በሆነ ተአምር ሽብርተኛው ሕወሓት 47 አመታት ወደኋላ ተጉዞ እንደገና በዳግማዊ ደደቢት ዳግም ቢወለድ እንኳ ተፈጥሮውንና ማንነቱን እንደማይቀይር ከአንድም፣ ሁለት፣ ሶስት ፣…ጊዜ አረጋግጦልናል። ሰሞነኛው “የማጠቃለያ ምዕራፍ” በሚል ርዕስ ይፋ በሆነውና ለከፍተኛ አመራሩ ባዘጋጀው ባለ 12 ገጽ ሰነድም ይሄን ማንነቱን አትሞልናል።
በዚህ ሰነድ ሕወሓት ሰላም እንደማይፈልግና አማራን እንዴት እንደጠላት ፈርጆ ሲያበቃ አሁን ወዳጅ መስሎ አዘናግቶ ለመበተን እየሰራ እንደሆነ ፤ በተጨባጭ ትጥቅና ስንቅ የሚያቀርቡለት የውጭ ኃይሎች መኖራቸውን፤ በሀገራችን የተለያዩ ክልሎች የሚንቀሳቀሱ አማፂያንና ሽብርተኞች ጋር እንዴት ተቀናጅቶና ተናቦ እንደሚሰራ ፤ የእርዳታ ድርጅቶችን እንዴት አግባብቶ የእርዳታ ቁሳቁስ እንዳይነፍጉት እያደረገ እንዳለ ፤ የትግራይ ወጣቶችን የማይቀርና የመጨረሻ ድል ነው እያለ እያምታታና እያታለለ ለእሳት እንደሚማግድ ያትታል ። በዚህ ሰነድም ሆነ ከዚህ በፊት በተገኘው 80 ገጽ ሰነዱ ሕወሓት አይደለም በዚህ ትውልድ በምጽዓትም ቢሆን የማይቀየር መሆኑን ጥሩ አርጎ አረጋግጦልናል።
ስለዚህ ቁሞ ቀርና ተቸካይ እኩይ ማንነቱ በተደጋጋሚ እዚህ ጋዜጣ ላይ ጽፌያለሁ። በቃ ሕወሓት፣ ሕወሓት ነው። ይለወጣል የሚል ጅላጅል የተስፋ እንጥፍጣፌ ካለን ሰሞነኛው ሰነድ እርማችንን አውጥቶልናል።
ይሄን “የማጠቃለያ ምዕራፍ” የሚለውን ሰነድ ስመለከት ምንም አዲስ ነገር አላገኘሁበትም ። ይልቅ “የማጠቃለያ ምዕራፍ” የሚል ሰነድ ማዘጋጀት ያለብን እኛ አልነበርንም፤ የሚል ጥያቄ አጭሮብኛል ። ሽብርተኛው ሕወሓትማ ራሱን በራሱ ማጥፋት እንጂ ምን የሚያጠቃልለው ነገር አለ ። ሰሞኑን በሁሉም ግንባሮች የከፈተው ጦርነት መልሶ እያጠፋው እንደሆነ እየታዘብን ነው። ስለዚህ ሕወሓት የሚሰጠንን አጀንዳ ከማመንዠክ ይልቅ ፤ ራሳችንን መጠየቅ ያለብን ፤ “በእርግጥ ከዚህ ጦርነት የመውጫ ስትራቴጂ አለን ወይ !”መልሱ በሰላማዊ ድርድር የሚል ከሆነም ሕወሓት መቼም ቢሆን በሰላማዊ ድርድር እንደማያምን እያረጋገጠልን ነው ። ጋላቢዎቹ እነ ግብጽም ዘላለሙን ሀገራችንን እንዳደማ እንዲኖር እንጂ እንዲደራደር አይፈቅዱለትም።
በዚህ ላይ የመውጫ በራችንን እየዘጋ አማራጭ እያሳጣን ነው። ታዲያ ከዚህ ጦርነት የመውጫ ስትራቴጂያችን ምንድን ነው !? ቀላልና ቁርጥ ያለ መልስ መስጠት ቢያስቸግርም ቢሆኖችን ማስቀመጥ ይቻላል።
1ኛ . ጦርነቱን በማያዳግም ሁኔታ ማሸነፍ፤
2ኛ . ከዚህ ጎን ለጎን የትግራዋይን ልብ ማሸነፍ
3ኛ. እውነትንና ፍትሕን ታቅፈን አጨብጭበን እንድንቀር ያደረገንን የዲፕሎማሲና የአለማቀፍ ግንኙነታችንን ችግርና ድክመት ቀርፈን ሌት ተቀን መስራት ናቸው።
እነዚህ የመውጫ ስትራቴጂዎቻችን የገጠመን ጠላት ተራ አሸባሪ አለመሆኑንና ክፉ ጠላት መሆኑን ያሳያሉ። ለዚህ ነው በተደጋጋሚ ሕወሓትን አሳንሶ ማየት እንደማይገባ ማሳስበው።
ከመውጫ ስትራቴጂው አንዱ የሆነው ጦርነቱን በማያዳጋም ሁኔታ መደምደም የሚለውን ለወታደራዊ ልሒቃን ትቸው፤ በሁለቱ የመውጫ ስትራቴጂዎች ግን እንደገና ሃሳብ አቀብላለሁ።
ከኢትዮጵያና ከእውነት አምላክ ጋር ለ3ኛ ጊዜ ተገደን የገባንበት ጦርነት ሙሉ በሙሉ በእኛ አሸናፊነት በቅርብ ይጠናቀቃል ። የድህረ ጦርነቱ ዳፋ ግን ላልተወሰነ ጊዜ አብሮን ይኖራል።
ደጋግሞ ያሳረፈብን የግርፋት ሰምበሩ ሳይሽር ሰሞኑን በቆቦ በሕጻናትና በሴቶች ከፍ ሲልም በንጹሐን ላይ ተመሳሳይ ጭፍጨፋ ፈጽሟል። የፍትሕ ሚኒስቴር ባለፈው የሽብር ቡድን ደቡብ ወሎን የኦሮሞ ብሔረሰብ እና የሰሜን ሸዋ ዞኖችን በወረራ ከመያዙ በፊት ይፋ ያደረገው ቅድመ ምርመራ ውጤት ይፋ እንደሆነው ሕወሓት ወሯቸው ነጻ በወጡ አካባቢዎች ብቻ 483 ሰዎች በግፍ ተገድለዋል፤ 163 ሰዎች አካል ጉዳተኛ ሆነዋል ፤ 109 ሕጻናትን ልጃገረዶችንና ሴቶችን ለመግለጽ በሚከብድ ሁኔታ በቡድን አስገድዶ መድፈር ተፈጽሞባቸዋል። እነዚህ ዞኖች ከወራሪው ነጻ ሲሆኑ የተፈጸመው ግፍና ሰቆቃ ህልቆ መሳፍርት እንደሌለው አረጋግጠናል።
እንግዲህ ቁስሉ እስኪጠግግ፣ ሰንበሩ እስኪጠፋ፣ የአእምሮና የስነ ልቦናው ቅሪቱ እስኪወገድ ድረስ ሕማማቱ አብሮን ይባጃል። አረመኔውና ግፈኛው ሕወሓት በማይካድራ፣ በጭና፤ በአጋምሳ በውጫሌ ፣ በጋሊኮማ በንፋስ መውጫ እና በወረራቸው አካባቢዎች በሙሉ ለመስማት የሚሰቀጥጡ ለማየት የሚዘገንኑ ዘግናኝ ግፎችና ስቃዮች ሰለባ የሆኑ ወገኖቻችን ለስነ ልቦና እና የአዕምሮ ሕመም ተዳርገዋል።
አራትና አምስት ልጆቹን ከእነ ባለቤቱ ያጣ፤ እናትና አባታቸውን በግፍ የተነጠቁ ብላቴናዎች፤ የክህነት ሚስቱ የተነጠቀ የሃይማኖት አባት፤ የተደፈሩ ልጃገረዶችና ሴቶች፤ እንደ ልጆቹ የሚያያቸው እንስሳት በጥይት የተደበደቡበት ፤ በጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓም በሰሜን ዕዝ ላይ ታሪክና ትውልድ ይቅር የማይለው ክህደትና ጭፍጨፋ ሲፈጸም የተመለከቱ የሠራዊቱ አባላት ፤ ወዘተረፈ ከደረሰባቸው የቅስምና የልብ ስብራት ለማገገም ዓመታት ይወስድባቸዋል ። ለዛውም የሕክምና የስነ ልቦና ምክርና መልሶ የማቋቋም ሥራው በተጠና አግባብ እና በጥብቅ ዲሲፕሊን ከተፈጸመ። አበክሮ የተሰበረን መንፈስና ልብ ስለመጠገን ፤ እንዲሁም በአሸባሪው ሕወሓት አስገድዶ ማጥመቅ (ኢንዶክትሬሽን) በተሳሳተ ትርክት እና በማስፈራራት የሸፈተን ልብ ስለመማረክም አበክሮ ማቀድና መስራት የጦርነቱ መውጫ ስትራቴጂ አካል ሊሆን ግድ ይላል።
አሸባሪውና ከሀዲው ሕወሓት የትግራይን ሕዝብ ይዞ ለመጥፋት ታጥቆ እየማሰነ ነው። በ3ኛውና ሰሞነኛው ጦርነቱ ትግራዋይን ለማይጠረቃው የስልጣን እርሀቡ እየማገደ እያስጨረሳቸው ነው። ትግራይን ሴቶችና ጨቅላዎች ብቻ የሚባዝኑበት የመናፍስት ክልል ሊያደርገው ቆርጦ ተነስቷል። እያደረገውም ነው። መጀመሪያ ወጣቱን በመቀጠል ሕጻናትን ከዚያ አረጋውያንንና አካል ጉዳኞችን በጦርነት እየማገደ እየጨረሳቸው ነው። በእብሪትና በማንአለብኝነት እያስገደደና እያታለለ ትግራዋይን በሕዝባዊ ማዕበል በየግንባሩ እየማገደ እያስፈጃቸው ነው። አምና በደቡብ ጎንደር በሰሜን ጎንደር በዋግ ኽምራ በሰሜን ወሎ በደቡብ ወሎ በተለይ በኩታበር በቦሩ ሜዳ በሐይቅ በጭፍራ በአፋር ትግራዋይ እንደ ቅጠል መርገፋቸው ሳያንስ ዘንድሮም በራያ ፣ በአፋር ፣ በወልቃይት፣ በሱዳንና በሌሎች ግንባሮች እየረገፉ ነው። ለትግራይ ሕዝብ እውነት ከሕዋሓት የባሰ ጠላትና ደመኛ አለው !?
ሕወሓት እንደ እልኸኛ ብላቴና ካፈርሁ አይመልሰኝ ብሎና ተስፋ ቆርጦ ትግራዋይን ይዞ እየሞተ ነው ። ከዚህ የከፋና የባሰ ምን ይመጣል በሚል ተስፋ የመቁረጥ ስሜት ጣዕረ ሞት ላይ ሆኖ እንኳ ትግራይን የወላድ መካን እያደረጋት ነው ። በ17 አመቱ ጦርነት 60ሺህ ልጆቹን በመነጠቁ ጧሪና ቀባሪ ማጣቱ ሳያንስ ዛሬ የተረፉ ልጆቹና የልጅ ልጆቹ ትርጉም ለሌለው ጦርነቱ ተማግደው ሲያልቁ ዛሬ ተረኛው እሱ ሆኗል። አሸባሪውና ከሀዲው ሕወሓት የእሱን ተስፋ መቁረጥ ወደ ሕዝቡ በማጋባት ስለነገ ሕይወቱና ኑሮው ተስፋ እንዲቆርጥና እንዳይጨነቅ በማድረግ ፤ ከአማራ ከኤርትራ ከአፋርና ከተቀረው ኢትዮጵያዊ ጋር ተቆራርጦ ከጎኑ እንዲሰለፍ እያደረገ ይገኛል።
ሆኖም የተረፈውን ትግራዋይ ከሕወሓት መንጋጋ ለመታደግ የኢትዮጵያ ሕዝብ በጠላትነት እንደማያየው ለማረጋገጥና የሕወሓትን ሰንኮፍ ለመንቀል የትግራዋይን ልብ ስለመማረክ አበክሮ ማሰብና ስትራቴጂ መንደፍን ይጠይቃል ። የጸረ ሽብር ትግሉ ውጤታማ ሊሆን የሚችለው የትግራዋይን ልብ በመማረክ ሲታጀብ ነውና። የጸረ ሽብር ትግል በአውደ ወጊያ በሚቀዳጁት ድል ብቻ አይረጋገጥም። የአሸባሪው ፖለቲካዊ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሠረት የሆነውን ሕዝብ ልቦና እና አመለካከት ከወዲሁ መማረክ ግድ ይላል። አሸባሪውን ከሕዝብ የመነጠል የተቀናጀ ርብርብ ይጠይቃል።
አሜሪካ ለ20 አመታት ከ2 ትሪሊዮን ዶላር በላይ ገፍግፋ በብዙ አስር ሺዎች የሚቆጠሩ ወታደሮቿን ሰውታና አካል ጉዳተኛ አድርጋ በባዶ እጇ አጨብጭባ ተሸንፋና ተዋርዳ የወጣችው የአፍጋኒስታውያንን ልቦና ማሸነፍ ባለመቻሏ ነው። የግንባሩን አውደ ውጊያማ ከ20 አመት በፊት ታሊባንን አይቀጡ ቅጣት ቀጥታ አሸንፋ ነበር። በኢራቅ በሶሪያ በሶማሊያ በየመን በሊቢያ በናይጀሪያ በማሊ በሞዛምቢክ ወዘተረፈ አሸባሪዎችን በቀላሉ ማሸነፍ ያልተቻለው ለዚህ ነው። አሸባሪዎችን በጦርነት ለማንበርከክ ከሚደረገው ፍልሚያ ባልተናነሰ ርዕዮተ ዓላማቸውን እንደ ሰብዓዊ ጋሻ ከሚጠቀሙበትና በአካልም በስነ ልቦናም ካገቱት ሕዝብ ማውጣትና ማጽዳት ይጠይቃል ።
በአሸባሪው ሕወሓት ላይ ከሶስት ሳምንታት ባነሰ ጊዜ የተቀዳጀነውን አንጸባራቂና በጥብቅ ወታደራዊ ዲሲፕሊን የተዋጀውን ድል ማጽናት ያልቻልነው የትግራዋይን ልቦና በቅጡ ባለመማረካችን ነው። አሁንም የማይቀረውን ወታደራዊ ድል ለማጽናትና ለማዝለቅ ከወዲሁ የትግራዋይን ልብ በማሸነፍ ልናጅበው ይገባል። ይበል የሚያሰኙ ሕዝባዊ ውይይቶችና ሌሎች ጅምሮች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው።
ከሸኔ ከጉሙዝ ታጣቂዎችና ከሌሎች አሸባሪዎችና ሽፍቶች ጋር የምናደርገውን ትግልም እንደዚሁ ። በውል ባንገነዘበውም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ወደ ኃላፊነት ከመጡበት ሰዓት አንስቶ የኢትዮጵያውያንን በተለይ ደግሞ የትግራዋይን ልብና አመለካከት ለማሸነፍ ብዙ ጥረዋል። ሩቅ መንገድ ተጉዘዋል። ዋጋም ከፍለዋል። ለሰላም ካላቸው ቁርጠኝነትና ጦርነት ምን ያህል አስከፊ እንደሆነ በውትድርና ሕይወታቸው ጠንቅቀው ስለሚያውቁት፤ ጓደኞቻቸውንና ወንድማቸውን ስለነጠቃቸው፤ ጦርነት የአገርን ኢኮኖሚ ምን ያህል እምሽክ ድቅቅ እንደሚያደርግና እንደሚያወድም አበክረው ስለተገነዘቡና ፤ የትግራይ ሕዝብም ጦርነት ይበቃዋል በሚል ጽኑ እምነትና የጦርነት ነጋሪት የሚጎስሙ ኃይሎች የድሀን ልጅ የእሳት ራት ያደርጋሉ እንጂ እነሱ አይዋጉም በማለት ለትግራይም ሆነ ለሌሎች ሕዝቦች ደህንነት ሲሉ እስከ መጨረሻው ሰዓት ሆደ ሰፊነትንና ትዕግስትን መርጠዋል።
አበው ጎሽ ለልጇ ስትል ተወጋች እንዲሉ በከሀዲውና የእናት ጡት ነካሹ በሆነው ትህነግ መከላከያችን፣ ሉዓላዊነታችን፣ አገራችንና ሕዝባችን ለሰላም በታመኑ ከአንድም ሁለት ሶስት ጊዜ ከጀርባ ተወጉ። ባጎረሱ ጣታቸውን ተነከሱ። አሸባሪው ሕወሓት በእብሪት በጫረው እሳት ክቡር የሆነው የሰው ልጅ ሕይወት ጠፋ ፤ አካል ጎደለ፤ የአገር ኢኮኖሚ ክፉኛ ደማ ፤ የሽብር ኃይሉ በመጀመሪያው ጦርነት ያወደማቸውን የመሠረተ ልማቶች መልሶ ለመጠገን ብቻ ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ ወጭ ሆነ። በወረራው ለተፈናቀሉ ወገኖች ዕለታዊ እርዳታ ለማቅረብ ወደ 10 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ወጭ ተደርጓል። ልብ አርጉ ይህ ወታደራዊውን ወጭ አይጨምርም። ጥገና ሲያካሒዱ የነበሩ የኢትዮ ቴሌኮምና የኤሌክትሪክ ኃይል ባለሙያዎች በግፍ ተገደሉ ። ይህ የትግራዋይን ልብ የማሸነፍ ጥረት አካል ነበር። መንግስት ከስምንት ወር ቆይታ በኋላ ለሰብዓዊነት ሲል የተናጠል የተኩስ አቁም ያወጀውም ለዚሁ ሰናይ አላማ ነበር።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አገሪቱን ከጠብመንጃ አዙሪት ለማውጣትና ከዚህ ቀደም የነበሩ ገዥዎች ያልሄዱበትን የሆደ ሰፊነትና ቁጭ ብሎ የመነጋገር አዲስ መንገድ በመምረጣቸው በልኩ እውቅና ሊሰጣቸውና አብዛኛው ዜጋ ከጎናቸው ሊቆም ሲገባ መንግሥታቸው በልፍስፍስነት ከመወቀሱ ባሻገር ፓርቲያቸውም ሆነ እሳቸው ቁጥሩ ቀላል ያልሆነ ደጋፊያቸውና ተከታያቸው ብዥታና ድንጋሬ ላይ እንዲወድቁ አድርጓል ። እነዚህ ሁሉ ጥረቶች የትግራዋይን ልብ ለመማረክ የተደረጉ እንቅስቃሴዎች እንደነበሩ ግንዛቤ አልተያዘም ። ይሁንና የእፉኝቱ ትህነግ የጥቅምት 24ቱን ታላቅ ክህደት ተከትሎ የሕግ የበላይነትን ለማስከበርና የአገር ሕልውናን ለማስቀጠል ያሳዩት ቁርጠኝነት እና ሠራዊቱ ከተፈጸመበት ታሪክና ትውልድ ይቅር ከማይለው ክህደት በኋላ ሞራሉና ወኔው አንሰራርቶ በእልህና በቁጭት ተነሳስቶ እጅን በአፍ የሚያስጭን አንጸባራቂ ድል በማስመዝገቡ አገራዊ ሞራሉ እንዲያንሰራራ አድርጓል። እፉኝቱ ትህነግ ይታበይበትና ይመካበት የነበረውን ልዩ ኃይልና ሚሊሻ አይቀጡ ቅጣት ቀጥቶ በሶስት ሳምንታት ውስጥ ሕዳር 19 ቀን 2013 ዓም መቐሌ ሊገባ ችሏል ። ለዛውም እጅ የመስጫ የመጨረሻ ቀነ ገደቡን ጨምሮ ስድስቱ ቀናት ሳይታከሉ።
ሰኔ 21 ቀን 2013 ዓም መንግስት ለሰብዓዊነት ሲል ያደረገውን የተናጠል ተኩስ አቁም እንደመልካም አጋጣሚ በመጠቀም አፋርንና አማራን በመውረር ሸዋ ድረስ የነበረው ወራሪው እንደ ልማዱ ተገርፎ ወደመማጸኛ ከተማው ቢፈረጥጥም፤ ሰሞኑን ደግሞ 3ኛ ዙር ወረራ ከፍቶብናል። ያለፈውን ስህተት ላለመድገም ከስህተታችን ተምረን ወታደራዊ ድሉን በፖለቲካዊና ስነ ልቦናዊ ድል ልናጅበው ይገባል። ሙሓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ባለፈው አመት እንዳሳሰበው ድሉን መያዝ ማጽናትና መጨመር ግድ ይላል።
እንደ መውጫ
አሸባሪው ሕወሓት እንደ ሰብዓዊ ጋሻና እንደ መደበቂያ የሚጠቀምበትን የትግራዋይ ልብና አመለካከት ማሸነፍ ሳይቻል ወታደራዊ ድሉ ሙሉኡ አይሆንም ። በጦር ሜዳ የሚገኘው ወታደራዊ ድል የትግራዋይን ልብና አመለካከት በማሸነፍ ካልታጀበ የአሸባሪው ሕወሓት መደምሰስ ብቻ እንደ አምናውና ካች አምናው ድሉን ዘላቂና አስተማማኝ አያደርገውም ። የኢፌዴሪ መንግሥት ከጦርነቱ ባልተናነሰ የትግራዋይን ልብና አመለካከት ለማሸነፍ የተግባቦት ስልት ነድፎ ሌት ተቀን መሥራት አለበት ። ደጀኑን ሕዝብ ዳር እስከ ዳር ለማነቃነቅ እና የአሸባሪው ሕወሓትን ጭካኔና አገር የማፍረስ ደባ ለማጋለጥ እየሰራው ባለ ልክ የትግራይ ሕዝብን ለመማረክም በአግባቡ መንቀሳቀስ አለበት።
ለ50 ዓመታት ያህል እንደ መዥገር በስስ ገላው ተጣብቆ ደሙን ከሚመጠው ፤ የወላድ መካን ካደረገው ፤ በአንድ ለአምስት አደረጃጀት ጠርንፎ በአፈናና ጭቆና ባሪያ ካደረገው፤ ከኢትዮጵያውያን ወገኖቹ ጋር ደም እያቃባው ካለ፤ በስሙ እየማለና እየተገዘተ የቡድናዊ ጥቅም ማሳደጃ ካደረገው ፤ ወዘተረፈ ይልቅ ከተቀረው ኢትዮጵያዊ ወገኑ ጋር በእኩልነት በፍቅር በሰላም በነጻነትና በአንድነት የመበልጸግ አቅምና ተስፋ እንዳለው ፤ ለአሸባሪው ሕወሓት ግለኛ ጥቅም ሲባል ልጆቹ ከጉያው እየተነጠቁ ለጦርነት እንደማይማገዱ፤ የትግራዋይ እጣ ፈንታ ከተቀረው ኢትዮጵያዊ ጋር በመስዋዕትነት የተሳሰረና የተገመደ መሆኑን ደጋግሞና በጥበብ አዋዝቶ በመግለጽ ልቡንና አመለካከቱን ማሸነፍ አለበት ።
በስሙ እየማለና እየተገዘተ ለ27 ዓመታት አገርንና ሕዝብን በጠራራ በአደባባይ እየዘረፈ ራሱን ሲያበለጽግ እሱን ከድህነት አረንቋ ከሴፍቲነትና ከተረጅነት ነጻ እንዳላወጣው ፤ አንድ ጊዜ ዐቢይ ሊያንበረክክህ ነው ሌላ ጊዜ አማራ ሊያጠፋህ ነው እያለ፤ በተሳሳተ ትርክትና ቁጭት ሲያታግለውና ሲማግደው የኖረው ፤ ከተደቀነብህ አደጋ የምታደግህ እኔ ብቻ ነኝ የሚለው ለግል ጥቅሙና ከተጠያቂነት ለማምለጥ መሆኑን ደጋግሞ ማጋለጥ ያስፈልጋል።
የትግራይ ሕዝብ መጻኢ እድል ከተቀረው ኢትዮጵያዊ ጋር በደም የተሳሰረ ነው !!!
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)
fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን መስከረም 3/2015 ዓ.ም