አሜሪካ ወይም አውሮፓ አገራት መኖር የምመኘው የተደላደለ ኑሮ ለመኖር አይደለም። ፒዛና በርገር ለመብላት ወይም ፈጣን የቴክኖሎጂ አማራጮችን ለመጠቀም አይደለም። ከዚህ በላይ የሚያጓጓኝ ንጹህ አየር መተንፈስ ነው። የዓለም ምርጥ የአየር ንብረት ያላት አገር ውስጥ ሆኖ፣ ተፈጥሮ ያደላላት የሚመስል ምቹ የተፈጥሮ ሀብት ያላት አገር ውስጥ ሆኖ፤ በሰው ሰራሽ ዓለም ውስጥ የሚኖሩ አገራትን አየር መናፈቅ ምንኛ መረገም ይሆን?
ደፈር ብለን እንናገረው ከተባለ ለዚህ ሁሉ የዳረገን መሃይምነት ነው። መሃይምነት ሲባል መጻፍና ማንበብ የማይችል ማለት አይደለም፤ ዲግሪ የደራረበ ብዙ መሃይም አለና።
የሰሞኑ የአየር ሁኔታ ነፋስና ፀሐይ የበዛበት ነው፤ በኢትዮጵያ የአየር ሁኔታ ይህ የተለመደ የግንቦት ወር ባህሪ ነው። ተፈጥሯዊ ክስተት ነው።
አደገኛ የሆነው ግን ይህ ሳይሆን በሰው ሰራሽ መንገድ ያበላሸናቸው ነገሮች ናቸው። ከተፈጥሯዊው የአየር ሁኔታ ጋር ተዳምሮ ብዙ ሰዎች ሰሞኑን ጉንፋን ተይዘዋል። ጉንፋን ቀላሉ ነው፤ ብዙ ሰው የአስም ህመምተኛ ነው። ይህ ሁሉ የሚሆነው በቆሻሻ በሚፈጠር መጥፎ ሽታ ነው።
አዲስ አበባ ውስጥ አፍንጫ ሳይያዝ የሚታለፉ ወንዞች የሉም። ቱቦ ባለበት ቦታ ያለፈ ሁሉ ጉንፋን ተይዞ ወይም ከፍተኛ የራስ ምታት አጋጥሞት ነው የሚያልፍ። ድልድዮች ባሉበት ሁሉ አጸያፊ ነገር እያዩ ማለፍ የተለመደ ሆኗል። በየቦታው ሽታ አለ። ይህ ወቅት ደግሞ ከፍተኛ ነፋስና ፀሐይ ያለበት ስለሆነ ለብዙ በሽታዎች አጋላጭ ነው። የዝናብ ወቅት ሲሆን ቢያንስ ዋና ዋናውን ዝናብ ሊያጥበው ይችላል፤ ሽታውም የከፋ አይሆንም።
ይሄ ሁሉ የሆነው እንግዲህ በግንዛቤ ማጣት ነው። በሰው ሰራሽ መንገድ ነው እየታመምን ያለነው። የጽዳት ባህላችን ደካማ ነው። የዕለት ከዕለት ሥራ መሆን የሚገባውን ጽዳት፣ በዘመቻ ነው የምናጸዳው።
ብዙ ነገሮችን የምናደርገው ዓመት ጠብቀን ነው። ለምሳሌ ዕቅድ የምናወጣው አዲስ ዓመት (መስከረም) ሲደርስ ነው። መስከረም ካለፈ በኋላ፤ እንኳን አዲስ ዕቅድ ማውጣት የታቀደውም ይረሳል። የበጎ አድራጎት ሥራዎችን (ለምሳሌ ህሙማንንና አቅመ ደካሞችን መርዳት) የምንሰራው እንደ እንቁጣጣሽ፣ ገና፣ ፋሲካ፣ መውሊድ ወይም አረፋ ያሉ በዓላት ሲመጡ ነው። እነዚህ በዓላት ሲያልፉ ይረሳል።
ብዙ ነገሮችን የምናደርገው አሁንም ሁነት ጠብቀን ነው። ለምሳሌ ከተሞች የሚጸዱት በከተማዋ ውስጥ የሆነ ዝግጅት የሚደረግ ከሆነ ነው። ለምሳሌ የብሔር ብሔረሰቦች ቀን፣ የከተሞች ሳምንት ወይም ሌላ መንግስታዊም ሆነ ሕዝባዊ በዓላት የሚደረጉ ከሆነ የዚያን ሰሞን ቀለሞች ይቀባሉ፤ ቆሻሻዎች ይጸዳሉ። ያ ዝግጅት ሲያልፍ ግን አይቀጥልም፤ እንዲያውም ይባስ ብሎ በዝግጅቱ ምክንያት የወዳደቁ ተረፈ ምርቶች የሚያቆሽሹት ይበልጣል።
በየዓመቱ ‹‹ህዳር ሲታጠን›› እየተባለ በየቦታው ቆሻሻ ይቃጠላል (ሌላ ቀን አይደረግም እንጂ)፤ ዋና ዓላማውም ቆሻሻን ማቃጠልና ጽዱ አካባቢ መፍጠር ነው።
እንዲህ አይነት አጋጣሚዎች የማንቂያ ምክንያት ይሆኑናል። ቢያንስ በእንዲህ አይነት አጋጣሚ እንኳን አስታውሰን መነቃቃት ቢፈጠር ማለት ነው። ልቦና ቢሰጠን ደግሞ በዚያው ቢለምድብን ጥሩ ነበር፤ ግን አልሆነም።
በነገራችን ላይ በዓመት አንዴ የሚደረገው ህዳር ሲታጠን እንኳን በዕለቱ የሚኖረው የቆሻሻ ማቃጠል ራሱን ችሎ ሌላ ብክለትም ሲሆን ይታይ ነበር። ከንጹህ አየር ፍለጋ ባህላችን ይልቅ ባህላዊ ለሆነው ልማድ ተብሎ ነበር ማለት ነው።
ቆሻሻ ጭስ የወጣውም የማጽዳት ሥራው የዚያን ዕለት ብቻ ስለተሰራ ነው። ሁሌም የሚጸዳ ቢሆን ኖሮ እንዲያ የሚያጥለቀልቅ ጭስ ባልኖረ ነበር። ሰዎች ቆሻሻውን ሲያቃጥሉ የዚያን ቀን ብቻ ማድረግ የሚቻል ነው የመሰላቸው። ይሄ ማለት ዋና ዓላማው ቆሻሻን ማስወገድ ሳይሆን ባህል ስለሆነ ብቻ የወጉን ለማድረስ ነበር ማለት ነው።
በነገራችን ላይ አዲስ አበባ ንጹህ የምትሆነው በማጽዳት ሳይሆን ባለማቆሸሽ ነው። የከተማዋ ነዋሪ በነቂስ ወጥቶ ሁሉንም ቆሻሻ ጠራርጎና አጽድቶ ቢገባ የአስተሳሰብ ለውጥ ከሌለ በአንድ ቀን ሊበለሻሽ ይቻላል።
የወንዝ ዳርቻዎች እኮ ጥሩ ምሳሌ ይሆኑናል። በክረምት ጎርፍ ጠራርጎ ሲወስደው ወንዙ ንጹህ ይሆናል፤ ወዲያውኑ ግን ረፋድ እንኳን ሳይሆን አፍንጫ ተይዞ የሚታለፍበት ይሆናል። በግንብ እና በአጥር ዙሪያ ያለው አፍንጫ የሚበረቅስ መጥፎ ሽታ አብሮ የተገነባ አልነበረም፤ በሰዎች ሽንት እና የቆሻሻ መጣያነት ነው እንዲያ የሚሆነው።
መቼም እንግዲህ ገና ለገና ይቆሽሻል ተብሎ ዝም መባል የለበትም። የሚያቆሽሸውን ያህል በዚያው መጠን ደግሞ ቶሎ ቶሎ የሚያጸዳ ቢኖር ችግሩ ይቀንሳል። ልብ ብላችሁ ከሆነ ብዙ ጊዜ ሽንት የሚሸናው ከዚህ በፊት የተሸናበት ቦታ ላይ ነው፤ ቆሻሻ የሚጣለው ቆሽሾ የሚታይ ቦታ ላይ ነው። የያዝነውን ሶፍት እንኳን ንጹህ ቦታ ላይ ለመጣል ይከብደናል። ቆሻሻ ቦታ ከጠፋ ብዙ ሰው ሊጥለው ያሰበውን ነገር በኪሱ ይከተዋል፤ ቆሻሻ ያለበት ቦታ ለመጣል ማለት ነው። እንግዲህ ከዚህ የምንረዳው ሁሉም አካባቢ ንጹህ ቢሆን ሁሉም ለንጽህና እንደሚበረታታ ነው።
የስብሰባ አዳራሽ ውስጥ ልብ ብላችሁ ታውቃላችሁ? ምንም እንኳን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የቀረ ቢሆንም የፕላስቲክ ውሃ የታሸገበትን ወረቀት ለመጣል ዘወር ዘወር ብለው ያያሉ። የተጣለ ካለ ሁሉም ይጥላል። የተጣለ ከሌለ ግን ፕላስቲኩ ወገብ ላይ ካለው ሽፋን ውስጥ ሸጎጥ ያደርጉታል፤ ወይም ኪሳቸው ይከቱታል (እኔ ብዙ ቀን ኪሴ ከትቻለሁ)። መሬት ላይ በመጣል የሚጀምረው አንድ ሰው ነው ማለት ነው፤ ከዚያ በኋላ መቼም አንዴ ተጥሎበታል በሚል ሁሉም እየጣለ ወለሉ የፕላስቲክ ፋብሪካ ይመስላል። ለምሳሌ አነሳሁት እንጂ የውሃ ፋብሪካዎች አሁን የመክደኛውን መሸፈኛ አስቀርተውታል።
እነሆ ይህ በዘመቻ ብቻ የሚደረግ የጽዳት ባህላችን ለውጥ ሳያመጣ ቀርቶ በእንዲህ አይነቱ ነፋስና ፀሐይ በሚበዛበት የግንቦት ወር ጉንፋን በጉንፋን ሆነናል። በእንዲህ አይነቱ ወቅት ይብስበታል ለማለት እንጂ የመጥፎ ሽታዎች ነገር ከዓመት ዓመት ነው። በመንደሮች መካከል ባሉ የውስጥ ለውስጥ ቦዮች ሁሉ መጥፎ ሽታ አለ።
የሚያሳዝነው ግን የተማረና የሰለጠነ የሚባል ሰው ባለበት ሁሉ እንዲህ አይነቱ አስነዋሪ ነገር የሚታይ መሆኑ ነው። ይሄ በትልልቅ የፌዴራል ተቋማት ውስጥ ሳይቀር የታዘብኩት ነው። በእንደዚያ አይነት ተቋም ውስጥ ቢያንስ መጻፍና ማንበብ የማይችል የለም፤ በብዛት ደግሞ ቢያንስ የመጀመሪያ ዲግሪ ያለው ነው። ምንም እንኳን ጥፋቱን የሚፈጽመው ጥቂት ሰው ሊሆን ቢችልም መጸዳጃ ቤት ውስጥ የሚታየው ነገር ከላይ እስከ ታች ምን ያህል ኋላቀር እንደሆንን ያሳያል።
ጽዳት በዘመቻ ብቻ አይሁን! ዓመታዊ በዓላትን ወይም የመንግሥት ባለሥልጣን የሚያስጀምረውን ዘመቻ ብቻ ተከትሎ ከማድረግ ወጥተን የዕለት ከዕለት ሥራ ይሁን፤ አዲስ አበባን ንጹህ ማድረግ የሚቻለው በማጽዳት ብቻ ሳይሆን ቆሻሻን ያለቦታው ባለመጣል ነው!
ዋለልኝ አየለ
አዲስ ዘመን ግንቦት 10/2014