ቀዳሚ ማስታወሻ፤
ለአንድ መቶ ፐርሰንት ጥቂት ነቁጦች ብቻ ሲቀሩ መላው ሕዝበ ኢትዮጵያ በተለያዩ የሃይማኖቶች ጥላ ሥር መሰባሰቡ የተረጋገጠ እውነት ነው። ስለሆነም ከወቅት ጋር የሚሄዱ ወይንም ከሁኔታዎች ጋር የሚስማሙ ሃሳቦችን ከቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ እየተዋሱ ርዕሰ ጉዳዮችን ማጎልበት ሊበረታታ የሚገባው እንጂ በፈራ ተባ ሊታለፍ የሚገባ መሆን የለበትም።
የሃይማኖት መጻሕፍት አዘውትረው ሊጠቀሱ የሚገባቸው ለነፍስ ትድግና ዋስትና ስለሚሰጡ ብቻ ሳይሆን ለዕለት ተዕለት የሕይወት ስምሪት፣ ለዕውቀትና ለጥበብ ሀሰሳ ጭምር ፋይዳቸው ከፍ ያለ መሆኑን ማስታወሱም አግባብ እንደሆነ እናምናለን። በቅዱስ መጽሐፍ ውስጥም ይሄው እውነታ በግልጽነት ተመልክቷል።“የሰው ልጅ ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ ቅዱሳት መጻሕፍት ለትምህርት፣ ለተግሳጽ፣ ልብንም ለማቅናት፣ በጽድቅም ላለው ምክር ሁሉ ይጠቅማሉ” ይላል። (2ኛ ጢሞ. 3፡16)።
ግራ ተጋብቶ እኛን ዜጎችንም ግራ መጋባት ላይ ጥሎ አሳራችንን እንድንባለ የፈረደብን ገዢው ሕገ መንግሥታዊ ሰነዳችን፡- “መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም። ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም” (አንቀጽ 11፡3)፤ በማለት የደነገገው ሃሳብ እንኳን ለእኛ ለተራ ዜጎች ቀርቶ ለሕገ መንግሥቱ “ጠበብትና ፖለቲከኞች” ሳይቀር በትርጉም አሰጣጥና በአፈጻጸም ረገድ ግራ ሳያጋባቸው እንደማይቀር እንገምታለን።
ለመጻፍ ያህል ብቻ ተጽፎም ከሆነ “አፉ” ብለን በአሜንታ እንቀበላለን እንጂ እውነትነቱን አምናችሁ ተቀበሉ የምንባል ከሆነ ግን በሙግቱ ረቺና ተረቺ ስለመኖሩ ያጠራጥረናል። ይኼው ሕገ መንግሥት ለወደፊቱ የሕዝብ ይሁንታ አግኝቶ ክለሳ የሚደረግበት ከሆነ ይህ “የጣልቃ መግባት ያለመግባት” ጉዳይ በአግባቡ እንዲፈተሽ ከወዲሁ ማስታወሻ በማኖር አደራችንን እናስተላልፋለን።
መነሻና መዳረሻችን፤
ለዚህ ጽሑፍ የሰጠነውን ርዕስ የተዋስነው “መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን” በሚል ስያሜ ከሚታወቀው የቅዱስ መጻሕፍ አንድ ክፍል ነው። “መኃልየ መኃልይ” ማለት “ከመኃልይ የሚበልጥ መኃልይ” ወይንም “ከመዝሙር ሁሉ የሚበልጥ መዝሙር” ማለት ነው። “የአማልክት አምላክ፣ የጌቶች ጌታ፣ የነገሥታት ንጉሥ ወዘተ.” ከሚሉት ማነጻጸሪያዎች ጋር ማስተያየቱ ለግልጽነት ይጠቅማል።
የቅዳሳት መጻሕፍት ተንታኞች “መኃልየ መኃልይ ዘሰሎሞን” የሚለውን ርዕስ የሚያብራሩት በሰሎሞን ወይንም ለሰሎሞን ወይንም ስለ ሰሎሞን የተጻፈ መዝሙር እንደሆነ ነው። ይህንን ማንጸሪያ (Analogy) በመዋስም “መኃልየ መኃልይ ዘኢትዮጵያ” በማለት ለዚህ ጽሑፍ በተዋስነው ርዕስ ለማሳየት የሚሞክረው “በኢትዮጵያ በራሷ” ወይንም ለኢትዮጵያ ወይንም ስለ ኢትዮጵያ ልንዘምር ስለሚገባን ዋና ጉዳይ ስለሆነ አንባቢያን ቀድመው የመነሻችንን ዐውድ በአግባቡ እንዲረዱ በማስታወስ ወደ ዝርዝር ጉዳያችን እናቀናለን።
ለኢትዮጵያ ወይንም ስለ ኢትዮጵያ የተዜ ሙት፣ የተነገሩት፣ የተወሩትና የተጻፉት የእስከ ዛሬ “መዝሙሮች” ይዘት በአብዛኛው ወደየት እንደሚያተኩር አይጠፋንም። በዚህ ጽሑፍ “መዝሙር” እየተባሉ የሚጠቀሱት ሃሳቦች የግጥምና የዜማ ጠበብት የተራቀቁባቸውን ድርሰቶች ብቻ ማለታችን አይደለም። ዕለት ተዕለት አፋችንን በእንጉርጉሮ የምናሟሽባቸውን፣ በቡድን ውይይትና በቤተሰብ መካከል የምናንሸረሽራቸውን፣ በየሚዲያውና በማኅበራዊ መድረኮች (Platforms) እየጣልን የምናነሳቸውን፣ እያከበርን የምናሞግሳቸውን፣ እያንቋሸሽን የምንተቻቸውንና ግራ በተጋባ ስሜት ውስጥ ስንሆን ስለ እርግጠኝነታቸው ሳንጨነቅ የምንቀባበላቸውን ዘርፈ ብዙ ዝርው ሙግቶችንና ርዕሰ ጉዳዮችን በሙሉ የሚያጠቃልል ነው።
አንኳር ሃሳባችንን የሚወክልልንን አንድ ጥቅስ የጽፉን ርዕስ ከተዋስንበት “የመኃልየ መኃልይ” መጽሐፍ በመዋስ እንንደርደር፡- “እነሆ! ክረምቱ አለፈ። ዝናቡም አባርቶ አበቃ። አበቦች በምድር ላይ ፈክተው ተገለጡ። የዜማም ጊዜ ደረሰ። የርግቦች ድምጽም በምድራችን ተሰማ” (ምዕ. 2፡11-12)።
በማንኛውም ቋንቋ ውስጥ ለቃላት ፍቺ የሚሰጠው አንድም በእማሬያዊ አለያም በፍካሬያዊ ይዘታቸው ነው። እማሬና ፍካሬ የሚሉት ሁለቱ ቃላት ምንጫው የግዕዝ ቋንቋ ነው። እማሬ የሚወክለው ያልተሰወረውን ግልጽ ፍቺ ወይንም የመዛግብተ ቃላት “ጥሬ ትርጉምን” ሲሆን በአንጻሩ ፍካሬ የሚወክለው ከጥሬ ትርጉሙ በስተጀርባ ያለውን ሰፊና ጥልቅ ሃሳብ ይሆናል።
በዚሁ መሠረትም ከላይ ከፍ ብለን ከጠቀስነው የመኃልየ መኃልይ መጽሐፍ የጠቀስነው ጥቅስ በሁለቱ የአተረጓጎም ስልት መሠረት ከሀገራዊ ጉዳዮቻችን ጋር እያስተያየን እንፈትሻለን። ክረምት የሚወክለው ከሰኔ 25 እስከ መስከረም 26 ያሉትን የዝናብ ወቅት ብቻ አይደለም። “ክረምት” በአንዳንድ ባህሎች በፍካሬያዊ ትርጉሙ የሚወክለው ከፍተኛ ችግር በተጋረጠ ወቅት የስሜት ህመም ጠንክሮ እንባ እንደ ውሃ በጉንጭ ላይ የሚታፈስበትን ጭጋጋማ የመከራና የሀዘን ቀናትን ነው። አበቦችም የብሩህ ተስፋ ምሳሌዎች ናቸው። ርግብ የሰላም መገለጫ ምልክት (Symblole) መሆኗም በሁሉም ዘንድ የታወቀ ነው።
ይህን መሰሉን ግርድፍ የቃላት አተረጓጎም መነሻ በማድረግ ከሀገራችን ወቅታዊ ሁኔታዎች ጋር በማዛመድ አንዳንድ ሁኔታዎች ለመቃኘት እንሞክር። የእስከ ዛሬው የሀገራችን ታሪክም ሆነ እያዜምን ያደግናቸው መዝሙሮችም ሆኑ ትርክቶች በጦርነትና በጦረኝነት የደመቁ መሆናቸው ለክርክር አይጋብዝም። በግፈኞች ሰለባ ደማቸው ከንቱ ፈሶ የቀረ የዜጎቻችን ቁጥርም ከ እሰከ ተብሎ በአሀዝ የሚገለጽ አይደለም።
እነዚህን መሰል “በክረምት የሚመሰሉ” ነባር ታሪኮቻ ችንንና ትርክቶቻችንን ለጊዜው አቆይተን በወቅታዊ የሀገራችን መከራ ላይ ብናተኩር እንኳን ለአስረጂነት የሚመጥኑ በርካታ ክስተቶችን አስተናግደንና እያስተናገድን ስለሆነ ወደ ሩቅ ዓመታት ታሪኮቻችን መንጠራራቱ እጅግም ለመነሻችን ቅርበት ላይኖረው ይችላል።
“ዛሬ” በምንለው ጀንበራችን ኢትዮጵያ ምን ያህል መከራዎችን ተሸክማ እየቃተተች እንዳለ የምናየውና የምንሰማው ነው። መዝሙሮቻችንም ሆኑ ውይይቶቻችን፣ ንግግሮቻችንም ሆኑ ምክክሮቻችን ወይንም ጽሑፎቻችን በሙሉ የታጀሉት የሀገርን መከራ በመተረክ ላይ ነው። በተለይም ባለፉት ሁለት ዓመታት ከውስጥና ከውጭ የደም ጥማተኞችና ግፈኞች የተፈጸሙብን መልከ ብዙ ጦርነቶች፣ አልቂቶች፣ ዝርፊያዎችና ዘርዝረን የማንዘልቃቸው መከራዎቻችን ኢትዮጵያን “ጥቁር ከል” ያስለበሱ፣ ሕዝቡን ለመፈናቀል፣ ለሥነ ልቦና ቁስልና በቀላሉ ሊሽር ለማይችል ስብራት የዳረጉ እንደነበሩ አይዘነጋም። ዛሬም ከመሰል መከራዎቻችን ነፃ ወጥተናል ብለን ለመፈንጠዝና “የአሳሮቻችንን ዝተት” አውልቀን የመጣል ደረጃ ላይ ደርሰናል ብለን አንፎክርም።
2014 ዓ.ምን ሸኝተን 2015 ዓ.ምን የተቀበልነውም የሀዘን ድባባችን ተገፎ፣ የጦረኞቹ ጠላቶቻችን የጠብ መንጃ ልሳን ተዘግቶ “በሃሌሉያ” ዝማሬ እያሸበሸብን ነው ማለትም አይደለም። በርእሰ ዐውዳመታችን ዕለት እንኳን ሳይቀር ከታዳጊ ልጆቻችን “የአበባ አየሽ ወይ” ዜማ ይልቅ ጎልቶ ሲደመጥ የነበረው “ጀግኖቻችን ዛሬስ የትኛውን አካባቢ ነፃ አውጥተው የምሥራች አሰሙን” የሚሉ “ዜናዎችና” ትንተናዎች ላይ ልባችንንና ቀልባችንን ሙሉ ለሙሉ ሰጥተን ነበር።
“እሰይ ደስ ይበለን” ከሚል የምሥራች ገላጭ ዜማ ይልቅ ጎልቶ ይደመጥ የነበረው፡-
“የሀገሬ ጀግኖች ሴት ወንዱ ታጠቁ፣
ከእንግዲህ ለጠላት አንተኛም ንቁ።
ጀግንነት እንደሆን የአባቶቻችን ነው፣
ኅብረታችን ጸንቷል ድል መምታት የእኛ ነው።”
እንዳለው ዜመኛው በቁጭት እንጉርጉሮ እያዜምን ነበር። ድል ለጀግኖቹ የመከላከያ ልጆቻችንና እንደ ተርብ ተናዳፊ ለሆኑት የጥምር ጦሩ አንበሶች ይሁንና በአዲስ ዓመት ዋዜማና መባቻ ቀናት እጅግ የሚያስገርሙና የሚያስፈነጥዙ የድል ብሥራቶችን እየሰማን ነው። አድማ የጠሩብን መንግሥታት ሳይቀሩ “እውነታው ቢተናነቃቸውም” የጨፈገገው ፊታቸው ፈታ የማለት አዝማሚያ ያሳየበትና አንዳንዶችም በሚሰሙት ታላላቅ ሀገራዊ ደማቅ የድል ዜናዎች “ጆሯቸው ጭው ብሎ” ግራ የተጋቡበት ቀናት ነበሩ። የእኛ ሀገራዊ መኃልይ በድል መዓዛ ሲታወድ የጠላቶቻችን ጠረን ደግሞ የተግማማ ወደ መሆን ደረጃ እየተቀየረም ይመስላል።
ለእኛ ለኢትዮጵያዊያንና ለውዷ ሀገራችን “የመከራችን ክረምት” እየጠባ፣ የተስፋችን መገለጫ አበቦችም እየፈኩና የቆሰለችው የሰላማችን ርግብ ወደ ፈውስ እየተቃረበች እንዳለች በድሉ መኃልየ መኃልይ እየተረጋገጠልን ነው። ድሉ ወደ መቋጫው እየተንደረደረ እንጂ የታመመችው የሰላም ተምሳሌቷ ርግባችን በአየ ራችን ላይ መኃልያችንን እያስተጋባች በሙሉ አቅሟ ለመብረር ገና የማገገሚያ ወራት ያስፈልጋታል።
ቢሆንም ግን በፈጣሪ ቸርነት በተቀበልነው የ2015 ዓ.ም ዜማችን የሰላም፣ ቋንቋችን የሰላም፣ ንግግራችን የሰላም ሆኖ አየሩን ብንፈውሰው ኑሯችንና ሕይወታችን በአጭር ጊዜ ተፈውሶ ሀገራዊ እንቆቅልሾቻችን በሙሉ እየተፈቱ ለመተርተር ይፋጠኑ ነበር።
ሀገራችንን የከበበው የጥፋት ደመና እየተገፈፈ፣ አየራችንን የበከለው የክፉዎች መርዝ እየተጠረገ የጦርነት ወሬዎች ታሪክ ለመሆን የተቃረቡ ይመስላል። ስለዚህም ኢትዮጵያ በራሷ አንደበት የምትዘምረው መኃልይ፣ ወይንም ስለ ኢትዮጵያ የሚቀነቀነው መዝሙር፣ ወይንም ለኢትዮጵያ የሚደረሰው ዜማና ግጥም ሰላምን የሚያሞግስ እንጂ በቂምና በቁርሾ የጠለሸ ሊሆን አይገባውም።
ንግግሮቻችን፣ ጽሑፎቻችን፣ ውይይቶቻችንና ምክክሮቻችን ሁሉ ሰላምን የሚያደምቁ፣ ስለ ሰላም አሸናፊነት የሚሰብኩ እንጂ ዳግም ሰላምን ጥቁር ቱቢት አስለብሰው የሀዘን ፍራሽ ላይ ጎዝጉዘን እንድንቀመጥ የሚጋብዙ መሆን የለባቸውም።
የዜማችን አስኳል መልእክት ቀደም ሲል የጠቀስነው የመኃልየ መኃልይ ሃሳብ ሊሆን ይገባል። ደግመን እናስታውሰው፡- “እነሆ! ክረምቱ አለፈ። ዝናቡም አባርቶ አበቃ። አበቦች በምድር ላይ ፈክተው ተገለጡ። የዜማም ጊዜ ደረሰ። የርግቦች ድምጽም በምድራችን ተሰማ።”
ከዜማችን በማስከተልም የኢትዮጵያን ፊት ሙሉ ለሙሉ ወደ ልማት ማዞር፣ እኛም ልጆቿ እጆቻችንን ለኅብረት ስራ ማጠናከር ይኖርብናል። በሌላኛው የቅዱስ መጽሐፍ ክፍል እንደተጠቀሰው፡- “ጠላቶቻችንም መልካም እንደሆነልን፣ ፈጣሪም ምክራቸውን ከንቱ እንዳደረገ ሰሙ። እኛም ሁላችን ወደ ሥራችን ተመለስን” በማለት በኢትዮጵያ አየር ላይ ዝማሬያችን ሊናኝ ይገባል።
እስከ ዛሬ ብዙ ተቸን፣ ጻፍን፣ ዘመርን፣ በክፉ የሀሜትና የመናናቅ ቃላት እርስ በእርስ ተቋሰልን። አሸናፊና ተሸናፊ በሌለበት እንካሰላንትያ እየተጠዛጠዝን ለልጆቻችን ክፉውን፣ ለታሪክም ትዝብት አተረፍን እንጂ ምንም አልፈየደልንም። ስለዚህ በፈጣሪ ቸርነት በተቀበልነው በዚህ “አዲስ” ዓመት ለኢትዮጵያ የምንቀኝላት መኃልይ የሰላም ቅኔ ሊሆን ይገባል።
ቀልባችንን አስክነን፣ ብሽሽቁን አቁመን፣ ፉከራውን ገታ አድርገን ስለ ሰላም ብቻ እንጻፍ፣ እንደስኩር፣ እንሟገት፣ እንማማር፣ እንቀባበል። “ክረምታችን አልፏል፣ አበቦችም ተገልጠዋል፣ ሰላማችንም በቅርቡ ይረጋገጣል” ኢትዮጵያም የሀዘን ጨርቋን አውልቃ የሙሽርነት የማዕረግ ልብሷን ትጎናጸፋለች። ልጆቿም ለሉዓላዊነቷ ክብር፣ ለእድገትና ብልጽግናዋ እጅ ለእጅ ተያይዘው በመሥራት በዓለም ፊት ደምቀው ይወጣሉ። ይኸው ነው። ሰላም ይሁን።
(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን መስከረም 4/2015 ዓ.ም