እነሆ ዛሬ ሰኔ አንድ ብለን የክረምቱን ወራት ጀምረናል። በኢትዮጵያ የወቅቶች ምደባ የክረምት ወር የሚጀምረው በሰኔ ነው። ሰኔ፣ ሐምሌ እና ነሐሴ ማለት ነው።
የክረምት ወቅት ደግሞ ለኢትዮጵያ ምን ማለት እንደሆነ ግልጽ ነው። ክረምት ማለት ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚያችን ዋልታና ማገር የሆነው የግብርና ሥራ የሚሰራበት ነው።
የዛሬው የክረምት መግባት ያስታወሰኝ ታዲያ የገበሬውን ሕይወት ነው። የገበሬውን ሕይወት ሳስታውስ ባለፉት ሳምንታትና ወራት ‹‹ምግቤን ከጓሮዬ›› በሚል በመንግሥት ደረጃ የተጀመረው የከተማ ግብርና ትዝ ያለኝ።
‹‹ምግቤን ከጓሮዬ›› በሚል በመንግሥት ደረጃ የተጀመረው የከተማ ግብርና እንቅስቃሴ በአንዳንድ ወገኖች ሲተች ነበር። ምክንያቱ ደግሞ ‹‹የትኛውን ትርፍ ቦታ ነው አትክልት የምንተክልበት›› የሚል ነበር። በመንግሥት በኩል ይባል የነበረው ደግሞ በተለያዩ መገልገያ ዕቃዎች መጠቀም እንዳለብን ነው።
ለዚህ የከተማ ግብርና እንቅስቃሴ ገበሬውን ነው ምሳሌ ማድረግ ያለብን። እርግጥ ነው ገበሬ ከዚህ ቀደም በመገልገያ ዕቃዎች ላይ አልጀመረም፤ ዳሩ ግን የእጅ መዳፍ የምታክል መሬትን እንዴት እንደሚጠቀማት ማየት ችግር ብልሃትን እንደሚወልድ ያሳያል።
በገጠር አካባቢ አሁን አሁን የእርሻ መሬት እየተወደደ ነው። ትልልቅ አባቶች የአሁን ወጣቶችን እያዩ ይገረማሉ። የሚገረሙበት ምክንያት፤ ቀደም ሲል ለእርሻ የማይውለውን መሬት ለእርሻ ሲያውሉ አይተው ነው። ቀደም ሲል በነበረው ዘመን የሚታረሰውና የማይታረሰው መሳ ለመሳ (እኩል) ነበር፤ እንዲያውም የማይታረሰው ሊበልጥ ይችላል። አሁን ግን እንደዚያ ብሎ ነገር የለም፤ የእግር መርገጫ የምታክል መሬት ሳትቀር ገበሬዎች እየፈቀፈቁ ያርሷታል።
‹‹ይህ ለምን ሆነ?›› ከተባለ፤ ችግር ነው ያስተማራቸው። ወጣቱ ገበሬ የእርሻ ማሳ ሲጠበው የፈጠረው መላ ነው። አባት ገበሬ መሬት ለልጁ አካፍሎ ሲጠበው ችግር ያመጣለት ዘዴ ነው። ቀደም ባሉት ዘመናት ከመኖሪያ ቤት አቅራቢያ ላይታረስ ይችል ነበር፤ አሁን ግን እስከ ቤቱ አጠገብ ድረስ ይታረሳል። እንደመሬቱ ባህሪ የሚስማማውን እህል ይዘራል ማለት ነው። ይህ ለምን ሆነ ከተባለ ችግር የወለደው መላ ነው።
በነገራችን ላይ ‹‹የሥልጣኔ ምንጩ ችግር ነው›› ነው የሚባለው። የሰው ልጅ ዋሻ ውስጥ ይኖር ከነበረበት ዘመን አንስቶ እስከ ዛሬው ረቂቅ ዓለም ድረስ የተለያዩ የፈጠራ ሥራዎችን አሳይቷል። እነዚህን ሥራዎች የፈጠራቸው ችግር ነው። ግዑዝ አካላትን አፋጭቶ እሳት ከመፍጠር እስከ ኤሌክትሪክ ድረስ፣ በእንስሳት ጀርባ ከመሄድ በሰማይ የሚበር አውሮፕላን እስከ መፈልሰፍ የደረሰው ችግር እያስተማረው ነው።
አንዲት የቅርብ ምሳሌ ብቻ እንውሰድ። ኮቪድ-19 በዓለም ብሎም በአገራችን ሲከሰት ከፍተኛ ጭንቀት ነበር። ቫይረሱ በእጅ ንክኪ እንደሚተላለፍ ሲታወቅ በእጅ መነካካት አስፈሪ ሆነ። ይህ ችግር ቀደም ሲል በእጅ እየከፈትን እንታጠብ የነበረውን ልማድ የሚያስቀር ዘዴ ወለደ። ይህን ዘዴ ለብዙ ዓመታት አላሰብነውም ነበር። ግን ችግር ብልሃትን ይወልዳል ስለሚባል ሲጨንቀን ያንን ዘዴ ፈጠርን። እርግጥ ነው ሁሉም ሰው እንዲህ አይነት ዘዴ ይመጣለታል ማለት አይደለም፤ ጥበብና ማስተዋልን ይጠይቃል።
ስለዚህ የከተማ ግብርና ችግር የወለደው ዘዴ ነው። አዎ! በበሬ ወይም በትራክተር የሚታረስ ሰፊ መሬት ቢኖር ጥሩ ነበር፤ ግን የለም! ስለዚህ መሬትም ምግብም እንጣ? እንዲህ አይነት ችግር ሲያጋጥም ችግሩን የምንወጣበት ዘዴ እንፈልጋለን ማለት ነው። የመገልገያ ዕቃዎች ውስጥ አፈር እያደረግን በየግድግዳውና አጥሩ ላይ እንሰቅላለን ማለት ነው። ከገበሬው ማሳ እንደሚታረሰው በኩንታል የሚታፈስ ምርት ባናመርትም የዕለት ምግብ ማምረት ይቻላል ማለት ነው።
ችግሩ ግን አዲስ ነገር በተጀመረ ቁጥር ማጣጣል ይቀናናል። የማይቻልና መሆን የሌለበት ነገር አድርገን ነው የምናየው። የእርሻ መሬት ችግርን ለመቅረፍ መፍትሔው በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መጠቀም እንጂ ማጣጣል አይደለም።
እዚህ ላይ ግን መንግሥትም አንድ ልብ ማለት ያለበት ነገር አለ። በቤትና በጓሮ ውስጥ በመገልገያ ዕቃዎች ላይ የሚተከል አትክልት ችግር ፈቺ አይደለም። በሄክታር የሚቆጠር ሰፋፊ መሬት በፀጥታ ችግር ምክንያት ከእርሻ ውጭ ነው። በዋናው ጦርነትም ሆነ በአካባቢያዊ ሽፍቶች የተፈናቀሉ ብዙ ገበሬዎች አሉ። እነዚህ ገበሬዎች ወደ ከተማ እየተሰደዱ ለልመና ተዳርገዋል። አርሶ የሚያበላው ወገን እየተፈናቀለ በጣሳ እና በፕላስቲክ የሚተከል ጎመን ችግርን አይቀርፍም።
‹‹ምግቤን ከጓሮዬ›› የከተማ ግብርና ከአንዳንድ ወገኖች ትችት ያገጠመው ዋናው አምራች ገበሬ ሁኔታዎች ይመቻቹለት በሚል ነው። ምክንያቱም በአገር ደረጃ ያለው ችግር የሚቀረፈው በተለመደው በበሬም ሆነ በዘመናዊው ትራክተር በሚታረሰው እንጂ ግድግዳ ላይ በሚንጠለጠል የውሃ ፕላስቲክ አይደለም። ስለዚህ መንግሥት ለዋናው አምራች ገበሬም ከፍተኛውን ትኩረት መስጠት አለበት።
ምናልባት አሁን የተጀመረው ሕግ የማስከበር እንቅስቃሴ ይህን ችግር ይቀርፍ ይሆናል። ከዚያ በፊት ግን በብዙ አካባቢዎች ገበሬው የእርሻ ማሳውን ለሽፍታ እየለቀቀ ወደ ከተማ ቦታ ሲገባ ነበር። አዲስ አበባ ውስጥ በየትኛውም አቅጣጫ ብትወጡ በየመስመሩ ዳር እጁን ለልመና የዘረጋ ገበሬ ነው የምታዩት። ይሄ ገበሬ የአገሪቱ የኢኮኖሚ ዋልታ የሆነው የግብርና መሰረት ነበር። ስለዚህ ሁኔታዎች ተመቻችተውለት ቶሎ ወደ እርሻው መመለስ አለበት። ለአገር የሚበቃው ገበሬ እጁን ለልመና ዘርግቶ በፕላስቲክ በጣሳ በሚተከል የጓሮ አትክልት ብቻ ኑሮን ማሻሻል አይቻልም።
ስለዚህ መሆን ያለበት ሁለቱም ነው። ገበሬው በሰፊው ይረስ፣ የከተማ ነዋሪው ደግሞ ያለችውን አጋጣሚ ሁሉ በመጠቀም በትንሹም ቢሆን ራሱን ይቻል። እንደዚያ ከሆነ ችግርን በጋራ መጋፈጥ ይቻላል ማለት ነው። ገበሬው ለልመና ከተዳረገ፣ የከተማው ነዋሪ በገበሬው ላይ ጥገኛ ሆኖ ከቀረ፤ ተያይዞ መውደቅ ሆነ ማለት ነው።
ቀደም ሲል እንዳልነው ችግር ነው ብልሃትን የሚያስተምረው። ለምሳሌ ቤታችን ሰፊ ሲሆን እና ጠባብ ሲሆን የቤት ውስጥ ዕቃ አቀማመጣችን ይለያያል። ቤታችን ሰፊ ከሆነ፤ እያንዳንዱ ዕቃ ራሱን ችሎ ይቀመጣል። ጠባብ ሲሆን ግን አንዱን በአንዱ ላይ እያነባበርን እናስቀምጣለን። በሥርዓት በሥርዓት እንደረድራቸዋለን። ለዕቃዎቹ አቀማመጥም ምቹ ይሆናል ማለት ነው። በሰፊ ቤት ውስጥ ግን በቂ ቦታ ስላለ በሥርዓት ከመደርደር ይልቅ ያገኘንበት እንጥለዋለን።
የእርሻ ቦታዎችም ልክ እንደዚሁ ነው። ሰፊ የእርሻ ማሳ በነበረበት ጊዜ የአረምና ድንጋይ መጣያ ይበዛል። የእርሻ ማሳው ጠባብ ሲሆን ግን እርከን ይሰራሉ፤ ድንጋዩ በሥርዓት ይደረደራል፤ አረምና ሌሎች ነገሮችም በሥርዓት ተለቅመው አንድ ቦታ ብቻ ይቀመጣሉ።
አጠቃላይ የጓሮ አትክልት ‹‹ችግር ብልሃትን ይወልዳል›› በሚለው ነውና እንልመደው!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ሰኔ 1/2014