አሁን አሁን አለማችን የምትገለፅበት ቋንቋ ከወትሮው የተለየ ነው። ምናልባትም ዘመን አፈራሹ ቴክኖሎጂ የፈጠረው፤ አልያም የዲፕሎማሲው ጉዳይ ብቻ አለማችን እየ”ጠበበች” (ወደ አንድ መንደርነት እየመጣች) እንጂ እየሰፋች አይደለም። ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” የሚለው አባባል በሁሉም ዘንድ ማለት በሚቻል ደረጃ እየተለመደ ብቻ ሳይሆን እየተዘወተረ ይገኛል። በፊት ”ሶስተኛው አለም” (አፍሪካን)፣ ”የሰለጠነው አለም” (ምእራቡን)፣ ”መካከለኛው ….” ወዘተ እየተባለ እንዳልተሸነሸነ ሁሉ፤ ዛሬ (ቢያንስ በሰነድ፣ በቃል ደረጃ) ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” ወደ’ሚለውና አብረን እንስራ፣ አብረን እንሁን፣ የጋራ ደህንነታችንን እናስጠብቅ፣ የጋራ ተቋማት እንገንባ … ወዘተ የሚለው ነገር የመንግስታት የእለት ተእለት ተግባርና አሳሳቢ ጉዳይ ሆኗል።
ረቂቁና የአንድን ወገን የበላይነት ለማስቀጠል ታስቦ የተወጠነ መሆኑ የሚታመንለት ”አዲሱ የአለም ስርአት” (New World Order) እንኳን በማይዘወተርበት ደረጃ ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” የሚለው ሰፊውን የአየር ሰአት ይዞ ነው የምናገኘው። ታዲያ ይህ ሁሉ ይባል እንጂ አንድ መንደርነቷን መቀበል የማይፈልጉ፤ የተከፋፈለች አለምን መፍጠር የሚፈልጉ አካላት የሉም ማለት አይቻልም። አለምን ቀርቶ አገርን ሳይቀር ለማፍረስና ፍርስራሿንም እያነደዱ መሞቅ የሚፈልጉ ድኩማን የሉም ማለትም አይቻልም።
ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ግን ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” ከሚለው ብዙም መሰረታዊ ልዩነት በማይታይበት ደረጃ ”ግሎባላይዜሽን” የሚለው ፅንሰ ሀሳብም መቀንቀን ከጀመረ ሰነባብቷል። ምንም እንኳን በጥንቃቄ ካልያዙት፣ በብልሀት ካላስተናገዱት በኒዎሊብራል አስተሳሰብና ፍላጎት መዋጥን ያስከትላል የሚለው ነገር አስፈሪ ቢሆንም፤ ቢያንስ በአስተሳሰብና ፅንሰ ሀሳብ ደረጃ የሚያስተላልፈው መልእክት ቢኖር ቀደም ሲል ያልነውን፤ ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” የሚለውን ባልተነጣጠለ አለም ውስጥ ስለሚኖረው አንድ ህዝብ ነውና ይዘን ከተነሳነው ሀሳብ ጋር የሚጣላ አይደለም።
”አለም አንድ መንደር ሆናለች” ከሚለው እሳቤ በተጓዳኝ ደግሞ፤ አለማችን ወዴት እየሄደች እንደሆነና አንዳንዶቻችን በተቃራኒው ወዴት እየሄድን እንደሆነ ማየቱ ተገቢ ይሆናል። ምክንያቱም ዛሬ አለማችን አንድ መንደር ሆናለች ቢባልም፤ አንድ በሆነችው መንደር ውስጥ ይህች መንደር የምትመራበት የተለያየና የተበጣጠሰ ርዕዮት እየናጣት መሆኑን በመገንዘብ ነው።
እንደሚታወቀው፣ አለማችን ከኃይማኖትም፣ ከባህልም፣ ከጎበዝ አለቃም … አመራር ተላቅቃ ለፖለቲካው እጇን ከሰጠች ቆየች። ፖለቲካውም በስመ ዲሞክራሲ በምሎ በመገዘት አለምን የመምራት ሀላፊነቱን ከተረከበ ቆየ። ችግሩ የመረከብና ማስረከብ፤ ወይም፣ የመረካከብ ጉዳይ አይደለም። ችግሩ ያለው ፖለቲካው ዘመኑን በመጠነ መልኩ መምራት አለመቻል/መቻሉ ላይ ነው።
እንደሚታወቀው፣ አለማችንን ሊመራት የሚገባው ፖለቲካው ነው፤ ፖለቲካውም መመራት ያለበት በፖለቲከኞች ነው፤ የሚል አስተሳሰብ አለ። ይህንን ተከትሎም በዛን ዘመን የነበሩ ቅን አሳቢዎች አዎ ፖለቲካና ፖለቲከኞች የመሪነት ስፍራውን ሊይዙ ይገባል (ፕሌቶ (Republic) እና ተከታዮቹ ባይደግፉትም – ”philosopher king”ን ያስታውሷል) አሉ። ይሁን እንጂ አማራጭ ፖለቲከኞችና አማራጭ ሀሳቦች ያስፈልጋሉ። ይህም የሀሳብ ፍጭትን በመፍጠር የተሻለና ህዝብን የሚጠቅም ስራ ይሰራ ዘንድ ያበረታታል። በመሆኑም ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች መኖር አለባቸው የሚል ”ድምዳሜ” ላይ ተደረሰ። ተደርሶም ወደ ተግባር ተገባ። ይህ እሳቤ እንዳለ ቢሆንም፤ በአሁኗ የአለማችን ይዞታ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችን የማያስተናግድ አገርም ሆነ ሕገ-መንግስትና መንግስት` በአጭር አገላለፅ ዲሞክራት መንግስታት አይደሉም፤ ወይም አምባገነን ስርአት/አገዛዝን በህዝባቸው ላይ የጫኑ ፀረ-ዲሞክራት ኃይሎች ናቸው የሚል የጋራ ግንዛቤ ነው ያለው።
ችግሩ ይህ አይደለም። እኔም ይሄን ለመሞገት አይደለም። ምክንያቱም አስቀድመን ከላይ እንዳልነው፣ ”አለም አንድ መንደር ሆናለች”። ባትሆንም እንኳን ወደ’ዛው እየሄደች ነው ተብሎ ይታሰባል። ዩሮ (ገንዘብ) የዚህ አንዱ ማሳያ ነው። ቻይና እየገነባች ያለችው የባቡር መስመርም (ሮድ ኤንድ ቤልት) ሁለተኛው ነው። አፍሪካን አንድ የማድረግ ጥረትና እንቅስቃሴውም እንደዛው።
የዚህ ጽሑፍ ዐቢይ አላማ ተቃዋሚነት ከዘመናዊነት ጋር ለምን ይጣላል? ለምንስ በተቃራኒ ይቆማል? በተቃራኒ ቆሞስ ለምን ከሰላም ይልቅ ተቃርኖን ያነግሳል? ተቃውሞው ለፉክክር መሆን ሲገባው ተቃውሞው ለምን ለመበላላት፣ ለመጨራረስ… ይሆናል? እና የመሳሰሉትን ትዝብትና ብስጭት አዘል ጥያቄዎችን ለማንሳትና የሚመለከታቸው እንዲያስቡበት ለማሳሰብ ነው። ገጣሚው ”… ምናልባት ቢያስፏጨው” እንዳለው ማለት ነው።
ከላይ ለ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” ማሳያ ይሆነን ዘንድ ከመልካም ተግባራት መካከል በሁሉም ሰው ዘንድ ይታወቃሉ ያልናቸውን አቅርበናል። ይሁን እንጂ፣ ከእነዚህ መልካም ካልናቸው ተግባራት የበለጠ አለማችን አንድ መንደር መሆኗን፤ ህዝቦቿም አንድ ህዝብ መሆናቸውን የሚያመለክቱ በርካታ መከራዎች ነበሩ፤ አሉም። ወደፊትም ይኖራሉ፤ እንደ አንዳንዶች ትንበያ የወደፊቶቹ ይብሳሉ።
ከእነዚህ ”አለም አንድ መንደር” መሆኗን ከሚያሳዩ መከራዎች መካከል ሊጠቀሱ የሚገባቸው በርካታ መከራዎች ቢኖሩም፣ ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ ሰዎች ግን የሚጠቅሷቸው የቅርብ ማስረጃዎች አሏቸው። አንዱና የዘመናችን የሰው ልጅ መቅሰፍ የሆነፍ ኮቪድ-19 (ኮሮና) ነው። በዚህ ባለንበት ዘመን እንደዚህ ቫይረስ የአለምን ህዝብ አንድ ያደረገ፤ በአንድ ሳንባ እንዲተነፍስ፣ በአንድ አንደበት እንዲናገር፣ ለአንድ መፍትሄ እንዲረባረብ፤ ለአንድ መመሪያ እንዲገዛ፣ በአንድ መመሪያም እንዲተዳደር፣ ለአንድ ነገር እንዲተጋ፣ አንድ ነገርንም እንዲያደርግ… ያደረገ የጋራ ጠላት (ቫይረስ) የለም። ኤችአይቪ/ኤድስ… እና ሌሎችንም ከዚሁ ጋር አያይዞ መግለፅ ይቻላል።
ይህ ብቻም አይደለም፤ ”አለም አንድ መንደር ሆናለች” ሲባል መገለጫውም ሆና ማሳያው ብዙ ሲሆን፤ ከብዙዎቹም ጥቂቶቹ የአየር ንብረት ለውጥ፤ ሽብርተኝነት፤ ፅንፈኝነት፤ ወንጀለኛነት፣ የሕዝብ ቁጥር እየጨመረ መሄድ፣ የስፖርት መስፋፋት… ወዘተርፈ ናቸው።
እነዚህና ሌሎች አሁን እኛ የማናውቃቸው ሁሉ አለምና የአለም ሕዝብ፣ ወደደም ጠላም እጅ ለእጅ እንዲያያዝ፤ ትከሻ ለትከሻ እንዲደጋገፍ፣ ሀሳብ ለሃሳብ እንዲረዳዳ፣ በድንበርና ማንነት ስም እንዳይታጠር፣ ተነጣጥሎ ሳይሆን በጋራ እንዲቆም… የሚያደርጉ ናቸው። ጥያቄው እነዚህን ሁሉ ለመቋቋም፤ መፍትሄያቸውንም ለማፍለቅ…. የሚበጀው ባልተነጣጠለ አለም ውስጥ ያልተበጣጠሰ ርእዮት አለምን በማራመድ ነው።
የፖለቲካ ፓርቲዎች ያስፈልጋሉ ወይ? ብለን ከጠየቅን ወደድነውም ጠላነውም መልሱ ”አዎ፣ ያስፈልጋሉ” ነው። ችግሩ ምን አይነት ርእዮት የያዙት ይምጡልን የሚለው ነው። ወደዱትም ጠሉትም እኛ የምንፈልገው ከዘመኑ ጋር የዘመነና ”አለም አንድ መንደር” መሆኗን ከልቡ የተረዳውን የፖለቲካ ፓርቲ (ተቃዋሚም ይሁን ሌላ) እንጂ አንድ በሆነ ህዝብ ውስጥ የተበጣጠሰ ርእዮት አራማጅን አንፈልግም (እንደ Croly (The Rise and Fall of Political Parties in Americaን አንብብ) አይነት አስወጋጅ አቀቋምን ባንይዝ እንኳን)። እኛ ብንፈልገው እንኳን ሄዶ ሄዶ በራሱ ጊዜ የሚጠፋ (የሚከስም) ነውና እኛ ባንለው እንኳ እራሱ ሊያስብበት ይገባል።
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን ሰኞ ነሐሴ 2 ቀን 2014 ዓ.ም