ተወልደው ያደጉት ሳውዲ አረቢያ ጅዳ ከተማ ውስጥ ነው።የመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን እዛው ጅዳ ከተማ ውስጥ በሚገኙ ዓለም አቀፍ ትምህርት ቤቶች ተከታትለዋል።በካይሮ በሚገኘው የካናዳ ዩኒቨርሲቲ በኒሮሊንጉስቲክ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን አግኝተዋል።
በተጨማሪም በብረት ብየዳ ትምህርት ስልጠና የወሰዱ ሲሆን፤ ግብፅ አስዋን ግድብና ሌሎች መንግስታዊ ተቋማት ላይ በዚሁ ሙያ የመሰራት እድል አጋጥሟቸው ነበር።በተለያዩ ጊዜያት ወደ ኢትዮጵያ እየተመላለሱ ለጥቂት ጊዜያት አስተምረዋል።
ይሁንና ግብፅ በነበራቸው ቆይታ ኢትዮጵያ ላይ የሚደረገው ደባና ጫና ቁጭት ይፈጥርባቸው ስለነበር ብዙም የማያውቁትን የአገራቸውን ክብር ለማስመለስ ሲሉ የተለያዩ ጽሑፎችን መፃፍ ያዙ፡፡
እንደአጋጣሚ ደግሞ በወቅቱ በግብፅ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሙሃሙድ ድሪል ጋር የመገናኘት እድሉ ገጠማቸውና ዕለት ዕለት ስለኢትዮጵያ ማንበብና መፃፍ ጀመሩ።ከአምባሳደሩ በሚሰጡ ምክረ-ሃሳቦች ላይ ተመስርተው በርካታ ጽሑፎችን በመፃፍ የአገራቸውን እውነት ለማሳወቅ ሲሠሩ ቆይተዋል።ከተለያዩ የአረብ መገናኛ ብዙሃን ጋር በመቅረብ በታላቁ ህዳሴ ግድብና በኢትዮጵያ ጉዳዮች ላይ በመሞገት የበኩላቸውን ድርሻ መወጣታቸውን ቀጠሉ።
ምንም እንኳን ኢትዮጵያ ባይወለዱም፤ ለኢትዮጵያ ቋንቋና ባህል እንግዳ ቢሆኑም ደማቸው ስለተቀዳባት እናት አገራቸውን አውቀው እንዲያድጉ የቤተሰቦቻቸው ሚና ከፍተኛ እንደነበር የሚናገሩት እኚሁ የማህበረሰብ አንቂ፤ በተለይም እ.ኤ.አ 2011 ዓ.ም ጀምሮ በዓለም ሚዲያዎች ላይ በመሟገት ከፍተኛ እውቅና እየተቸራቸው ከሚገኙ ሰዎች ኢትዮጵያኖች መካከል ለመሆን ችለዋል።
በአሁኑ ወቅት ደግሞ ከኡስታዝ ጀማል ጋር በመሆን ኪንግስ ኦፍ ዓባይ የተሰኘውን በዓባይ ወንዝ ላይ ትኩረት አድርጎ በሚሰራው ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴ ውስጥ በርካታ ሥራዎችን በመስራት ላይ ይገኛሉ።
አዲስ ዘመን ጋዜጣም የህዳሴ ግድብ ተሟጋችና የኪንግስ ኦፍ ዓባይ ምክትል ኃላፊ የሆኑት አቶ ዛሂድ ዚዳን አልሃበሻን የዛሬው የዘመን እንግዳ አድርጎ እንደሚከተለው አቅርቦላችኋል።
አዲስ ዘመን፡- የሳውዲ ቆይታ ምን እንደሚመስል አንሱልኝና ውይይታችንን እንጀምር?
አቶ ዛሂድ፡- እኔ ሳውዲ ተወልጄ ባድግም እንደማንኛውም ስደተኛ ዜጋ ለሳውዲ አረብያም ሆነ ለኢትዮጵያውያን የኖርኩት ባይተዋር ሆኜ ነው። ምክንያቱም የተወለዱኩበት አገር መንግስት ሁልጊዜም የሚቆጥረኝ እንደስደተኛ ነው።
የኢትዮጵያ ማኅበረሰብም ከሌላው እኩል አይቆጥረኝም ነበር። እርግጥ ነው፤ የሳውዲ ሕዝብ መልካም በመሆኑ የሚያየኝ እንደራሱ የነበረው። በተለይ እኛ በነበርንበት ጊዜ የሚመለከተን እንደቤተሰብ ነበር። ለመንግስታቸው ግን ሁልጊዜም የምንቆጠረው መጤ ተደርገን ነው።
በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ሕዝብ ቋንቋ ባለመቻሌና ባህሉን ባለማወቄ እንደሌላው ዜጋ አያየኝም ነበር። ስለዚህ የቆየሁት ከዚህም ከዚያም ሳልሆን መሃል ላይ ነበርኩ። አምባሳደር በድሪ ሸሪፍ ከመጡ ወዲህ ግን ሳውዲ የምንኖር የኢትዮጵያ ማኅበረሰብን እቅፍ ድጋፍ በማድረጋቸው ነገሮች እየተሻሻሉ መጥተው ነበር።
በሌላ በኩል ደግሞ የሐረሪ ተወላጅ የሆንን ኢትዮጵያውያን እርስ በእርስ እንቀራረብና እንደጋገፍ ስለነበር የመገለል ጫናው እንዳይበረታብን አድርጎብናል ብዬ አምናለሁ። በተለይም የእኔ አባት ለአገሩ በርካታ ሥራዎችን የሠራና የሚታወቅ በመሆኑ የሐረሪ ማኅበረሰብ ለቤተሰባችን የተለየ አክብሮት ነበረው።አባቴ ከሠራው ሥራ አንዱን እንኳን ባነሳልሽ ሐረር በር ላይ ያለው የአሚር አብዱላሂ ፎቶ የአባቴ ስጦታ ናት።
በኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም ጊዜ አባቴ በእጁ ሰርቶ ለሐረሪ ክልል የሰጠው ነው። አዲስ ዘመን፡- በታላቁ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች መሟገት የጀመሩበት አጋጣሚ ምን ነበር?
አቶ ዛሂድ፡- እኔ ተወልጄ ያደኩት ጅዳ ነው።እዚህ የመጣሁት እ.ኤ.አ 2007 ዓ.ም ነው።ለአንድ ዓመት ከኖርኩኝ በኋላ ወደ ካይሮ ሄጄ እስከ 2013 ዓ.ም መጨረሻ ቆይቻለሁ።እዛም ቢሆን አማርኛ ባለመቻሌ በርካቶች ኢትዮጵያዊ ስለመሆኔ ይጠራጠሩ ነበር።አንዳንዶቹም በግልፅ ፓስፖርትህን ሰርቀህ ይሆናል እንጂ ኢትዮጵያዊ አይደለህም ይሉኝ ነበር።
ይህ ችግር የደረሰብኝ በኢትዮጵያ ማኅበረሰብ ብቻ ሳይሆን በኢምባሲ ሰራተኞችም ሳይቀር ነበር። ከአምባሳደር ሙሃሙድ ድሪል ጋር የመገናኘት እድሉን ያገኘሁት በዚያ አጋጣሚ ነበር።
እኚህ ሰው ብዙዎች እንደሚመሰክሩላቸው መላውን የኢትዮጵያ ማኅበረሰብ በአንድ ላይ የሰበሰቡ ስለአገራቸው በተግባር ዘብ የቆሙ፤ ለአገራቸው ጥቅም ዋጋ የከፈሉ ግለሰብ ናቸው።በተለይም ካይሮ በስደት የገቡ በርካታ ኢትዮጵያኖችን ሕይወት በመታደግ ለአገር ትልቅ ውለታ ውለዋል።
እኔም አሁን ላለሁበት ማንነቴ መሰረት የጣሉልኝ እንደአርዓያ የማያቸው ሰው ናቸው።አገሬን እንድወድና ስለአገሬ ዘብ እንድቆም የነበረኝን አመላከከት በመልካም የቀየሩት እኚሁ አምባሳደር ናቸው፡፡
በዋናነት የታላቁ ህዳሴ ግድብ መሰረት ከተጣለበት እለት ጀምሮ ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ሃብቷ የመጠቀም መብቷን የዓለም ሕዝብ እንዲያከብርላት፤ ይህንን ግድብ የምትገነባው ሕዝቦቿን ከድህነት ለማላቀቅ እንጂ የማንንም አገር ሕዝብ ለመጎዳት እንዳልሆነ ግንዛቤ የማስጨበጥ ሥራ በስፋት እንሰራ ነበር።አምባሳደሩ በዚህ ምክንያት ብዙ ጫናዎች ይደረጉባቸው ነበር።ብዙ ዋጋም ከፍለዋል።
ግን ደግሞ በጣም የማዝነው ያንን ያህል ዋጋ ከፍለው ስለእሳቸው የተሟገተ አንድም ኢትዮጵያዊ አለመኖሩ ነው።አረብኛ ደግሞ የተወላጆችን ያህል ጠንቅቀው የሚያውቁ በመሆኑ ከማኅበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው ይኖሩ ነበር። አምባሳደር ሙሃሙድ ድሪል ምንም እንኳን ዲፕሎማት ቢሆኑም ከራሳቸው ክብር ይልቅ ለአገራቸው ክብር ቅድሚያ በመስጠት ቀን ከሌሊት የተጉ ሰው ናቸው።አምባሳደሩ ለአገራቸው ይህንን ያህል ዋጋ ከከፈሉ እኔስ ስለአገሬ ምን ማድረግ ይገባኛል? የሚል ጥያቄ ራሴን መጠየቅ ያዝኩኝ።አረብኛ አፍ መፍቻ ቋንቋዬ ነው።
የተማርኩት በአረብኛ ነው።ከሁሉም በላይ ግን የአረቦችን ሥነ-ልቦና የማውቀው በደንብ ነው።የተለያዩ ገልፍ አገሮችን የማየት እድሉ ስለነበረኝ ባህላቸውን ጠንቅቄ አውቃለሁ።በመሆኑም በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ በፌስቡክ መፃፍ ጀመርኩኝ።ከዚያ በፊት ግን አይ.ሲ.ኪውና ሃይ. ፋይፍ የተባሉ ሁለት የሚዲያ ፕሮግራሞች ላይ በጥቂቱ ሃሳብ ማካፈል ጀመርን። ከዲዛይነሩ ወንድሜ ጋር በመሆን የኢትዮጵያን የተፈጥሮ መስዕብ የሚያሳዩ ምስሎችን በቲሸርትና በተለያዩ ቁሳቁሶች ላይ በማተም አገራችንን እናስተዋውቅ ነበር።
በአረብኛ ‹‹ኢትዮጵያ የፈጣሪ ገነት ምድር ላይ›› ተብሎ የተፃፈበት ቲሸርት በመልበስ የበለጠ አረብ ሕዝብ ጋር ለመድረስ እንሞክር ነበር። ከሁሉ በላይ ምስጋና ይግባቸውና አምባሳደር ሙሃሙድ ድሪል በውሃ ሃብታችንና በውሃ ቴክኖሎጂ ዙሪያ በተለይም በዓባይ ምንጭና ታሪክ ዙሪያ ሰፊ ግንዛቤ አስጨብጠውኛል። አጫጭር ርዕሰ ጉዳዮችን እየሰጡን በዚያ ጉዳይ ላይ እንድንፅፍ ያግዙኝ ነበር። ‹‹ቀስ በቀስ እንቁላል በእግሩ ይሄዳል›› እንደሚባለው በሂደት በዓባይና በግድቡ ላይ በስፋት እስከመሟገት ደርሻለሁ። በነገራችን ላይ ግብፅ ሳለሁ ከሁስኒ ሙባረክ ጀምሮ ያየሁት ስድስት መንግስታትን ነው። ከኢትዮጵያ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት ሲመጡ እኔ እዚያው ነበርኩኝ።
እስከዚያ ድረስ በዚህ ጉዳይ ላይ በየሚዲያው እሟገት የነበረው ወጣ ገባ እያልኩኝ ነበር። ይሁንና እ.ኤ.አ 2015 ዓ.ም የሶስቱ አገራት መሪዎች ስምምነት ካደረጉ በኋላ በስፋት ትግሌን ቀጥያለሁ። ምክንያት የሆነኝም ሶስቱ መሪዎች በአንድ ላይ ተያይዘው የተነሱት ፎቶግራፍ ቦሌ መንገድ እና ቸርቸር ጎዳና ላይ ተለጥፎ ነበር።ያ ፎቶ ከላዩ ላይ በአረብኛ ‹‹ምንም ችግር ቢኖር ሶስቱ አገራት ወንድማማች ሕዝብ ነን፤ እንስማማለን›› የሚል ነው። አረብኛ ፅሁፎ ከቀኝ ወደ ግራ መፃፍ ሲገባው ልክ እንደአማርኛ ከግራ ወደ ቀኝ ተፅፎ ስመለከት ከፍተኛ ቁጭት አደረብኝ።
ያንን ፅሁፍ ፎቶ አንስቼ ትክክል አለመሆኑ የሚገልፅ ፅሁፍ ፅፌ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ላስገባ ስሄድ በፌደራል ፖሊሶቹ ጥሩ መስተንግዶ አላገኘሁም። መታወቂያ ሲጠይቀኝ መታወቂያ እንደሌለኝ ግን ደግሞ ፓስፖርት መያዜን ነገርኩት። በመሰረቱ የመታወቂያ
ትርጉምን ራሱ ያወኩት ያን ጊዜ ነበር። ይህንን ሲያይ ያ ፌደራል ፖሊስ አመናጭቆና አስፈራርቶ አባረረኝ።ያ ሁኔታ ለእኔ እጅግ ተስፋ አስቆራጭ ነበር።ከዚያ በኋላ ግን መጀመሪያ መታወቂያ መያዝ እንዳለብኝ አመንኩኝ። መታወቂያ ማግኘት እንዳሰብኩት ቀላል አልሆነልኝም።
ከሶስት ጊዜ በላይ ለፍቻለሁ። በተለይ ቋንቋ አለመቻሌ ኢትዮጵያዊ ስለመሆኔ ብዙዎች እንዲጠራጠሩኝ ያደረገ በመሆኑ ብዙ ዋጋ አስከፍሎኛል። እነዚህ ሁኔታዎች ተስፋ አስቆራጭ ነበሩ፤ ግን ደግሞ በባለቤቴ ድጋፍ እርሷ ፅናት ሆናኝ አለማዬን ወደፊት መግፋት ችያለሁ።የዓባይ ጉዳይ ደግሞ ከጊዜ ወደ ጊዜ አነጋጋሪ እየሆነ መጣ።በግድቡ ዙሪያ ላይ የአረቡ ማኅበረሰብ እውነታውን እንዲገነዘብ የሚያደርጉ ፅሁፎችን በመፃፍና በሚዲዎች ላይ ሃሳቤን በመግለፅ የበኩሌን ጥረት አድርግ ነበር።
በተለይ ግብፅ በነበርኩበት ጊዜ ኢትዮጵያ የዓባይ ምንጭ ስለመሆንዋ፤ እነሱ አስዋንን ለመገደብ ባሰቡበት ሰዓት እኛም አቅደን እንደነበር፤ ይህ ሃብት እያለ ሕዝቡ ምን ያህል በችግር እየኖረ ስለመሆኑ ለግብፅውያኑ በማስረዳበት ጊዜ አንተ የኢትዮጵያ መንግስት ሰላይ ነህ ይሉኝ ነበር። በተለይ ደግሞ ከቀለም ትምህርቱ ጎን ለጎን የብየዳ ትምህርት ተምሬ ስለነበር ፤ በዚያ ሙያዬ ምክንያት አስዋን ግድብ ውስጥ ያሉ የኢንተርኔትና የነዳጅ መሰረተ ልማቶችን የማየት እድሉ አጋጥሞኝ ነበር።
ይህም ሆነ ተብሎ ለስለላ እንደሄድኩኝ አድርገው እንዲያስቡ ያደረጋቸው ይመስለኛል። ከሁሉ በላይ የሚያሳዝነው ደግሞ ያንን ሁሉ ዋጋ በሰው አገር ከፍለን ኖረን እዚህ ስንመጣ ሃሳባችንን የሚቀበል የመንግስት አካል አለመኖሩ ነው።
አንዴ እንዳውም በሬዲዮ ቀጥታ ስርጭት ላይ በነበረ ውይይት አንድ ከፍተኛ የውጭ ጉዳይ ሰው ሲወያይ እኔም ስልክ ደውዬ በአረብ አገራት ሊደረጉ ስለሚገባው ነገሮች ስነግረው ሃሳቤን ከመቀበል ይልቅ አጣጥሎና ሸፋፍኖ ማለፍን መርጧል። በነገራችን ላይ ያን ጊዜ የሰጠናቸው ጥቆማዎች ቢቆይም አሁን ላይ ተተግብረዋል።
የመጀመሪያ የውሃ ሙሌት ከመከናወኑ በፊት በየአረቡ ሚዲያ ላይ ሃሳቤን ስገልፅ የነበረው በአስተማሪ ደመወዜ ከፍተኛ ወጪ እያወጣሁ ነበር። ሆኖም ሙሌቱ ሲከናወን ፈላጊዎቹ እነሱ ሆኑ።ሁሉም የአረብ ሚዲያዎች ሃሳብ እንድንሰጥ ይጠይቁን ነበር። በተለይ ወንድማችን ሙሀመድ አልአሩሲ መውጣት ሲጀመር ሁላችንም መደገፍ ጀመርን። ምክንያቱም አንድ ሰው ጭንቅላቱን ካስገባ ሌሎቻችንን ተያይዘን የምናልፈው እንደባቡር ነው የሚል እምነት ስለነበረን ነው።
የተወሰነ ጊዜ ማገዶ መሆን ቢያጋጥምም ማለፉ አይቀርም። ደግሞም ሁላችንም ድምፃችንን ማሰማት ስንጀመር ተሰሚነታችን እያደገ መጣ። አሁንም ቢሆን ግን አረብኛ ተናጋሪ ከሆኑ ኢትዮጵያዊኖች ቁጥር ጋር ሲነፃፀር ስለአገራችን የምንሟገተው ሰዎች በጣም ጥቂት ነን። በየሚዲያው ስንሯሯጥ ይደርስብን የነበረው ዛቻና ማስፈራሪያ ከፍተኛ ነበር።
እኔን በአደባባይ አንድ ኦስትሪያ የሚኖር ግብፃዊ ምሁር በየትኛውም የአረብ ሚዲያ ላይ እንዳልቀርብ ቅስቀሳ አድርጎብኝ ነበር። ይህ የሆነው እንግዲህ ከግድቡ ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት በኋላ ነው።
ግብፆች የምዕራብውያኑን ቀልብ ለመግዛት የሚጠቀሙበት አንዱ ዘዴ የዓባይ ውሃ ኢትዮጵያ የምትገድብ ከሆነ የግብፅ እርሻ እንደሚደርቅ፤ ይህም ወጣቶች ስራ አጥ በመሆን ወደ አውሮፓና አሜሪካ ይሰደዳሉ።
አልያ ደግም አሸባሪ ይሆናሉ የሚል ማስፈራሪያ ነው። ይህንን ሃሳብ የሚያራምዱት ደግሞ የግብፅ የውሃ እና የእርሻ ሚኒስትር መሆናቸው ለእኔ አሳፋሪ ጉዳይ ሆኖብኛል። በአንድ የአረብ ሚዲያ ላይ ቀርቤ እነዚህ ሰዎች በሚኒስትር ደረጃ ተቀምጠው ሳለ ምን ያህል የግብፅን ወጣቶች እንደናቁት የሚያሳይ መሆኑን እንዲሁም ወደ አውሮፓ ሄዳችሁ በለመናችሁት ቴክኖሎጂ እንደበለጣችሁን እናውቃለን።
አሁንም ከምትለምኑ እኛ ጋር ኑና እውቀታችሁን አካፍሉን የሥራ እድልም እንፍጠርላችሁ አልኳቸው። ይህ ንግግሬ በርካታ የግብፅ ምሁራንና አክቲቪስቶችን እጅግ አስቆጣ። በተለይ ኦስትሪያ ያለው ግብፃዊ ‹‹ለግብፅ ወጣት ብቻ ሳይሆን ለመላው የአረብ ወጣት ያለህን ንቀት የሚያሳይ ነው›› አለኝ። እኔ ግን የናቋችሁ ሁለቱ ሚኒስትሮቻችሁ ናቸው እንጂ እኔ አይደለሁም፤ እኔ ለእናንተ እድል ይከፍታል ብዬ ያሰብኩትን ተናገርኩኝ። ይህ ደግሞ የእኔ እይታ እንጂ የኢትዮጵያ መንግስትም ላይቀበለው ይችላል፤ የሚል ምላሽ ሰጠሁት። በነገራችን ላይ እኔና ኡስታስ ጀማል የተዋወቅነው በዚህ አጋጣሚ ነው።
እኔ በአረብኛ ከዚያ ግብፃዊ ጋር ያደረኩትን ክርክር አስተርጉሞት ነበር። ከዚያ ወዲህ እየተቀራረብን መጣንና በጋራ ሥራዎችን መስራት ጀመርን፡፡
አዲስ ዘመን፡- እናንተ ለምትሠሩት ሥራ ድጋፍ የሚያርግላችሁ አካል አለ?
አቶ ዛሂድ፡- ከዚያ በፊት ለዚህ ድል ያበቁንን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ማመስገን እፈልጋለሁ።ከሁሉ በላይ ከአፄ ኃይለስላሴ ጀምሮ ለግድቡ እውን መሆን አስተዋፅኦ ላበረከቱ መሪዎች እውቅና በመስጠታቸው ሳላደንቃቸው ማለፍ አልፈልግም። ለእነሱ ብቻ ሳይሆን አረብኛ ተናጋሪ የሆንን ተሟጋቾችንም አመስግነውናል። ከዚህ ቀደም ግን እኛ የምንሰራውን ስራና የምንከፍለውን ዋጋ ሕዝቡ አያውቅልንም የሚል ቁጭት ነበረኝ።
በነገራችን ላይ የግብፅ ጠላት የሆኑ የውጭ አገራት መንግስታት በግል ደውለው የሚያመስግኑን አሉ። እዚህ ያሉ የውጭ አገራት አምባሳደሮች ሳይቀሩ ለእኛ ያላቸውን ክብር የተለያዩ ድጋፍ በማድረግ ይገልፁልናል። በተቀራኒው የእኛ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና የሚመለከታቸው አካላት በቂ ድጋፍ አድርገውልናል ብዬ ለማለት ይከብደኛል።
በዚህ ሁኔታ ብዙ ጊዜ የተካፋሁባቸው አጋጣሚዎች እንደነበሩ መሸሸግ አልፈልግም። ግን ደግሞ ኡስታአስ ጀማል እውቅና በመሰጠቱ ደስተኛ ነኝ። ይሁንና እንደማገዶ የተቃጠሉ አሁንም ለአገራቸው ዋጋ እየከፈሉ ያሉ ፊት ቢመጡ ደስ ይለኝ ነበር። እርግጥ ነው፤ የሐረሪ መንግስት ለእኔ የሚገባኝ ክብር ሰጦቶኛል። ለዚህም ላመሰግን እወዳለሁ።እኔ ግን ሐረሪን ብቻ አይደለም፤ መላው ኢትዮጵያዊያንን ጭምር አመሰግናለሁ። ኪንግስ ኦፍ ዓባይ የእኛ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያዊ ነው።
የኢትዮጵያ ወዳጆች ጭምር ነው። ምክንያቱም ብር የማሰባሰብ ሥራ ስንሰራ መጀመሪያ ያቀድነው 50 ሺ ዶላር ነበር። በዚህ ጊዜ ግብፃውያኖቹ አልጀዚራና በሌሎች የአረብ ሚዲያ ላይ ወጥተው ኢትዮጵያኖች የፈለገው ቢሆን ይህንን ያህል ብር መሰብሰብ አይችሉም ብለው ፎከሩብን። ኡስታዝ ጀማል ይህንን ሲሰማ እንዳውም ወደ አንድ ሚሊዮን ዶላር ከፍ እናደርገዋለን ብሎ ሲናገር ሕዝቡ መረባረብ ጀመረ።እርግጥ ነው፤ አንዳንድ ሰዎች ገንዘቡን ለግል ጥቅማቸው ያውሉታል የሚል ስጋት ነበረ።
ግን በተለይ በምዕራቡ ዓለም ያለው ኢትዮጵያዊ ኡስታዝ ላይ እምነት ስላለው 50ሺ ዶላሩ በሰዓታት ውስጥ ተሰበሰበ። በአስር ቀን ውስጥም 400 ሺ ዶላር በላይ ማግኘት ቻልን።
አንድ ኩዌታዊ ግለሰብ መጀመሪያ ላይ ለግብፅ ሲከራከር ቆይቶ እውነታውን ስናስረዳው ለግድቡ ግንባታ የለገሰው አንድ ሺ ዶላር ነው። ከዚህ አልፎ እውነታውን ለአረቡ ዓለም የሚያሳይ ዶክመንተሪ ካዘጋጃችሁ እኔ ወጪያችሁን ሁሉ እሸፍናለሁ ብሎ ቃል ገባልን።
ከባንግላዲሽ የሰጠን ሰው አለ። ኤርትራ ውስጥ የኮካ ጠርሙስ እየሸጡ የሚተዳደሩ ሴት ድጋፍ አድርገዋል። በአጠቃላይ መነሻው የአገር ጉዳይ ስለሆነና እልህና ቁጭት ስላለ ከጠበቅነው በላይ ድጋፍ ማሰባሰብ ችለናል፡፡
አዲስ ዘመን፡- ታዲያ ከዚያ ሁሉ በኋላ አሁን ላይ ግድቡ ኃይል ማመንጨት መጀመሩ ምን ስሜት ፈጠረብዎት?
አቶ ዛሂድ፡- በነገራችን ላይ ግብፆች አሁንም ድረስ የሃሰት ፕሮፖጋንዳቸውን አላቆሙም። በተለይ ግንባታው ላይ የተለያዩ እንከኖችን እያነሱ የዓለም ሕዝብ ትኩረት ለመሳብ ጥረት ያደርጋሉ። በተለይም የግድቡ ተርባይኖቹ በመበላሸቱ ዶክተር ዐቢይ ኢንጂነር ስለሺን ከስልጣን እንዳነሳ አድርገው በየሚዲያዎቻቸው ሲነዙት የቆዩት በሬ ወለደ ወሬ በጣም ያስደንቀኛል።
የሚገርመው ያቀረቡት ሰበር ዜና አድርገው ነበር።ግን ወሬው ሃሰትም ቢሆን ሕዝባቸውን ለማሳመን አግዟቸው ነበር። ይሁንና ሰሞኑን የኃይል ማመንጨቱ ብስራት በተነገረበት እለት ዶክተር ዐቢይ ኢንጂነር ስለሺን በይፋ ማመስገናቸው ለግብፅ ፕሮፖጋንዲስቶች ትልቅ መልስ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። ከመጀመሪያው ጀምሮ ‹‹ግድቡ አይሰራም›› አሉ። ነገር ግን ደግሞ ተሰራ፤ ‹‹አይሞላም›› ቢሉም ተሞላ። ‹‹ኃይል አይመነጭም›› አሉ፤ ይህንንም ችለን በማሳየታችን የስነልቦና የበላይት እንድናገኝ አድርጎናል ባይ ነኝ።
በተለይ እኔ የግድቡ እውን መሆን ቀድሞም ባልጠራጠርም ግን ደግሞ ይደርስብን ከነበረው ጫና አንፃር የዚያን ቀን የተሰማኝ ስሜት ልክ ልጅ እንደተወለደልኝ አይነት ስሜት ነው።ግን ደግሞ ይህ ቀን ከዚህም በላይ በድምቀት ሊከበር ይገባ ነበር ብዬ አምናለሁ። በእለቱ እንደእብድ መንገድ ላይ ሁሉ እያወራሁና እየሳኩኝ ነው የዋልኩት።በአጠቃላይ ደስታውን በቃላት ልገልፀው አልችልም።
አዲስ ዘመን፡- የግድቡ ኃይል ማመንጨት ዜና በአረቡ ዓለም ላይ የፈጠረው ስሜት ምን ይመስላል?
አቶ ዚሃድ፡- አሁንም ቢሆን በተለይ ናድር ኑረዲን የተባለው የግብፅ የውሃ ሚኒስትር እውነታውን መቀበል አልቻለም። ይህ ግለሰብ የእርሻ ባለሙያ እንጂ ስለውሃ የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ሚሊዮኖች በሚከታተሉት የአልጀዚራ የቀጥታ ፕሮግራም ላይ ተገናኝተን አፋጠጥነው፤ ምላሽ መስጠት ተሳነው። በቅርቡ በሩሲያ ቴሌቪዥን ላይ ቀርቦ ደግሞ ‹‹ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አላመነጨችም፤ ያስተላለፈችው ውሃ ነው፡፡›› እያለ ሲናገር ነበር።
በአጠቃላይ በተለያዩ ሚዲያዎች ላይ እየቀረቡ ግድቡ ችግር እንዳለበት መግለፃቸውን ቀጥለዋል።ግን ይህ ፈፅሞ ከእውነት የራቀ እንደሆነ እሙን ነው። የውሸት ፕሮፖጋንዳቸውን ሲነዙ ምንም እንኳን መቶ በመቶ ባይባልም እንኳን ግማሹን ሕዝብ ማሳመን ችለዋል። አንድ ሶስተኛ የሚሆነው የአረብ ሕዝብ አምኖላቸዋል።
ይህ በሚዲያ ኃይል ያገኙት ነው።አንዳንዱ ወሬያቸው ግን በተጨባጭ መሬት ላይ ያለው ነገር ይመስላል።ለምሳሌ የሲሚንቶ እጥረት ስላለ ግድቡ ግንባታው እንደተስተጓጓለ፤ ግድቡን የሚጠብቁ ወታደሮች በአማፂዎች በቀስት እንደሚገደሉ ይናገራሉ።ይህ ወሬ ሲታይው በከፊል ሊያሳምን ይችላል። ሚያዚያ ወር ግንባታው ከፍ የሚልበትና የውሃው መጠን የሚቀንስበት በመሆኑ ጩኸታቸው፤ ከዚህ በላይ ሊበረታ እንደሚችል አስባለሁ።
ከሰኔ በኋላ ደግሞ ሶስተኛው ዙር የውሃ ሙሌት ሲከናወን በየሚዲያው የተለመደው ለቅሷቸውን ይቀጥላሉ። ስለዚህ እኛም በዚያው ልክ ለፕሮፖጋንዳ ዘመቻው ከዚህ በላይ መዘጋጀት አለብን።ከዚያ በላይ ደግሞ ውስጣዊ ሰላማችን መሻሻል አለበት።በረባ ባልረባው እየተባላን መቀጠል የለብንም።በተለይ የእምነት አባቶች ለአገር ዘላቂ ሰላም መስፈን ወሳኝ ሚና ሊጫወቱ ይገባል ባይ ነኝ።
አዲስ ዘመን፡- በውጭ ያለውን ጫና በመከላከል ረገድ ምን መሰራት አለበት?
አቶ ዚሃድ፡- እንደተባለው የውጭ ጫናው እየበረታ መጥቷል።በተለይም አሜሪካና ምዕራብውያኑ የአፍሪካውያን ሕይወት በእጃቸው እንዳለ ስለሚያስቡ እንደፈለጉ ሊበታትኑን እንጂ እንድንለወጥ አይሹም።
የተለያዩ ማስፈራሪያዎች እያደረጉብን ያለው ለእዚህም ነው። እኛ ግን ሁሌም ቢሆን ተጨማሪ ፕላን ልናቅድ ይገባል።እነሱ ማዕቀብ ቢያደርጉም እንደቻይና እና ሩሲያ ያሉ የዓለም ሃያላን አገራት አማራጮቻችን እንደሆኑ ማሳየት መቻል አለብን።ሁሌም አማራጭ ሊኖረን ይገባል።አፍሪካውያን እጅና ጓንት ሆነው መሥራትና አህጉሪቱን ከምዕራብውያን ጫና ማላቀቅ አለባቸው።
በተመሳሳይ ኢትዮጵያኖች የአገራችንን ጥቅም ለማስጠበቅና የውጭ ጫናውን ለመከላከል ህብረታችንን ማጠናከር ይገባል። እነሱም ቢሆኑ የሚፈልጉት ጥቅማቸውን ነው። በአገር ልንደራደር አንችልም። በነገራችን ላይ የአሜሪካ መሪዎች የቱንም ያህል ቢደነፉ ያወሩትን ሁሉ አይተገብሩም። ከዚህ ቀደም ዶናልድ ትራምፕ በግድቡ ላይ ብዙ ሲዝት እንደነበር እናውቃለን፤ ግን አንዱም አልሆነም።
አሁንም ባይደን ብዙ ቢያወራም ይተገብረዋል ማለት አይደለም።አሜሪካ ደግሞ ፕሬዚዳንቱ የተናገረው ሁሉ የሚፈፀምባት አገር አይደለችም፤ ምክር ቤቶቻቸውና በየደረጃው ያለው የመንግስት አካልን ውሳኔ እስካልታከለበት የትኛውም ማስፈራሪያ አዘል መመሪያና አዋጅ አይተገበርም። አረብ አገራት ላይ ዲፕሎማሲ በመስራትም ረገድ ሰፊ ክፍተት አለብን። አምባሳደሮቻችን የሚመደቡት የየአገሩን ቋንቋና ባህል አውቀው አይደለም።
ይህም የአረቦችን የልብ ትርታ እንዳያዳምጡ ምክንያት ሆኗል ባይ ነኝ።አረብ አገር ላይ ያሉ ዲፕሎማቶችን ስለአገራቸው የሚወራውን እና የሚሰራውን ደባ ነቅተው ሊጠብቁ ይገባል።ደግሞም ሁሉም አረብ የኢትዮጵያ ጠላት አለመሆኑን መገንዘብ አለብን። አብዛኛው ዓለም ፊቱን ሲያዞርብን ከጎናችን የቆመችው የተባበሩት አረብ ኢምሬት ናት።
ይህንን ጠቅላይ ሚኒስትራችን የመሰከሩት ጉዳይ ነው። ስለዚህ አረብ ብለን በደፈናው ሁሉንም በመጥፎ መፈረጅ የለብንም። አንድ ጊዜ ሁሉንም አረብ አገር በአንድ ጨፍልቀን የምንናገረው ነገር ወዳጅ አገራትን ሊያሳጣን ስለሚችል ጥንቃቄ ማድረግ ይጠበቅብናል።ከስሜት መውጣት በሚዛናዊነት ማሰብ ይገባናል።
እንደሚታወሰው የኢምሬቱ አልጋ ወራሽ እኮ በኢድ እለት ኢትዮጵያ ድረስ መጥተው የሶስት ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ አድርገዋል። ይህን ያደረጉት ምናልባት የጋራ ጥቅም ስላለው ነው ሊባል ይችላል፤ ግን ከሁሉ በላይ በአረቦች በኢድ እለት ወደ ሌላ አገር መሄድ ልዩ ትርጉም አለው።
ለእዚያ ያላቸውን ከበሬታና ፍቅር የሚገልፀው ነው።አንዳንድ ጊዜ የእዚህ ትርጉም የማይረዱ ዲፕሎማቶች ያጋጥሙኛል። የአረቦችን ባህል ማወቅ ጠቃሚ ነው፤ ያልኩት ለዚህ ነው፡፡ እርግጥ ነው፤ ግብፅ የአረብ ሊግ መስራች፤ መቀመጫና ሰፊውን ስልጣን የምትይዝ እንደመሆንዋ በአረብ አገራቱ ላይ ተፅዕኖ እንደምትፈጥር እሙን ነው።ግን ደግሞ ሁሉም ግብፅን ይደገፋሉ ማለት አይደለም።እንዳውም በቢላል ምክንያት ኢትዮጵያን የሚወዱ በርካታ አረብ አገራት አሉ። ለሃበሻ ልዩ ፍቅርና አክብሮት ያላቸውም ጥቂት አይደሉም።
ሁሉም ሰው እንደሚያውቀው ደግሞ ነብዩ ማሃመድ ሃበሾችን እንዳትነኩ ብለው ከሌላው ሕዝብ ለይተው ቦታ ሰጥተዋል። ስለዚህ ትክክለኛ ቁርዓን አዋቂ የሆነ አረብ የኢትዮጵያ ደጋፊ ነው።በቅርቡ በአፍሪካ ህብረት ላይ የተገኙት የቱኒዚያ መሪዎች ኢትዮጵያን ይቅርታ ጠይቀዋል። ስለዚህ በሂደት ሌሎችም አገራት ወደ እኛ ሃሳብ መምጣታቸው አይቀርም።
አዲስ ዘመን፡- እንደሳውዲ ተወላጅነትዎ በዚያች አገር በኢትዮጵያኖች ላይ እየፈፀመች ያለችው ግፍ ስታስቡ የሚሰማዎን ስሜት ቢገልፁልኝ? አንዳንዶች የግብፅ እጅ አለበት ይላሉ፤ በዚህ ሃሳብ ይስማማሉ?
አቶ ዛሂድ፡- እኔ ሳውዳ አረቢያ በኢትዮጵያኖች ላይ ይህንን አይነቱ ግፍ እየፈፀመች ያለችው የግብፅ መንግስት ጫና አሳድሮባት ነው ብዬ አላምንም።እርግጥ ነው አብረው የሚሰሩበት ስምምነት እንዳላቸው ይታወቃል።
ግን በዚህ ጉዳይ ላይ ግልፅ የሆነ መረጃ ስለሌለ እንዲህ ነው ብዬ ለመናገር ይከብደኛል።አንቺም እንዳልሽው እኔም በተመሳሳይ መንገድ ሲወራ ሰምቻለሁ።ግን ደግሞ ኢትዮጵያኖች ላይ የሚፈፀመው ግፍ በጣም የሚያሳዝን ነው። ይህንን ጉዳይ በሚመለከት እስከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ድረስ በመሄድ ለማነጋገር ሞክረናል።
ፈጣሪ ይመስገን፤ ከዚያ በኋላ ልዑካን ቡድን በመላክ ሁኔታውን ለማጣራት ተሞክሯል።ሆኖም መንግስትም ሆነ ብዙዎቻችን እንደምናምነው ዋናው ክፍተት ያለው ከእኛ ነው።
አገራችን በጦርነት ላይ በመቆየቷ በዜጎች ጉዳይ ላይ ትኩረት ማድረግ አልተቻለም።የማያጠያይቀውና አፋጣኝ እርምጃ ሊወሰድበት የሚገባው ጉዳይ እዛ ያሉ ወገኖቻችን ከስቃይ መታደጉ ላይ ነው።
አዲስ ዘመን፡- ለነበረን ቆይታ በአንባቢዎቼና በዝግጅት ክፍሉ ሥም ከልብ አመሰግናለሁ፡፡
አቶ ዛሂድ፡- እኔም አመሰግናለሁ።
ማህሌት አብዱል
አዲስ ዘመን የካቲት 19 /2014