ባለፈው ሳምንት በዚሁ አምድና ገጽ ላይ “ወሰኑ እስከ መጻሕፍት ልገሳ የዘለቀው ኢትዮጵያዊ እሴት” በሚል ርእስ ከዛሬው ርእሳችን ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለው ጽሑፍ ለንባብ አብቅተን ነበር። ፕሬስ ድርጅትም “በአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ የሆነውና ጫማ በመጥረግ የሚተዳደረው ወጣት ታሪኩ ወዬሳ 975 መጻሕፍት ለአብርኆት ቤተ መጻሕፍት እንዲደርስለት ለኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት አበርክቷል።” “የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ለአብርኆት ቤተ-መጽሐፍት ያሰባሰበውን ከአምስት ሺህ በላይ መጻሕፍት አስረከበ።” (“በአምስት ቀን አምስት ሺህ መጽሀፍ” በሚል ሃሳብ ባካሄደው የመጽሃፍ ማሰባሰብ መርሃ-ግብር ከእቅዱ በላይ መጻሕፍት ማሰባሰብ መቻሉን የድርጅቱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ጌትነት ታደሰ በርክክቡ ወቅት መናገራቸውም ይታወሳል።) የሚሉ ዜናዎችን ማስነበቡም ይታወሳል። ዛሬም በዛ ጽሑፍ ያነሳናቸውን ፍሬ ሀሳቦች በተግባር ያረጋገጡ ለጋስን እንግዳችን አድርገናል።
እንግዳችን አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ ይባላሉ። ነዋሪነታቸው እዚሁ አዲስ አበባ፣ ፈረንሳይ አካባቢ ሲሆን፤ የባህር ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ድርጅት ባልደረባ ናቸው።
አቶ አስፋወሰን የመጀመሪያና ሁለተኛ ዲግሪያቸውን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያገኙ ሲሆን፤ ከመጻሕፍት ጋርም የጠበቀ ግንኙነት አላቸው። በተለይም ከአንባቢና ተመራማሪ ቤተሰብ መውጣታቸው ለዛሬው ሰብእናቸው ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳደረገም ነው በቀጥታም ባይሆን በገደምዳሜው የነገሩን። (አባታቸው አቶ ሺመላሽ በቀለ ሲበዛ አንባቢ፣ የሶስት መጻሕፍት ደራሲ፣ በንጉሱ ዘመን በተለያዩ የመንግስት ተቋማት በኃላፊነት የሰሩ ከመሆናቸውም በላይ ለ11 አመታት በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ዜን ሴክሬታሪ በመሆን ያገለገሉ ሰው መሆናቸውን አቶ አስፋወሰን አጫውተውናል።)
ለዚህ አምድ የዛሬ እንግዳችን ልናደርጋቸው በማሰብ ስንጠይቃቸው ላሳዩት ትህትናና ፈጣን ትብብር እያመሰገንናቸው ወደ አደረግነው ቃለ ምልልስ እንሂድ።
አዲስ ዘመን፡— የተለያዩ መጻሕፍትን ለግሰዋል የሚባል ጭምጭምታ ሰምተናል፤ እውነት ነው?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አዎ፤ እውነት ነው።
አዲስ ዘመን፡— ተቋሙን ሊነግሩን ይችላሉ?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አዎ፣ ለአዲስ አበባ ዪኒቨርሲቲ ነው የሰጠሁት።
አዲስ ዘመን፡— ምን ያህል መጻሕፍትን ለገሱ?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— 120 መጻሕፍት ነው የሰጠሁት።
አዲስ ዘመን፡— ለማወቅ ባደረግነው ጥረት የሰጧቸው መጻሕፍት ለየት ያሉ ናቸው የሚል ነገር ሰምተናል። መጻሕፍቱን ምንድን ነው ለየት የሚያደርጋቸው?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— መጻሕፍቱ በሙሉ ማለት በሚቻል ደረጃ የሕግ፣ ሕገ መንግስትና የፍልስፍና መጻሕፍት ናቸው። በይዘት ደረጃ ላቅ ያሉ ናቸው። አንዳንዶቹን ዩኒቨርሲቲው የሌለው ናቸው። ገበያም ላይ በቀላሉ የሚገኙ አይደሉም። በተለይ አገር ውስጥ የሚታሰብ አይደለም። ተከታታይ ቅፆችም መሆናቸው ሌላኛው ልዩነታቸው ነው። በዋናነት እነዚህ ናቸው ልዩ የሚያደርጓቸው።
አዲስ ዘመን፡— ለመሆኑ ለዚህ አይነቱ የተባረከ ሀሳብ ያነሳሳዎት ምክንያት ምንድን ነው፤ በተለይ በዚህ መጻሕፍት ውድ በሆኑበትና ብዙ ገንዘብ ሊያስገኙ በሚችሉበት ሰአት በዚህ ደረጃ ያሉ መጻሕፍትን እንዲለግሱ የገፋፋዎትን ምክንያት ቢነግሩን?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— ይህን እንዳደርግ የገፋፋኝ ወይም ያሳሰበኝ ጉዳዩ የትውልድ ጉዳይ፣ የአገር ጉዳይ በመሆኑ ነው። አንባቢ ትውልድ መፈጠር አለበት። በእውቀት የታነፀ ትውልድ መፈጠር አለበት። ለዚህ ደግሞ እውቀት ያስፈልጋል። ተገቢውን እውቀት ለመቅሰም ደግሞ መጻሕፍት ያስፈልጋሉ። በመሆኑም መጻሕፍቱን በተደራጀ መልክ አዘጋጅቶ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን አመንኩበት። አደረኩትም። ባጭሩ ይኸው ነው።
አዲስ ዘመን፡— ከንባብ ባህል አኳያ አሁን ያለውን ሁኔታ እንዴት ያዩታል፣ አንባቢ ጠፍቷል የሚሉ አሉ፤ እርስዎ በዚህ ይስማማሉ?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አይ፣ እኔ ሙሉ ለሙሉ “የለም” ወይም “ጠፍቷል” የሚል ማጠቃለያ የለኝም። ከቀድሞው ትውልድ አኳያ ሲታይ እውነት ነው ደክሟል፤ ደከም ያለ ነገር አለው። እንዲሁ “አንባቢ የለም” የሚለው ግን አያስኬድም፤ የሚያነቡ አሉ። የቀድሞውን ትውልድ በተመለከተ እሱ ከባድ ነው፤ ያ ትውልድ ከባድ ነው። ለዛውም ምንም አይነት የቴክኖሎጂ እገዛ በሌለበትና ነገሮች እንዳሆኑ ባልቀለሉበት በዛ ዘመን ከመጻሕፍት (ሀርድ ኮፒ) ጋር ታግሎ ነው በዛ ደረጃ አንባቢ የነበረው። የቀድሞው ከባድ ነው።
አዲስ ዘመን፡— መጻሕፍቱን በመለገስዎ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በኩል ያገኙት ምላሽ ምን እንደሚመስል ቢያጫውቱን?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በጣም ነው የተደሰተው። ኃላፊዎቹ እጅግ ተደስተዋል። በተለይም የመጻሕፍቱን ይዘቶች ሲመለከቱ ከመገረምም አልፈው በጣም ደስተኞች ነበሩ። ተደስተዋል።
አዲስ ዘመን፡— መደሰት ብቻ ነው፤ ወይስ ሌላ …
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— ብዙ ነገር ነው ያደረጉልኝ። የምስክር ወረቀትና ደብዳቤ ሰጥተውኛል። የዩኒቨርሲቲው ቤተ መጻሕፍት አባል አድርገውኛል። በምፈልግበት ግዜ ሁሉ ገብቼ እንድጠቀም የሚያስችል እድልን ሁሉ ሰጥተውኛል።
አዲስ ዘመን፡— በዚህ ደስተኛ ነዎት?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አዎ፣ እኔ ለመስጠት ስወስን እነዚህን ነገሮች አስቤ አይደለም። መስጠት እንዳለብኝ ወሰንኩ፤ ሰጠሁ። ይሄው ነው። በእርግጥ እንደዚህ አይነት ምስጋናና ልዩ እድልን በማግኘቴ ደስተኛ ነኝ። ዩኒቨርሲቲውን አመሰግናለሁ።
አዲስ ዘመን፡— አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን ከሌሎቹ ተቋማት በተለየ እንዴት መረጡት?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— ምክንያቴ ዩኒቨርሲቲ ማለት የሁሉም ስለሆነና መጪው ትውልድ በዚሁ ተቋም ውስጥ ስለሚያልፍ እንዲጠቀምባቸው በማሰብ ነው። ዩኒቨርሲቲ ዘር፣ ብሄር፣ ቀለም … ሳይለይ የሚያስተናግድ በመሆኑ፤ ሁሉንም ተጠቃሚ ስለሚያደርግ …. በዛ ምክንያት ነው ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ልሰጥ የቻልኩት። አሁንም እያደራጀሁ ያለኋቸው መጻሕፍት ስላሉ እንደዚሁ ለሌሎች ተቋማትም እሰጣለሁ። ይህ ብቻም አይደለም። ተቋሙ በከፍተኛ ደረጃ የጥናትና ምርምር ስራዎች የሚሰሩበት ነው። ያበረከትኳቸው መጻሕፍት ደግሞ በይበልጥ ለጥናትና ምርምር ሰዎች በከፍተኛ ደረጃ ሊያግዙ የሚችሉ ናቸው። በተለይ በሕግ፣ ሕገ መንግስት፣ ፍልስፍና …. ባጭሩ ለማህበረሰብ ሳይንስ ዘርፍ በከፍተኛ ደረጃ የሚያግዙ ስለሆነም ነው ዩኒቨርሲቲውን የመረጥኩት።
አዲስ ዘመን፡— ለፕሬስ ድርጅትስ ምን አስበዋል?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— (ሳቅ) አስቤያለሁ። ይመጣል።
አዲስ ዘመን፡— በዚህ ደረጃ የመጻሕፍት ክምችትዎን በተመለከተ የሚሉን ካለ፤ ማለት እንዴት ነው፤ በተለያዩ ጊዜያት የገዟቸው?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አዎ፣ የገዛኋቸው ናቸው። የእኔንም ከአባታችን የወረስኳቸውንም አንድ ላይ አድርጌ ነው ስጦታውን ያበረከትኩት።
አዲስ ዘመን፡— አሁን እንደዚህ አይነት እንቅስቃሴ፣ መጻሕፍትን የማሰባሰብና የመለገስ እንቅስቃሴዎች እየታዩ ነው፤ በእንቅስቃሴው ላይ ምን አስተያየት አለዎት?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— አዎ፣ እንደዛ አይነት እንቅስቃሴ እየታየ ነው። በጣም ጥሩ ነው። የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እያደረገ ያለው መጻሕፍትን አሰባስቦ ለአብርኆት ቤተ-መጻሕፍት የማስረከብ ተግባር ሊያስመሰግነውና ሌሎችም ሊከተሉት የሚገባ አርአያነት ያለው ተግባር ነው። ይህ በሁሉም የአገራችን አካባቢዎች ተግባራዊ ሊደረግ ይገባል ብዬ አስባለሁ። መጻሕፍት ወደ እሚያነቧቸው ጋ መድረስ አለባቸው። አንባቢም የሚያነባቸውን መጻሕፍት በአቅራቢያው ሊያገኝ ይገባል።
አዲስ ዘመን፡— ከዚህ፣ መጻሕፍትን ከመለገስ አኳያ ለአጠቃላይ ህብረተሰቡ የሚያስተላልፉት መልእክት ካለ?
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— በየግለሰብ ቤት መጻሕፍት በብዛት አሉ። ግሩም የሆነ ኮሌክሽን ያላቸው ሰዎች ሞልተዋል። በመሆኑም ታማኝና የሚረከብ አካል ካለ የሚለግስ ሰው የለም ማለት አይቻልም። ብዙ ይኖራል። ሌሎችም፣ በተለይም ሰፊ የሆነ የመጻሕፍት ክምችት ያላቸው ሰዎች ለተቋማት የመለገሱን ጉዳይ ችላ ሊሉት አይገባም። መጻሕፍትን ለተቋማት መለገስ እውቀትን ለትውልድ እንደማስረከብ ይቆጠራል። ሁሉም ሰው፣ አቅሙ የሚፈቅድ ሁሉ፣ ለመጻሕፍት ልገሳ ጥሪ ፈጣን ምላሽ ሊሰጥ ይገባል። በመሆኑም መጻሕፍት ያላቸው ሰዎች ለተቋማት ቢለግሱ አገርና ህዝብን ጠቀሙ ማለት ነው፤ አንባቢ ትውልድ ከመፍጠር አኳያ የዜግነት ኃላፊነታቸውን ተወጡ ማለት ነው። ትውልድ ስለ ሕግ፣ ሕገመንግስት፣ ፍልስፍና ወዘተ አወቀ ማለት ደግሞ ትርጉሙ ብዙ ሲሆን ጥቅሙም በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ተቋማት የማስተባበሩንና ልገሳውን የመረከቡ ጉዳይ፣ ልክ እንደ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ሁሉ፣ ሃላፊነትና ተነሳሽነትን በመውሰድ መስራት ይጠበቅባቸዋል። አሁን እንደሚቻል ታይቷል፤ ሰውም እንደ’ሚለግስ እየታየ ነው። በመሆኑም መጻሕፍትን በማሰባሰብ፣ በመለገስና ተደራሽ በማድረግ ህብረተሰብን ተጠቃሚ ማድረግ ይገባል።
አዲስ ዘመን፡— ስለ ሰጡን ማብራሪያ እናመሰግናለን።
አቶ አስፋወሰን ሺመላሽ፡— እኔም አመሰግናለሁ።
አዲስ ዘመን ግንቦት 1 ቀን 2014 ዓ.ም