ጭልፊት ክረምት ላይ እልም ብላ ትጠፋለች ይባላል። በተለመደው አካባቢ ስታንዣብብ አትታይም። የአገራችን ማኅበረሰብ ለእዚህ የሚሰጠው አስተያየት የጭልፊትን ብልሃተኛነት ያመለክታል። ክረምት ሳይመጣ በፊት ቀለቧን አጠራቅማ አርፋ ስለምትቀመጥ ነው ይላል።
የአዕዋፍ ባለሙያዎች ደግሞ ይህ አይደለም፤ ክረምት ወደ አልሆነበት አካባቢ ሄዳ ክረምቱን ስለምታሳልፍ ነው ይላሉ። ይሄ ሊያስኬድ ይችላል። ለእዚህ ጽሑፍ ግን የመጀመሪያውን የማኅበረሰቡን አስተያየት ያዙልኝ። ለዛሬ።
ጠንካራው ኢትዮጵያዊ ማኅበረሰብም በእዚህ ወቅት እንደ ጭልፊቷ ነው። ክረምትን የጨለማ ወቅት አርጎ ይመለከተዋል፤ ብዙም አያላውስምና፤ ለሸመታም ለወፍጮም ብዙ አይመችም። ብልህ አባወራ ወይም ቤተሰብም ዋና ዋና ቀለቦቹን አስቀድሞ ይሸምታል። ይህን የሚይዝበት ወቅት ደግሞ ከጥር ወር አንስቶ ባሉት ጥቂት ወራት ውስጥ ነው።
በእዚህ ወቅት ቢችል የዓመቱን፣ ባይችል ለክረምቱ የሚሆነውን ቀለቡን ይሸምታል። ምክንያቱም አርሶ አደሩ ምርቱን ለገበያ በብዛት የሚያወጣበት ወቅት ይህ ነውና። በዋጋም፣ በጥራትም ከእዚህ ጊዜ የተሻለ ወቅት የለም። በእዚህ ወቅት እህል ባይረክስ ይረጋጋል። እናም አባወራውን ጭልፊቷን በሉት። በየመንደሩ አይታችሁ ከሆነ በርበሬ በብዛት ተሰጥቶ የሚታየው በኅዳር ፣ታኅሣሥና ጥር ወር ነው።
የዚህም ምክንያቱ ያው ነው። በእዚህ ወቅት በርበሬ በብዛት ገበያ ይወጣል፤ ብልህ እናቶች የዓመቱን የበርበሬ የሚያዘጋጁት በእነዚህ ጊዜያት ነው። እናቶችም እንደ ጭልፊቷ ናቸው።
ዘንድሮ የእነዚህ ብልሆች ሩጫዎች ብዙም አልታዩኝም። በተለይ የበርበሬው ዋጋ ሰማይ ነበር። ኅብረተሰቡ የሚብስ እንጂ የሚሻል ጊዜ አይመጣም ብሎ አቅሙ የፈቀደውን ያህል ግን ማዘጋጀቱ አልቀረም። በእህልም እንደዚያው ነው። ዋጋ መጨመሩ ይወራል። ለነገሩ ዓለም አቀፉም፣ አገራዊውም፣ የኛ አገር ነጋዴዎች ባህሪም ሲታይ የእህል ዋጋ ጉዳይ አነጋጋሪ ሆኖ ቀጥሏል።
አባወራዎችም እናቶችም ዘንድሮ ጭልፊቷን መሆናቸውን እንጃ። የእህል ዋጋ ተንገብግቧል። ዋና ዋና እህል አምራች አካባቢዎች ላይ በእርሻ ወቅት የተፈጠረ ችግር የለም። የግብርና ሚኒስቴር መረጃዎችም ቢሆኑ ምርት እንደሚጨምር እንጂ እንደሚቀነስ አላመለከቱም።
የእህል ዋጋ መረጋጋቱን ሳንሰማ፣ መንገብገቡን የሚያረዱን ሁኔታዎች እየተስተዋሉ ናቸው። በእዚህ የእህል ዋጋ መጨመር አርሶ አደሩ ተጠቅሞ ከሆነ ችግር የለውም። አርሶ አደሩ ከተጠቀመ ከርሞ የበለጠ ያመርታል። አርሶ አደር በዋጋ ከተጎዳ ለከርሞ ምርት የሚቀንስ ስለመሆኑ በልምድ ይታወቃል።
በእህል ዋጋ መጨመር ሁሌም የሚጠቀመው ሕገወጥ ነጋዴና ደላላዎች ናቸው። ነጋዴዎቻችን ሠርተው የሚያተርፉ አይመስላቸውም፤ ይሰርቃሉ። ትርፍ ብለው የሚያስቡት አጭበርብረው ወይም አግባብ የሌለው የዋጋ ጭማሪ አድርገው የሚዘርፉትን ነው። ቅቤ ነጋዴ ሁሌም ስለ ድርቅ ያወራል የሚባለውም ለእዚህ ነው። ስለድርቅ ካላወራ ትርፍ የሚያገኝ አይመስለውምና።
በቅቤ ነጋዴ ላይ ተተረተ እንጂ ነጋዴውም ያው ነው። በሠራተኛ የተማረሩት አንድ የሰፈራችን እናት የሰራተኛ እናት አንድ ናት ያሉት ታሰበኝ። እንደ ልጃቸው ሲመለከቷት የነበረች ሠራተኛቸው በሌሉበት ጥላቸው ብትሄድ ነው ይህን ማለታቸው።
አብዛኞቹ ሠራተኞች ለመሄድ ሲፈልጉ በቃኝ፤ ደህና ሁኑ፤ ለእስከ አሁኑ አመሰግናለሁ፣ወዘተ አይሉም፤ አባብለው ያስቀሩናል ብለው አስበው ሊሆን ይችላል። ቀጣሪዎቻቸው ግን ይህን አይመለከቱትም፤ ሁሉም ሠራተኛ በባህሪ አንድ ነው ብለው ይመለከታሉ። ሠራተኞች ሲሞላላቸው ጥለው መሄዳቸው ያለ መሆኑን ለማመልከት የሠራተኛ እናት አንድ ናት ማለታቸው።
ይቅርታ ብዙ ዘበዘብኩ መሰለኝ። ሕገወጥና ሕገወጥ ያልሆነውን ነጋዴ ለይ ትሉኝ ይሆናል። ነጋዴዎች ብዙ ሆድ የሚያስብስ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ መታወቃቸው፣ ምርትመደበቅ እና የመሳሰለውን እያረጉ በመሆናቸው ከነጋዴ ነጋዴ መለየት አልፈልግም። እናንት ካላችሁ ግን እሺ ሕገወጥ ነጋዴ እላለሁ። እነዚህ ሕገወጥ ነጋዴዎች ጥቂት እንዳይመስሏችሁ፤ ሕጋዊውን መጋረድ ላይ ደርሰዋል። ሕጋዊውን ነጋዴ እንደ ዳዋ በልተውታል።
ተራብተዋል ነው የምላችሁ። ለእነሱ አሁንም አሁንም ዋጋ መጨመር፣ ምርት እያለ መደበቅ፣ ኪሎ ማጉደል/ መቀሸብ/፣ ደህናውን ከመጥፎ በመቀየጥ በደህናው ዋጋ መሸጥ፣ ወዘተ ምንም ነውር የለውም። በእዚህ ላይ ደላላዎች አሉ፤ ሌሎቹ የሕገወጥ ንግዱ ንጉሦች። በዓለ ሲመት ማድረግማ ማክበር ብቻ የቀራቸው እነዚህ ንጉሦች እየተወገዙም ይበዛሉ።
የእቃውን ዋጋ አየር ላይ ነው የሚወስኑት። ብዙ ጊዜ እንደ ምጣኔ ሀብት ባለሙያም ያደርጋቸዋል። ዘንድሮማ ሰርግና ምላሻቸው ነው። ከአስመጪዎች ጋር ሆነው ዋጋውን እንደ ኳስ ይጫወቱበታል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ የሸቀጦች፣ የነዳጅ፣ እና የሎጂስቲክስ ዋጋ መጨመር.፣ በአገር ደረጃ የተካሄደው ጦርነት፣ አሁንም ድረስ በተለያዩ አካባቢዎች ያለው ግጭት፣ ድርቅ ለእነሱ ትልቅ ግብአቶች ናቸው። እንኳን እነዚህ ችግሮች አፍጠው መጥተው ልክ ሁሌም ስለድርቅ እንደሚያወራው ቅቤ ነጋዴ ዋጋ ለመጨመር የማይሠሩት ምክንያት የለም።
እስከ አሁን በመጣንበት መንገድ መንግሥት አነዚህን የቀን ጅቦች የሚያስታግስ አይመስለኝም። በሲሚንቶው፣ በዘይቱ ወዘተ ሞከረ፤ አልተሳካለትም፤ ለውጥ ቢኖርማ ትንሽ እፎይ ያልንበት ጊዜ በነበረ። እፎይ ብለን እኮ አናውቅም።
እፎይ ናፈቀን። አሁንም እነሱ አንድ ችግር ሆነው እንደሚቀጥሉ እናስባለን። መንግስት በኑሮ ውድነት የተፈተኑ አገሮችን ተሞክሮ በመውሰድ፣ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች መላ እንዲያፈላልጉ በማድረግ የዘንድሮውን የዋጋ ንረት በፍጥነት ማስታገስ ውስጥ መግባት አለበት። በእዚህ የእህል ምርት በስፋት ለገበያ በሚቀርብበት ወቅት የእህል ዋጋ መረጋጋት ወይም መቀነስ ሲገባው ከተወደደ የአሁኑ ወቅት ብቻ አይደለም ቀጣዩ ጊዜም ፈታኝ ይሆናል።
ለአዲስ አበባና በዙሪያዋ ለሚገኙ ነዋሪዎች ዳቦ ያንበሸብሻል የተባለው ሸገር በስንዴ አቅርቦት አለመኖር ሳቢያ ከሥራ ውጪ ሲሆን በየቤቱ ሊኖር የሚችለውን ችግር ገምቶ መፍትሔ ማስቀመጥ ከብልህ መንግሥት ይጠበቃል። ብዙዎች የሸገር ዳቦን በእጅጉ ይፈልጉት ነበር።
የጎዳና ተዳዳሪዎች፣ ተማሪዎችን በሆነ መልኩ የመከተም ነበረ። መንግሥት ጊዜ ሳይሰጥ የሸገርን ችግር መፍታት ይኖርበታል፤ ሥራውን ሲጀምር የሆነ ውል ያላቸውም መሰለኝ ። እንደ ጠቀስኩት የእህል ዋጋ እየናረ ነው። እኔ ከአሁኑ ይልቅ ቀጣዮቹ የክረምት ወራትና ከወዲህ ያሉት ጊዜያት በእጅጉ ያሳስቡኛል። በተለይ ድንቹ፣ ጎመኑ፣ የበቆሎ እሽቱና የመሳሰሉት እስከሚደርሱ ያሳስባል።
መንግሥት በብዙ አጣብቂኝ ውስጥ እንዳለ የማይገነዘብ ኢትዮጵያዊ የለም። ዞሮ ዞሮ ወደ መንግሥት ነው አቤት የሚባለውና አሁን እየታየ ያለውን የኑሮ ውድነት እንዲሁም በቀጣይ ሊመጣ የሚችለውን የባሰ ሁኔታ ታሳቢ ያደረገ አዲስ አሠራር ቀይሶ መሬት ላይ ማውረድ ከመንግሥት ይጠበቃል።
አገራዊና ዓለም አቀፋዊ እንዲሁም የሕገወጥ ንግዱ ቀበኞች ያስከተሏቸው ችግሮች እያባባሱት የሚገኘውን የኑሮ ውድነት ለመፍታት እንደ እኔ ከማጣፈጫው ዘይትና ስኳር በፊት እንደ ስንዴ፣ ሩዝና በቆሎ ያሉት አቅርቦቶች መቅደም ይኖርባቸዋል።
በተለይ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኘው ማኅበረሰብ እነዚህ አቅርቦቶች በሸማቾች ማኅበራት በኩል በነጻ ወይም በዝቅተኛ ዋጋ መቅረብ ይኖርባቸዋል። የኑሮ ውድነቱ መካከለኛ ኑሮ ውስጥ ያሉትንም በእጅጉ እየተፈታተነ መሆኑ ይታሰብበት፤ እነዚህ ደግሞ እንደ ጸጉራም ውሻው ናቸው።
ጸጉራም ውሻ አለ ሲሉት ይሞታል አደል የሚባለው። መንግሥት እነዚህን አቅርቦቶች ለማሟላት ከአገሮችም ከአበዳሪ ተቋማትም መበደር ካለበትና መበደር የሚችልበት ሁኔታ ካለ መበደር ያለበት ጊዜ አሁን ነው። ስንዴው ከቀረበ እናቶች እንደሚሆን አንደሚሆን ያደርጉታል።
ጢቢኛ፣ እንጀራ፣ ወዘተ ያደርጉታል። ልጆቻቸው ጢቢኛ ካገኙ ምንም አይፈልጉም። ልጅ እጁን ነው የሚርበው እንደሚባለውም የልጆቻቸውን መሠረታዊ ፍላጎት በተወሰነ መልኩም ቢሆን ይመልሱበታል። እናም ከማጣፈጫው ስንዴው ይቅደም!!
ኃይሉ ሣሕለድንግል
አዲስ ዘመን የካቲት 26 /2014