ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በሀገራችን እየተካሄደ ያለው ጦርነት የመረጃ ፣ የውክልናና የዲፕሎማሲ ጦርነቶችን ያጃመለ የግራጫ ጦርነት ነው ሲሉ ይደመጣሉ። ሰሞነኛው ወቅታዊ የሀገራችን ሁኔታም ይህን የሚያረጋግጥ ነው። አልሻባብና ኦነግ ሸኔ ግንባር ፈጥረው በምስራቁ የሀገራችን ክፍል ተደጋጋሚ ጥቃት እየሰነዘሩ ሲሆን ፤ ሱዳንም ድንበር ጥሳ ወረራ መፈጸሟ የሚዘነጋ አይደለም። ሕወሓትም ቢሆን ከጥፋቱ የመማር ባህሪ ስለሌለው የሰላም ጥረቱን ቅድመ ሁኔታ በመደርደር ሊያንኮላሸው እየኳተነ ነው ። በሀገራችን ላይ እየተነዛ ያለው የመረጃና የዲፕሎማሲ ዘመቻ ጋብ አለ እንጅ አላበራም። ከዚህ ሁሉ ጀርባ ታሪካዊ ጠላታችን ግብጽ አለች። የኤል ጋህድ ፓርቲ መስራችና ሊቀመንበር አብድልአዚዝ ኑር ኢትዮጵያን በማተራመስ ለማዳከም እነ ሕወሓትን መጠቀም ይገባል ሲል በአደባባይ መናገሩ የግብጽ መንግስት ደህንነት በሀገራችን ላይ እየዶለተ ያለውን ሴራ ገላልጦታል። በሀገራችን ላይ እየተቃጣ ያለው የሳይበር ጦርነትም የዚሁ ደባ አካል ነው። በዚያ ሰሞን በኢትዮጵያ ላይ የተከፈተው የመረጃ ጦርነት በሳይበር ደሕንነትና ሌሎች ተቋማት የጋራ ጥረት እየተመከተ መሆኑን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ማስታወቁ ግብጽ መቼም እንደማትተኛልን ያረጋገጠ ሀቅ ነው። በዛሬው መጣጥፌም እዚህ ላይ አተኩራለሁ።
በሀገራችን ጥንታዊ ታሪክ እንደ ግብፅ ተደጋጋሚ ወረራ ፣ ጥቃትና ዘመቻ የከፈተብን ሀገር የለም ። ከዛ ሩቅ ዘመን አንስቶ ግብፅ ተኝታልን አታውቅም ። አንድ ጊዜ በሰሜን ፣ ሌላ ጊዜ በሰሜን ምዕራብና በምስራቅ 11 ጊዜ ጦርነት ከፍታብናለች ። ይሁንና በሁሉም ወረራዎች በጀግኖች አባቶቻችን አከርካሪዋን ተመታ ፣ የውርደት ከሏን ተከናንባ ተመልሳለች ። ከቅርብ አመታት ወዲህ ደግሞ በእነ ሻዓብያ፣ ጀብሀ ፣ ወያኔ ፣ ኦነግ ፣ ኦብነግና ሶማሊያ የውክልና ጦርነት ስታደርግብን እንደነበር አይዘነጋም። የባህር በር እንድናጣ በዘር ተከፋፍለን እንድንዳከም ሌት ተቀን ሰርታለች። ድካሟ ከንቱ ሆኖ አልቀረም። እቅዷን አሳክታለች። የባህር በርና ቀይ ባህር ላይ ለእልፍ አእላፍ አመታት የነበረንን ባለቤትነት በእሷ በተቀነባበረ ሴራና ድጋፍ ማጣታችን ምን ያህል በቀጣናው ላይ የነበረንን ተፅዕኖና ጂኦ ፓለቲካዊ ሚዛን እንዳኮሰመነው ለማንም የተሰወረ አይደለም። በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ሳይቀር ለኤርትራ በገፍ የጦር መሳሪያ በማቅረብና ወታደራዊ እገዛ በማድረግ ተሳትፋለች።
ዛሬም በዲፕሎማሲያዊ መተላለፊያ / ኮሪደር / ከከፈተችብን የፈጠራ ክስና ሀገራችንን ከማሳጣት ዘመቻ ጎን ለጎን ፤ ባንዳዎቿን በውክልና በመጠቀም ሀገራችን ለማተራማስ ፣ ወደለየለት የእርስ በርስ ጦርነት ለመክተትና ለመበታተን ከመስራት አልቦዘነችም። በሱዳን ፣ በአልሻባብ ፣ በሕወሓትና በተላላኪዎቹ የውክልና ጦርነት እያካሄደችብን ትገኛለች። የዛሬ ትኩረቴ የሳይበር ጦርነቱ ላይ ስለሆነ ወደእሱ ልመለስ ። የሳይበር ጦርነት በአጭሩ እጅግ ጠቃሚ የሆኑ እንደ ፋይናንስ ተቋማት ፣ መከላከያ ፣ ደህንነት ፣ ቴሌኮም ያሉ ተቋማትን የበይነ መረብ የመረጃ ስርዓቶችን ከጥቅም ውጭ ማድረግ ነው ። ስለላ ማካሄድም የጦርነቱ አካል ነው። ራሽያ ከዩክሬን ጋር ጦርነት ውስጥ በመግባቷ አኖኒመስ የተባለ የሀክቲቪስቶች ስብስብ በራሽያ ላይ የሳይበር ጦርነት እንዳወጀው ፤ ግብጽም በህቡዕ የሳይበር ጦርነት ከከፈተችብን ከራርማለች።
የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ ቆየት ባለ አንድ መግለጫው ፤ “…መሰረታቸውን ከግብጽ ያደረጉ የመረጃ መረብ ሰርሳሪዎች ኢትዮጵያ ውስጥ በሚገኙ ተቋማት የመረጃ መረብ መዋቅር ላይ ጥቃት ለማድረግ ሞክረው ነበር።…” እንዳለው ተራ ሙከራ ሳይሆን የሳይበር ጦርነት ነው የተከፈተብን። በዋዛ ፈዛዛ ሙከራ በሚል ብቻ የሚታለፍ አይደለም። በሉዓላዊነታችን ፣ በደህንነታችንና በተቋሞቻችን የተቃጣ ጥቃት መሆኑ ሳይቃለል በልኩ ነው መታየት ያለበት። ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ በአንድ መድረክ በ21ኛው መክዘ ጦርነት የሚካሄድበት ጦርነት በየብስ ፣ በባሕርና በአየር ብቻ ሳይሆን በሳይበርና በስፔስ መሆኑን ጠቆም አርገው ነበር።
በebs የ” Tech Talk With Solomon “ አዘጋጅ ሰለሞን ሙሉጌታ ካሳ” ግርምተ ሳይቴክ “ በሚል ርዕስ በ2010 ዓ.ም ለንባብ ባበቃው መፅሐፍ ፤ “ የማይታየዉ ጦርነት “ በሚል ምዕራፍ ስር ገፅ 157 ላይ ፤ “…በ21ኛው ክፍለ ዘመን አዲስ አይነት ጦርነት ብቅ ብሏል ። ጦርነቱ የሚካሄደው በጥይትና በቦንብ ሳይሆን በሀከሮችና በኮምፒውተሮች ነው።… ይህ በአይን የማይታየው የሳይበር ጦርነት/ ዋርፌር / ነው። “ ሲል የጠቅላይ ሚንስትሩን ሀሳብ ያጠናክራል። እሳቸው ያሉት ነገር እንደ ዋዛ ደረሰና ግብፅን በአየር ፣ በየብስ ስንጠብቃት ፤ ምን አልባት ባልጠበቅነውና ባልተዘጋጀንበት ስስ ብልታቸው ይሆናል ብላ በገመተችው በሳይበር ግንባር ጦርነት ከፍታብናለች ። ጠቅላይ ሚንስትሩ ለርዕያቸውና አርቆ አሳቢነታቸው ምስጋና ይግባቸውና በእሳቸው ሀሳብ አፍላቂነት የተቋቋመው የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት ኤጀንሲ /ኢንሳ/መሰረታቸውን ከግብጽ ያደረጉ የመረጃ መረብ ሰርሳሪዎች በሀገራችን ተቋማት የመረጃ መረብ መዋቅር ላይ ጥቃት ለመሰንዘር ያደረጉትን ሙከራ አክሽፏል።
በኤጀንሲው የወቅቱ መግለጫ መሰረት በሦስት የተለያዩ ቡድኖች አማካይነት የተሞከረው የመረጃ መረብ ጥቃት በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጫናን ለመፍጠር ያነጣጠረ ነበር ። የጥቃቱ ሙከራ ባደረጉት ቡድኖች ላይ አበክሮ ክትትል በማድረጉ በ13 የመንግሥት እና አራት መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትን ድረ-ገጾችን ኢላማ በማድረግ የተሰነዘሩ ከፍተኛ የመረጃ መረብ የጥቃት ሙከራዎችን በቁጥጥር ስር ማዋል ችሏል ። ኤጀንሲው ኃላፊነቱን ስለተወጣ በዚህ አጋጣሚ እውቅና ልንሰጠው ይገባል ። የመረጃ መረብ ጥቃት ሙከራው የተደረገው ሳይበር ሆሩስ ግሩፕ ፣ አኑቢስ ዶት ሃከር’ እና ሴኪዩሪቲ ባይ ፓስ በተባሉ መረጃ መረብ ሰርሳሪ ቡድኖች ነው ። የጥቃቱ ኢላማ የነበሩት ተቋማት በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የመንግሥት ተቋማት ፣ የደኅንነት መስሪያ ቤቶች እና የግል ድርጅቶች ድረ-ገጽ ላይ መሆኑን ኤጀንሲው በመግለጫው አብራርቷል። ሆኖም ባልተለመደ ሁኔታ በአገሪቱ ባሉ ተቋማት የመረጃ መረብ ላይ ጥቃት ለማድረስ የሞከሩ ቡድኖች በግልፅ ኃላፊነቱን መውሰዳቸው ግብፅ ለሀገራችን ያላትን ንቀትና እብሪት የሚያሳይ ሆኖ አግኝቸዋለሁ ። ሌላው ኤጀንሲዉ የሳይበር ጥቃቱ አላማ ፤ “ በኢትዮጵያ ላይ በሁሉም አቅጣጫ ተጽእኖ ለማሳደር ነዉ፤” የሚለው ግምገማው ጥቃቱን አሳንሶና አቅልሎ ያየው እንዳይመስል እሰጋለሁ ። በቅጡም ሊመዘን ይገባል ።
ምክንያቱም የሳይበር ጥቃቱ ተፅዕኖ ከመፍጠር በላይ ተጠናክሮ የሚቀጥል ጦርነት ነውና ። አስቀድሞ ቅድመ ዝግጅት በማድረጉ የመረጃ መረብ ጥቃቱ ኢላማ በነበሩት ተቋማት ላይ ጉዳት አልደረሰም ። ጥቃቱን ማክሸፍ ባይችል ኖሮ በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ፤ ፖሊቲካዊ እና ሥነ ልቦናዊ ጉዳት ሊያስከትል ይችል እንደነበር ኤጀንሲው መግለጹ የሳይበር ጥቃቱን አደገኝነት አጉልቶ ያሳያል። ቀጣዩ አውደ ውጊያ በሳይበር ግንባር ስለሆነ የጦር እቃውን ታጥቀን ፣ የራስ ቁሩን ደፍተን ፣ ጡሩሩን ለብሰን፣ ጦሩን እየሰበቅን ፣ ዘገሩን እየነቀነቅን ተጠንቅቀን ልንጠብቅ ይገባል ። ከዚህ በኋላ የማይቀርልን እዳ/ ዘ ኒው ኖርማል / ነውና ። ሰሞነኛው የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት መግለጫም ይሄንኑ የሚያረጋገጥ ሆኖ አግኝቸዋለሁ። ግብጽ የሳይበር ጦርነቱን ቀጥላበታለች።
ለመሆኑ የመረጃ መረብ ጥቃት ሲባል ምን ማለት ነዉ? በሰለሞን ሙሉጌታ ካሳ “ ግርምተ ሳይቴክ “ መፅሐፍ ፤” የማይታየው ጦርነት “ በሚል ምዕራፍ ስር ገፅ 157 ላይ ፤ “… ሚስጥራዊ የሆነና ያልሆነን ዲጂታል መረጃን ከባለቤቱ ፈቃድ ውጭ መስረቅ ፣ ይዘቱን ማበላሸት ፣ ከእነ አካቴው ማጥፋት…” ሲል ይበይንና፤ ታሪካዊ ዳራውን እንዲህ ያብራራል ። “ከሙከራ ላብራቶሪ በዘለለ መልኩ የመጀመሪያው ‘ኤልክ ክሎነር’ የተባለ የግል ኮምፒዩተርን የሚያጠቃ ቫይረስ በ1982 ዓ.ም የ15 አመት ወጣትና የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ በነበረው አሜሪካዊው ሪቻርድ ስክሬንታ ከተፈጠረ ጊዜ ጀምሮ በኮምፒዉተር መረጃዎች ያነጣጠረ ‘ሳይበር’ ጥቃት በመንግስታት መካከል ጭምር ሳይቀር የሚካሄድ የሳይበር ጦርነት /ሳይበር ዋር / አሀዱ ብሎ ጀመረ ። በወቅቱ ኢንተርኔት ገና ለሕዝብ ጥቅም ያልዋለበት ጊዜ ስለነበር ወንጀሉ በስፋት አልተስተዋለም ። በ1980ዎቹና 90ዎቹ አጋማሽ ድረስ ጥቃቱ በብዛት ይሰነዘር የነበረው እንደ ‘ ፍሎፒ ዲስክ ‘ እና ‘ ሲዲ ‘ በመሳሰሉ ተንቀሳቃሽ የመረጃ ማስቀመጫ ቁሶች አማካኝነት ቫይረስ ከአንድ ኮምፒዩተር ወደ ሌላ ኮምፒዩተር በማስተላለፍ ነበር ።
በ1990ዎቹ አጋማሽ በኋላ የኢንተርኔት አጠቃቀም እያደገ ሲመጣ ጥቃቱም መልኩን ቀይሮ ብቅ አለ ። በ2003 ዓም ገደማ የሳይበር ወንጀል ፍፁም አዲስ በሆነ መልኩ ድረ ገጾችን የማጥቃት አላማ ይዞ ተነሳ ። ይህ የሆነበት ምክንያት በወቅቱ የኢንተርኔት ‘ኢኮሜርስ ‘ ግብይት ስርዓቱ እየተጧጧፈ በመምጣቱ ነው ። በተለይ የክሬዲት ካርድ ቁጥሮችን በመስረቅ ላይ ያነጣጠረ የሳይበር ወንጀል በ2000ዎቹ ተጧጡፎ ቀጠለ ። ከ2005 እስከ 2007 ዓ.ም ባለው ጊዜ አልበርት ጎንዛሌዝ የተባለ አደገኛ አሜሪካዊ የኮምፒዩተር ሀከርና የሳይበር ወንጀለኛ የተለያዩ ግዙፍ የንግድ ኩባንያዎችን የኮምፒዩተር ሲስተሞችን በማጥቃት ፤ የግለሰቦችን ክሬዲት ካርዶችን ቁጥር በመመንተፍ 45 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ዘርፏል ። …” ዛሬ የሳይበር ጥቃት ምርጫን ፣ ኢኮኖሚንና ማህበራዊ ግልጋሎትን በማስተጓጎል ውድ ዋጋ እያስከፈለ ይገኛል ።
ከፍ ብዬ የጠቀስሁት ደራሲና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያ በመፅሐፉ ይበልጥ እንዲህ ያብራራዋል ። “…የመረጃ ፍሰቱ አለምን ማጥለቅለቁ ፤ መንግስታትም አሰራራቸውን በኢንተርኔትና በኮምፒዩተር ማድረጋቸው ፤ መሰረተ ልማታቸውን የሚያስተዳድሩት ፤ መረጃዎቻቸውን የሚያስቀምጡት ፤ አገልግሎት የሚሰጡት እንዲሁም ታላላቅ ወታደራዊና የደህንነት መረጃዎችን በዲጂታል መልክ መያዛቸው ለጥቃት አጋልጧቸዋል ። የእንግሊዝ የደህንነት ተቋማት እነ ኤም አይ ፋይፍና ኤም አይ ሲክስ እንዲሁም የአሜሪካው ኤፍ ቢ አይ የሳይበር ጥቃትን ከፍተኛ የጸጥታ ስጋት አርገው ወስደው መስራት ከጀመሩ ውሎ አድሯል ። … “
እንደ መውጫ
የሳይበር ጥቃት በሚቀጥሉት ጥቂት አመታት እስከ ስድስት ትሪሊዎን ዶላር የሚደርስ ኢኮኖሚያዊ ጉዳት እንደሚያስከትል ጥናቶች አበክረው ይተነብያሉ። ከአለማቀፍ ሽብርተኝነት ባልተናነሰ የደህንነት ስጋት እስከ መደቀንም ደርሷል ። አለም በሉላዊነት / ግሎባላይዜሽን / እና በኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ወደ ትንሽ መንደርነት በተቀየረችበት የሳይበር ጥቃትና ጦርነት ለሀገራችንም ስጋት መሆን ከጀመረ ሰነባብቷል ። በንግድ ባንክ በተደጋጋሚ የተቃጡ ጥቃቶች ፤ የፈተና ስርቆት በተማሪዎች ስነ ልቦና እንዲሁም በጊዜያቸው ላይ ያስከተለው ጉዳት እንዳለ ሆኖ በሀገር ኢኮኖሚ እና በተቋማት አመኔታ ላይ ጥያቄ ማስነሳቱ አልቀረም ።
የሳይበር ጥቃት በተደጋጋሚ የሚሰነዘር ቢሆንም መከላከል እንደሚቻል የዘርፉ ባለሙያዎች ይገልጻሉ። ሆኖም 99 በመቶ የሚሆኑ ድርጅቶች ለሳይበር ጥቃት የተጋለጡ ናቸው። የሀገራችን ተቋማት ይህን ተጋላጭነታቸው መቀነስ ላይ አበክሮ መስራት ይጠበቅባቸዋል። በተለይ የደህንነት ፣ የፋይናንስ ፣ የኤሌክትሪክ ኃይልና የሚዲያ ተቋማት ልዩ ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። የሳይበር ጥቃት ዋና መከላከያ ዘዴ ከጫፍ ጫፍ ሁሉንም ኔት ወርኮች ፣ ተንቀሳቃሽ ስልኮችንና የመረጃ መነሻና መዳረሻዎችንና ክላውዶችን ታሳቢ ያደረገ ተጋላጭነት የመቀነስ ስራ መከወን ነው። ጠንካራ የሳይበር መከላከያ ፣ ጥቃቱን መለየት ላይ ከማተኮር ይልቅ መከላከል ላይ በማተኮር ፣ ጥቃት ሊቃጣባቸው የሚችሉ አሰራሮችን በመከላከል ፣ የመጨረሻውን ቴክኖሎጂ በመጠቀም እና ስለ ስጋት ምንጮች ወቅታዊ ግንዛቤ መጨበጥ ከዋና ዋናዎቹ የመከላከያ ዘዴዎች የሚጠቀሱ ናቸው።
ግብፅ ለከፈተችብን ተደጋጋሚ ወረራ ጀግኖች አባቶቻችን አይቀጡ ቅጣት ቀጥተው አሳፍረው እንደመለሷት ፤ ለሳይበር ጥቃቷም አስተማሪ የሆነ የመልስ ምት መስጠት ያስፈልጋል። አገልግሎቷ ፣ አሰራሯና የመረጃ አያያዟ ከእኛ በብዙ እጥፍ ዲጅታል ስለሆነ ለመልስ ምቱ የተመቸ ነውና።
ሀገራችን ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ፈጣሪ አብዝቶ ይባርክ ! አሜን።
በቁምላቸው አበበ ይማም (ሞሼ ዳያን)fenote1971@gmail.com
አዲስ ዘመን ሰኞ ነሐሴ 2 ቀን 2014 ዓ.ም