥላቻቸውን ጥግ አስመስክረዋል።
በተለይም በማይካድራ ብሔርን መሠረት ባደረገ መልኩ ሳምሪ የሚባል የወጣቶች ጨፍጫፊ ቡድን በማቋቋም ከ1ሺ 500 በላይ አማሮች በጅምላ ፈጅተዋል። በጭና ሰፊ ጭፍጨፋ አድርገዋል። በአፋር ጋሊኮማ ሕፃናትንና ሴቶችን በከባድ መሣሪያ ገድለዋል። በአማራና በአፋር የሃይማኖት ተቋማት ላይ ጭምር በመጸዳዳትና በማርከስ ነውረኛነታቸውን አሳይተዋል።
ሰዎችንም በመግደል በመኖሪያ ቤትና በማሳ በመቅበር ከሰብአዊነት ያፈነገጠ ተግባር አከናውነዋል። በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎችም ከአሸባሪዎቹ ሸኔና አልሻባብ ጋር በማበርም ንጹሃንን ጭካኔ በተሞላበት መልኩ እንዲታረዱ አድርገዋል። ጨቅላ ሕፃናት ሳይቀሩ በጥይት ተደብድበው እንዲሞቱ ፈርደዋል።
የትህነግ የሽብር ብድን ቆሜለታለሁ ለሚለውም የትግራይ ሕዝብ የሚራራ አይደለም። ሕፃናትን በሀሽሽ አድንዝዞ በጦርነት ከማሰለፍ ባሻገር የእናቶች ዘመቻ በሚል ወላዶች የጦርነቱ ሰለባ እንዲሆኑ አድርጓቸዋል። ወላጆች ልጆቻችን የት ደረሱ የሚል ጥያቄ እንዳያነሱ በርካታ ልጆች በጦርነቱ የሞቱባቸውን በመለየት ‹‹የእናቶች ዘመቻ›› በሚል በግንባር ለጦርነት ግዳጅ አሰልፏቸዋል።
በአግባቡ ያልሰለጠኑ ሕፃናትን በግዳጅ በማሰለፍ ዘመናዊ መሣሪያ ከታጠቀ ሰራዊት ፊት እንዲቆሙ ከማስገደዱም ባሻገር ፈርተው የሚሸሹትን ከኋላቸው በጥይት እንዲደበደቡ ትዕዛዝ እስከመስጠት ድረስ የዘለቀ አረመኔያዊ ድርጊት የሚፈጽም ግፈኛ ቡድን ነው። ሰሞኑንም ተጠልፎ የወጣ የድምጽ መረጃ ለዚህ አንዱ ማሳያ ነው።
ይህ አረመኔ ቡድን የሕዝብ ማዕበል የሚል ኋላ ቀር የጦርነት ስልት በመከተል ሕፃናትንና አረጋውያንን ጭምር በጦርነት ጭዳ እንዲሆኑ በማድረግ ላይ ይገኛል። ይህም ሳያንሰው በጦርነቱ አካላቸውን ያጡ ሕፃናትን ደብቆ በማስቀመጥ ከሕዝብ እንዳይደባለቁ መድሎ በማድረግ ላይ ነው።
የትህነግ የሽብር ቡድን ርሃብን እንደፖለቲካ የሚጠቀምና በሕዝብ ዕልቂት የፖለቲካ ጥቅም እስካገኘ ድረስ ማንኛውንም ተግባር ከመፈጸም ወደ ኋላ የማይል ነው። በተለይም የሰብአዊ ድጋፎችና የእርዳታ እህልን ከተራቡ ጉሮሮዎች በመንጠቅ ህልውናውን የማቆየት ባህል አለው። በ1977 በተከሰተው ርሃብ ለትግራይ ሕዝብ የተላከውን ስንዴ በመሸጥ ለጦር መሣሪያ መግዣ አውሎታል። በዚህም የሚበሉት አጥተው በርካቶች በርሃብ እንዲረግፉ ምክንያት ሆኗል።
ሰሞኑንም መቀሌ ከሚገኘው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መጋዘን ከግማሽ ሚሊዮን ሊትር በላይ ነዳጅ በመስረቅ የእርዳታ እህል ለሕዝብ እንዳይደርስ የተለመደ ክህደቱን ፈጽሟል። በተመሳሳይም የሕፃናትን አልሚ ምግብ በመስረቅ ለታጣቂዎቹ እንደሚያውል ቡድኑ በኃይል ከለቀቃቸው ምሽጎች ውስጥ ማስረጃዎች መገኘታቸው የሚታወቅ ነው። የቡድኑ ከትናንት እስከ ዛሬ የጭካኔ ጥግ እንዘርዝር ካልን በዚህ ጽሑፍ የሚያልቅ ሳይሆን ታሪክ በስፋት የሚዘግበው ይሆናል።
አሊ ሴሮ
አዲስ ዘመን መስከረም 5/2015 ዓ.ም