ዘርፉ ብዙም የሚታወቅ አይደለም። ነገር ግን በዘመናዊው የፊልም ኢንደስትሪ ውስጥ ወሳኝ ቦታ ከሚሰጣቸው ስራዎች አንዱ እና ዋነኛው ነው። በእኛ ሀገር የፊልሙ ዘርፍ ገና ቀና ቀና እያለ ስለሆነ ይህ ሙያ በቅጡ ዋጋው አልታወቀለትም። ቀስ በቀስ ግን እየተለመደ እና እየታወቀ ነው። ይህ ስራ የፊልም ስኮር ስራ ነው። በኢትዮጵያ ደግሞ በዚህ ዘርፍ ተጠቃሹ ዋነኛ ሰው አቀናባሪው ታደለ ፈለቀ ነው። ዛሬ ከእሱ ጋር ቆይታ እናደርጋለን።
ታደለ ፈለቀ የተወለደው አዲስ አበባ ፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ ነው። ወቅቱም 1973 ዓም ነው። አባቱ አስር አለቃ ፈለቀ ታፈሰ የኢትዮጵያ ወታደር ነበሩ። በሶማሌ ወረራ ወቅት ሀገራቸውን ለማዳን ከተፋለሙት ጀግኖች መካከል ይጠቀሳሉ። እናቱ ደግሞ ወይዘሮ ሌዲ ለገሰ ይባላሉ፤ የቤት እመቤት ናቸው። ታደለ እና ሌሎች አራት ወንድ ልጆች ከአንዲት ሴት ልጅ ጋር ወልደዋል። መኖሪያቸው የሚገኘው ፈረንሳይ ለጋሲዮን ላይ ጀግናው አትሌት አበበ ቢቂላ ይኖር ከነበረበት ቤት ጎረቤት ነው።
ታደለ የመጀመሪያ ትምህርቱን ቀድሞ ጽጌ በሻህ በሚባለው በኋላ ደርግ ትግል ለነጻነት ባለው ትምህርት ቤት ነው የተማረው። ከዚያም ጎረቤት የሚገኘው ሚያዝያ 23 ትምህርት ቤት ገብቶ ተምሯል። ሁለተኛ ደረጃን የተማረው ደግሞ ከፍተኛ 12 ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ነው። የታደለ እናት እና አባት እንደማንኛውም የዘመኑ ሰዎች ልጆቻቸው በትምህርት እንዲበረቱ ቢፈልጉም የልባቸውን መሻት እንዲከተሉም ፈቅደዋል። በዚህም የተነሳ የታደለ ወንድም ዮሀንስ ፈለቀ ኪነ ጥበብ ይሞካክር ነበር። ታደለም ቢሆን ሙዚቃ የመሞካከር ዝንባሌ ነበረው። ትምህርት ቤት እያለ ዴስክ እየደበደበደ ጓደኞቹን የሚያዝናና ሲሆን፤ በዚህም የተነሳ ታደለ የኪነ ጥበብ ዝንባሌ እንዳለው ብዙ ሰው ይረዳ ነበር።
ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ከገባ በኋለ ታደለ በትምህርት ቤቱ ላሉ የሚኒ ሚዲያ አባላት በመላላክም በሌላም የሚያገለግል በመሆኑ የተነሳ ጥሩ ቅርበት ነበረው። አንድ ቀን በትምህርት ቤቱ ውስጥ ሚኒ ሚዲያው አዘጋጅቶ በነበረው የመዝናኛ መርሐ ግብር በሌላ ጉዳይ መድረክ አቅራቢያ ተገኝቶ የነበረው ታደለን ያዩ ተማሪዎች በጩኸት እና በፉጨት ታደለ እንዲዘፍን ገፋፉት። እሱም የተመልካቹ ግፊት በፈጠረለት ሞቅታ ተነሳስቶ ሊዘፍን ፈቃደኛ ይሆናል። አንድ የሳተው መሰረታዊ ቁምነገር ግን ከባንድ ጋር ለመዝፈን ሲነሳ በየትኛው ቅኝት እና ከፍታ ላይ እንደሚዘፍን ማሳወቅ ነበር። ይህን ሳይናገር ነው ለመዝፈን የተነሳው።
ስለዚህም ሙዚቃ ተጫዋቾቹ በመሰላቸው ቅኝት ላይ ሙዚቃውን መጫወት ጀመሩ። የሚጫወተው ዘፈን ደግሞ የታላቁ ድምጻዊ ምኒሊክ ወስናቸውን በግል እኔና አንቺ የተሰኘ ትልቅ ሙዚቃ ነው። ሙዚቀኞቹ ሙዚቃውን እየተጫወቱበት ያለው ከፍታ እና የታደለ የድምጽ አቅም አልተመጣጠኑም። ከታደለ ጉሮሮ የሚወጣው ድምጽ ከመቅጠኑ የተነሳ ሙዚቃውን እየተጫወተ ሳይሆን እየቀለደ ነበር የሚመስለው። ተመልካችም እየሳቀ ነበር። በመጨረሻ ታደለ በገጠመው ስህተት ደንግጦ እና አፍሮ ከመድረክ ወረደ። ያኔ የክበቡ አባል የነበረው ድምጻዊ አብርሽ ዘጌትም ታደለን ወደ ዳር ወስዶ አረጋጋው፤ አበረታታው። በቀጣይ መድረክ ላይ በድፍረት እንዳይወጣም መከረው።
ከዚያ በኋላ ታደለ እና ሙዚቃ ተኮራረፉ። በገጠመው ሀፍረት ምክንያት የትምህርት ቤቱ ተማሪ በሙሉ እንደሚስቅበት ስለተሰማውም ለሁለት ሳምንት ያህል ትምህርት ቤት ሳይሄድ ቀረ። ከዚያ በኋላ ትምህርት ቤት ሲሄድ ግን የሚሄደው ከተለመደው መንገድ ቀይሮ ተማሪ ሊሄድበት አይችልም ብሎ ባሰበው መንገድ ዙሪያ ጥምጥም ሆነ። ሰንብቶ የሀፍረት እና የድንጋጤው ስሜት ሲቀንስ ግን ለምን እንደዚያ ድምጼ ሊቀጥን ቻለ፤ የቱ ጋር ነው የተሳሳትኩት ብሎ ራሱን ጠየቀ። ስለዚህም ሙዚቃ መማር እንደሚገባው አሰበ። ነገር ግን ይህን ትምህርት ለማግኘት የመረጠው እዚያው ሰፈሩ ፈረንሳይ ውስጥ ባሉ ክበባት ሳይሆን ራቅ ብሎ ነው። ስለዚህም ጀርመን ኤምባሲ አቅራቢያ የሚገኝ አቦል የቴአትር እና ሙዚቃ ክበብ ገባ። እዚያ እየተሳተፈም ቅኝት፣ ምት፣ ፒች፣ ሬንጅ ወዘተ የመሳሰሉ ነገሮችን አወቀ። አንዳንድ የሙዚቃ መሳሪያዎችንም መጫወትን ተማረ።
12ኛ ክፍል ደርሶ ብሄራዊ ፈተና ከተፈተነ እና ወጤቱ ዩኒቨርሲቲ እንደማያስገባው ካወቀ በኋላ ግን ሌላ የህይወት እጥፋት ተከሰተ። እድሜው ለስራ ደርሷልና ስራ መስራት ስላለበት ከሙዚቃ ጋር ያለውን ቆይታ አቁሞ ቴሌ የጥገና ሰራተኛ ሆኖ ተቀጠረ። ታደለ እና ሙዚቃ የተለያዩም መሰለ።
አንድ ቀን ከስራ እረፍት አግኝቶ ሰፈሩ ውስጥ ዞር ዞር ሲል ግን አንድ ሰው አገኘ። ያ ሰው ደግሞ የድምጻዊት ትዕግስት ፋንታሁን ወንድም ኢዮብ ፋንታሁን ነው። ኢዮብ እግረ መንገዱን ላገኘው ታደለ አንድ ዜና ሹክ አለው። አብነት አካባቢ የሚገኝ ፕሮፕራይድ የሚባል ድርጅት ሙዚቀኛ እየፈለገ ነው እና ሄደን እንወዳደር አለው። ሄደውም ተወዳደሩ። ከብዙ ተወዳዳሪዎች መሀል ሁለቱ ጓደኛማቾች አለፉ፤ በ180 ብር ደሞዝም ተቀጠሩ። ታደለ በድጋሚ ወደ ሙዚቃ ተመለሰ። ፕሮፕራይድ ውስጥ እያለ የሙዚቃ ተሰጥኦውን አጠናከረ። ብዙ መሳሪያ መጫወትንም ለመደ። ከስራው ጎን ለጎንም የኮምፒውተር ሳይንስ ትምህርት ተምሮ ዲግሪውን ያዘ። ያኔ በሚሰራበት መስሪያ ቤት ከተመረቀበት ሙያ ጋር የተያያዘ የስራ እድገት ስለነበር ያን እድገት እንደሚያገኝ ገምቶ ነበር። ነገር ግን መስሪያ ቤቱ ሌላ ሰው ቀጠረ፤ ይሄኔ ታደለ አኮረፈ። ስምንት ዓመታት የሰራበትን መስሪያ ቤት ትቶም ወጣ።
ስራ ፈት በሆነበት ወቅት አንድ ቀን የቀድሞ መስሪያ ቤቱ አጋር የነበረች አንዲት ሴት አገኘ። ስራ ፈት እንደሆነ ሲነግራትም አዲስ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት እንዳቋቋመች ትነግረዋለች። ኮምፒውተር እና ሙዚቃ እንዲያስተምርላትም ትጠይቀዋለች፤ በደስታ እሺ ይላል። የስራ ቦታው ግን ዝዋይ እና ሆለታ ነው። በዚህ መልኩ ሁለቱም ከተሞች እየሄደ እያስተማረ ለሁለት ዓመታት ቆየ፤ ጥቂት ገንዘብም ያዘ። ይሄኔ ትልቁን እርምጃ ተራመደ። የራሱን ኪቦርድ ገዛ፤ ወንድሙ ዮሀንስ ፈለቀ ደግሞ አግዞት ስቱዲዮ ሰራ። (ዮሀንስ ፈለቀ ሳምራዊ 1 እና 2 ፊልሞችን ጨምሮ በርካታ ፊልሞችን የሰራ የጥበብ ሰው ነው)።
ከዚያን በኃላ ታደለ ራሱን ችሎ መቆም ጀመረ፤ አቀናባሪም ሆነ። መደበኛውን ሙዚቃም ቢሰራ ልቡ ግን ያመዘነው የፊልም ማጀቢያ ሳውንድ ስኮር ወደ መስራት ሆነ። ለዚህም የገፋፋው በልጅነቱ ፊልሞችን ሲያይ በፊልሞቹ ጀርባ የሚጫወተው ሙዚቃ በፊልሙ ላይ ያለውን ተጽእኖ በማስተዋሉ ነው። ስለዚህም እሱን ሊሰራ ፈለገ። ነገር ግን መስራት መፈለጉ ብቻውን በቂ አልነበረም። መስራት መቻል አለመቻሉን ማረጋገጥ አለበት። ያረጋገጠውም ቴሌ ባዘጋጀው አንድ የስልክ ሙዚቃ ላይ ተሳትፎ የእሱ ሙዚቃ በማሸነፉ ነው። በወቅቱ እሱ በሰራው ሙዚቃ ተገቢውን ሽልማት ባያገኝበትም እንኳ የሙዚቃው ማሸነፍ ግን የመስራት አቅሙ እንዳለው አሳየው። ከዚያም ወደ ስራው ገባ። እስከዛሬ ተዘርዝረው የማያልቁ ሳውንድ ስኮሮችንም ሰርቷል።
በቁጥር ለማስቀመጥ ያህል ከ80 በላይ ፊልሞችን እና ከ80 በላይ ዶክመንተሪዎችን በሙዚቃው አጅቧል። በታደለ የተቀናበሩ የዜና መግቢያ፤ ፕሮግራም መግቢያ እና መሰል ስራዎችም ተዘርዝረው አያልቁም። እሱ ሳውንድ ስኮር ከሰራባቸው ተከታታይ የቴሌቪዥን ድራማዎች ብንጠቅስ እንኳ በቅርቡ የተጠናቀቀው እረኛዬ፣ ደርሶ መልስ፣ ምን ልታዘዝ፣ ሞጋቾቹ ተጠቃሽ ናቸው። የነገን አልወልድም ፊልም ላይ በሰራው ሳውንድ ስኮር አራተኛው የጉማ አዋርድ ላይ አሸናፊ የሆነው ታደለ በጥላሁን እልፍነህ የተዜመው አይ ኮበሌ፤ በይግረም አሰፋ የተዜመው ዱራሜ ሺንሲቾ የተሰኙ ሙዚቃዎችን ጨምሮ በርካታ ሙዚቃዎችንም አቀናብሯል። በአሁኑ ወቅትም ከማቀናበር ስራው በተጨማሪ ራሱ ባቋቋመው ኮከብ የተሰኘ ባንድ የፋና ላምሮት የሙዚቃ ውድድር ላይ ተወዳዳሪዎችን በሙዚቃ በማጀብ ይሳተፋል። የውድድሩ መግቢያ ሙዚቃም የእሱ ቅንብር ነው።
ታደለ ባለትዳር እና የሁለት ልጆች አባት ነው። ባለቤቱ ወይዘሮ ካሰች ቢቂላ ትባላለች። የተገናኙበት መንገድ አስገራሚ ነው። ታደለ ካሰችን ከማግኘቱ በፊት ከአንዲት እንግሊዛዊ ጋር የፍቅር ግንኙነት ነበረው። ነገር ግን ግንኙነቱ ወደ ማብቃቱ ገደማ ነበር። በዚያው ወቅት ደግሞ አንድ ጓደኛው ከእጮኛው ጋር ሊጋቡ ዝግጅት ላይ ነበሩ። አንድ ቀን ቤታቸው ይጋብዙታል። የተጋበዘውም ስለ እነሱ ቀጣይ ሰርግ ለማውራት ነበር። እሱ ከሴት ጓደኛው ጋር እየተለያየ አንደሆነም በወሬ መሀል ይነሳና ሲወራ የጓደኛው እጮኛ እሷ ውጭ ሀገር የምትኖር ጓደኛ እንዳለቻት እና ስሟም ካሰች እንደሚባል በቅርቡም ሚዜዋ ልትሆን እንደምትመጣ ትነግረዋለች። ወሬውም እዚያ ላይ ያበቃል።
በሌላ ጊዜ ታደለ ፌስቡክ ሲጠቀም ያን ስም ያየዋል። የት እንደሚያውቀው ባያውቅም የጓደኛ እንሁን መጠየቂያውን ይልካል። ካሰችም የፌስቡክ ጓደኝነት ጥያቄውን ትቀበላለች። ማውራትም ይጀምራሉ። ካሰች ማለት የጓደኛው እጮኛ የነገረችው ሴት እንደሆነች ያወቀው ቆይቶ ነው። ሁለቱ በፍቅር ቀጠሉ ተጋቡ ልጆችም ወለዱ፤ አሁንም አብረው ይኖራሉ። አስገራሚው ነገር ታደለን እና ካሰችን ያስተዋወቁት እጮኛማቾች ለሰርጋቸው አፋፍ ላይ ደርሰው ሳይጋቡ መቅረታቸው ነው።
ታደለ አሁንም ቢሆን ብዙ ስራዎች እንደሰራሁ አይሰማኝም ይላል። ብዙ ሀሳቦችን ለመስራትም እቅድ ይዟል። በታደለ ስቱዲዮ ውስጥ በሌሎች ስቱዲዮዎች እንደተለመደው መቃም ማጨስ እና መጠጥ መጠጣት የማይፈቀድ ሲሆን እሱም ስራውን በፕሮግራም ቀን ላይ ጨርሶ ማታ ከቤተሰቡ ጋር ነው የሚያሳልፈው። ወደፊት በፊልሙም ሆነ በሌሎች ዘርፎች ፊት ለፊት ከሚታየው ሰው ጀርባ ያሉ ሰዎች እውቅና የሚያገኙበት ዘመን እንዲመጣም ተስፋ ያደርጋል።
አቤል ገብረኪዳን
አዲስ ዘመን ነሃሴ 29/2014