ማዋዣ፤
ለዚህ ጽሑፍ የተሰጠው ርዕስ በትርጉምና በይዘቱ ጠንከርና ከበድ ያለ አንድ ሃይማኖታዊ መሳጭ ጸሎት እንደሚያስታውስን ቀድሜ ልግለጽ። ይህ የሕዝበ ክርስቲያን የዘወትር ጸሎት የሰላምና የትህትና መገለጫ ጭምር ስለሆነ ፋይዳው ከፍ ያለ ነው። በተለይም ሚሊዮኖች የክርስቶስ ተከታይ አማኒያን በሚያከብሩት በዚህ በዛሬው የዐውድ ዓመት ዕለት የዚህ ጽሐፍ ርዕስ የሚያስተውሰን ጸሎት ተደጋግሞ ወደ ፀባዖት ስለሚያርግ እኛም ዐውዱ ስለሚደግፈን “ኢትዮጵያ ሆይ ሰላም ለኪ” (ሰላም ላንቺ ይሁን) ብለን ብንተባበር የአገራችን እናትነት ክብርና የታሪኳ ግዝፈት ግድ ይለናል።
አንዳንድ ጉዳዮች ተደጋግመው እንዲታወሱ ሁኔታዎች ያስገድዱናል። በመደጋገማቸውም መልዕክቱ በሰሚዎቹና በአንባቢዎቹ አዕምሮ ውስጥ ተቀርጾ እንዲቆይ ያግዛል። በዚህ ሁነኛ ምክንያት ተደፋፍሬ በአንድ ወቅት በዚሁ ጋዜጣ ላይ ከንባቤ ማግኘቴን ጠቅሼ ነካ በማድረግ ያለፍኩትን አንድ ታሪክ ዘርዘር አድርጌ ላስታውስ።
ታሪኩ በእርግጥም ተፈጽሞ ከሆነ እሰየው። የጠቢባን አእምሮ የቀረጸው ማስተማሪያም ከሆነ ግሩም የፈጠራ ታሪክ ነው። ስለሆነም እኔም ከንባቤ ያተረፍኩትን መልሼ ለአንባቢያን እንደሚከተለው ላካፍል። በአንድ አገርና በአንድ ወቅት ተፈጸመ የሚባለው ይህ ክስተት ዝርዝር መረጃ ስለማይሰጥ መቼ እና እንዴት ሊሆን ቻለ ለሚሉት ጥያቄዎች ተገቢውን መልስ ለመስጠት ያዳግታል።
ታሪኩ ተፈጸመ የሚባለው በአንድ ዓለም አቀፍ የዝነኛ ሠዓሊያን የሥዕል ውድድር ላይ ነው። ለመጨረሻ ውድድር ለቀረቡት ሦስት ተፋላሚዎች የተሰጠው ርዕስ “ሰላም” የሚል ነበር። ሠዓሊያኑ ይህንን ግዙፍ ርዕስ የሚወክለውን የየግል ሥዕላቸውን ያቀረቡት በነፍስ ወከፍ በተመደበላቸው ክፍሎች ውስጥ ሸራቸውን በመዘርጋት ነበር።
በዝና ላይ ዝና የተጎናጸፉ ሦስት ዳኞች በጋራ የሚመርጡትን አሸናፊ ሠዓሊ ለመምረጥ ሰዓቱ ደርሶ ውድድሩ ተጀመረ። የመጀመሪያውን ሠዓሊ ሥራ ለማየት ዳኞቹ የክፍሉን በር ዘልቀው በመግባት “ሰላምን” የሚወክለውን ሥዕል መመርመር ጀመሩ። በተወጠረው ሸራ ላይ የቀረበው ሥዕል ፍሬው የተንዠረገገና ብሉኝ ብሉኝ እያለ የሚያስጎመጅ ለምለም ዛፍ ነበር። በሞገስም በይዘትም የገዘፈ የፍሬ ዛፍ።
ዳኞቹ የአሳሳሉን ጥበብ በየግላቸው እያደነቁ በሚገመግሙበት ወቅት አንዲት ወፍ ቱር ብላ በመግባት ሥዕሉ እውነተኛ ዛፍ መስሏት ፍሬውን ልትበላ ከሸራው ላይ ግብግብ ፈጠረች። ገምጋሚዎቹ ዳኞች በክስተቱ እጅግ ተገርመው “ሆ! ሆ! ይህ ሠዓሊ ተፈጥሮን እንኳን የሚያሳስት ጥበብ የታደለ ባለ ተሰጥዖ ነው” በማለት አግራሞታቸውን ገልጸውና በየግላቸው ውጤት ሰጥተው ወደ ሁለተኛው ሠዓሊ ክፍል አመሩ።
ሁለተኛው ሠዓሊ ሰላምን የወከለው እጅግ ውብና አማላይ በሆነ መጋረጃ ነበር። ዳኞቹ ወደ ክፍሉ ውስጥ ሲገቡ ሥዕሉ እውነተኛ ስለመሰላቸው ገለጥ አድርገው ወደ ውስጠኛው ክፍል ለመዝለቅ እጃቸውን በጋራ በመዘርጋት መጋረጃውን ለመግለጥ ሞከሩ። ሥዕል መሆኑ ሲገባቸው ግን በውስጣዊ እፍረት አንገታቸውን በመፋት በመታለላቸው ተጸጽተው እጃቸውን በመሰብሰብ በአፋቸው ላይ ጫኑ። የመጀመሪያው ሠዓሊ ተፈጥሮን (ወፏን) አታለለ፤ ይህ ሁለተኛው ሠዓሊ ደግሞ እኛን ዳኞቹን ሳይቀር በጥበቡ ርቅቀት እውነተኛ መጋረጃ እስኪመስለን ደረስ አዕምሯችንን ሰለበ። “ሆቸ ጉድ አይጣልን ያቀሏል!” እየተባባሉ ወደ ሦስተኛው ሠዓሊ ክፍል አመሩ።
ይህ የመጨረሻውና ሦስተኛው ሠዓሊ ሰላምን የወከለበት ሥዕሉ እጅግም የተወሳሰበ አልነበረም። በሸራው ላይ የሣለው አንድ በማዕበል የሚናወጥ ባህርን ነበር። በባህሩ መካከል ግዙፍ ቋጥኝ ጎላ ብሎ ይታያል። በቋጥኙ ላይ አንዲት ወፍ መንቆሯን ወደ ሰማይ አቅንታ ትዘምራለች። ለማዕበሉ መደንፋት ቁብ የሰጠች አትመስልም። ገምጋሚ ዳኞቹ ውጤት ለመስጠት እጅግም አልተቸገሩም።
ወፏን (ተፈጥሮን) ያማለለውን ሠዓሊ ከልብ አድንቀው በማጨብጨብ ሥራው ግን “ሰላምን” ሊወክል እንደማይችል አረጋገጡ። የሁለተኛውንም ሥዕል እንዲሁ በማድነቅና ዳኞቹን ራሳቸውን በማታለሉ አድንቀው ይዘቱ ርዕሱን እንደማያገዝፍ በመስማማት ለአሸናፊነት ሳያበቁት ዘለሉት። የተንዠረገገው የፍሬ ዛፍም ሆነ ውብ መጋረጃው ለአድናቆትና በስሜት ለመርካት ብቻ ካልሆነ በስተቀር የሰላም ውክልናቸው በእጅጉ የሳሳ መሆኑን በጋራ ተስማምተዋል። የማረካቸው የሦስተኛው ሠዓሊ የጥበብ ሥራ ነው።
“በማዕበል የሚናወጥ ባህር። ለማዕበሉ ሁከትና ድንፋታ ቁብ ሳትሰጥ ተስፋ በመሰነቅ የምትዘምር ገራሚ ወፍ – በርግጥም ለሰላም ውክልና የሚመጥን ምናብ ወለድ የጥበብ ስራ ነው።” ሦስቱም በአንድነት በአሜንታ ተስማሙ። አሸናፊውን “የጥበብ ጀግናም” ከእንኳን ደስ ያለህ አድናቆት ጋር በሽልማት አንበሸበሹት።
አገሬ ሆይ ሰላም ለኪ!
የኢትዮጵያን ዛሬያዊ ሁኔታ በሦስተኛው ሥዕል ብንወክል ብዙም ልዩነት ላይኖረን ይችል ይመስለኛል። በዚህ የወቅት ክፉ እናት አገራችን በብዙ ወጀቦች እንደተከበበች እያስተዋልን ነው። ያለምንም ማዳነቅ ኢትዮጵያን የከበቡትና በወጀብ የሚመሰሉት የዚህ ወቅት ክስተቶች ከአሁን ቀደም በታሪካችን ውስጥ ተፈጽመው ስለመሆናቸው ከሰንዶችን ብናገላብጥ ፍንጭ የምናገኝ አይመስለኝም። ደፈር ብለን የሌሎች አገራትን ታሪክም ጎን ለጎን እንፈትሽ ብንል እንኳን በእርግጠኛነት የእኛን መሰል ፈተና ደርሶባቸው የነበሩ ብጤዎችን ማግኘት የሚቻል አይመስለኝም።
የውስጥ ከሃዲያንና አሸባሪዎች በዕብሪት ሰክረው ጦር በመምዘዝ የብዙ ንጹሐን ወገኖቻችንን ሕይወት ቅርጥፍ አድርገው በልተዋል። ብዙ ዜጎቻችንም ለአካልና ለስሜት ስብራት ተዳርገው ልቅሶ የእለት ቀለባቸው ሆኗል። በቢሊዮን ብሮች የሚቆጠር የመንግሥትና የግል ንብረት ወድሟል፤ ከስሏል። የወረራው ተቀዳሚ ሰለባ በሆኑት የአማራ፣ የአፋር ክልሎችና በሸኔ ተብዬው እብሪት በየአካባቢው የተሰዉትንና የተፈናቀሉትን ነፍሶች አስልተንና የወደሙትን ንብረቶች መጠን መርምረን የመከራችንን ወርድና ስፋት እንመትር ብንል በድምዳሜ ላይ ለመድረስ ገና ብዙ ጥናት ማድረግ ይቀረናል። ሰሞንኛው የድርቅ ማዕበልም በዙሪያችን ተጋርጦ እያስነከሰን ነው።
ከአገራዊ ተግዳሮታችን ጎን ለጎንም “የኃያልነትን ክብር” ለራሳቸው በሰጡ በርካታ የውጭ መንግሥታት አገሬን ፊት ተነስታ አኩራፊው በዝቶባታል። ማኩረፍ ብቻም ሳይሆን የማዕበሉን መናወጥ ይበልጥ ለማተረማመስ የባህር ጃዊሳ ሆነውብናል። በተሰነጠረ ሸንበቆ እየመሰሉም ሊሰብሩን ተግተዋል። ተስፋችንን ጭል ጭል በሚል የኩራዝ ብርሃን በመመሰልም አሟርተውብናል።
የተለያዩ የተንኮል ወጥመዶች እየዘረጉብንም ሊያዳክሙን ፈልገው ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም። አንዴ በማዕቀብ፣ አንዴ ርዳታ በማቆም፣ ሲላቸው የልማት ድጋፋቸውን በማቋረጥ፣ አልሳካ ሲላቸው የንግድ አከርካሪያችንን ለመስበር ቀንና ሌሊት ይወራጫሉ። የኢትዮጵያን የተስፋ ወጋገን ሳያጨልሙ እንደማይመለሱ በመፎከርም በነጋ ጠባ ቅዠታቸው ሲያልሙ የሚያድሩት መፈራረሳችንን ነው። አንዳንዶች “ድንጋይን የሚፈነቅል እፉኝት ይነድፈዋል” እንዲሉ በእኛ ላይ የሚያስፈነጥሩት ቀስት ወደራሳቸው ዞሮ ሲያቆስላቸው እያስተዋልን ነው።
የአንዳንድ አገራት ሚዲያዎችም ጭርሱኑ ሰክረዋል ቢባል የተሻለ ይሆናል። የሙያ ሥነ ምግባራቸውን አርክሰውና ቃል ኪዳናቸውን አግማምተው በዱልዱም ብዕራቸው እየጎነተሉና በተበከለው አየራቸው እያጠኑ ሊያስነጥሱን የማይቧጥጡት ተራራ የለም። ቢሯቸውን ዘግተው የሀሰት ዜናና ትንታኔ የሚፈበርኩት ኅሊናቸውን ገድለውና ሰብዕናቸውን አግማምተው መሆኑን እያወቁም ቢሆን ዛሬም ድረስ ከድርጊታቸው ሊታቀቡ አልቻሉም።
የዛሬዪቱን ኢትዮጵያ የከበቡት ማዕበሎችና ወጀቦች እነዚህ ብቻ ሳይሆኑ በመልክም በአይነትም ሆነ በቁጥር የተዥጎረጎሩ ስለሆኑ ዘርዝሮ ለመግለጽ ያዳግታል። ወጀቡ ቢበረታም አገሬ የሚናወጠውን ባህር እያስተዋለች አላዞራትም፤ አላጥወለወላትምም። ለከበባት ማዕበልም እጅ ሰጥታ ገበርኩ አላለችም። እጆቿንም ለተዘጋጁላት ሰንሰለቶች ሰጥታም አልተሸነፈችም። ለማራኪነት ያሰፈሰፉ የከንቱዎች ጨኸትም አላስበረገጋትም። የቆመችበት ጽኑ የኅብረ ብሔራዊነት አለቷ እጅግ የገዘፈ ብቻም ሳይሆን የሚጋጫትን ኃይል ለመሰባበር የበረታ ነው። የሉዓላዊነት ክብሯም በአርቴፊሻል ሆይ ሆይታ ሳይሆን በእሳት እንደነጠረ ወርቅ ተፈትኖ በከበረና በደም በቀለመ መስተጋብር የተሸመነ መሆኑን አጥብቃ ለዓለም በማስተዋወቅ ላይ ነች።
የባህሩና የውቅያኖሱ ወጀብና ተግዳሮት ሳይበግራቸው ከዓለም ጫፍ እስከ ጫፍ ማዕበሉን ሰንጥቀው እየመተሩ በመቅዘፍ ወደ አገር ከተሰባሰቡት ተወላጅ ልጆቿ ጋራ ኢትዮጵያ መከራዋን ሳይሆን አሸናፊነቷን እየዘመረች ያለችው በይቻላል ዜማ ቃኝታ እንጂ በሽንፈት እንጉርጉሮ እየተከዘች አይደለም።
እስትንፋሳቸው በግፍ የጨለመባቸው ዜጎቻችን አንድነታችንን አጠናከሩልን እንጂ ለቁዘማ አልዳረጉንም። እንደ ክፉዎቹ የቅርብና የሩቅ ጠላቶቻችን ምኞት ቢሆን ኖሮማ የማዕበሉ አስፈሪነት አስበርግጎ ባብረከረከን ነበር። ኢትዮጵያ ዛሬ በአሸናፊነት፣ ነገም በሰላም አብሳሪነት መዘመሯን ትቀጥላላች። ኢትዮጵያ ሆይ በወጀቡ ግልቢያና ማጓራት እንዳትበገሪ ሰላም ለኪ ብለን እንመርቅሻለን። ሰላም ለኪ እናት ዓለም! ሰላም ለኪ ሀገሬ! ሰላም ለኪ ለሁልጊዜም። አሜን!
(ጌታቸው በለጠ /ዳግላስ ጴጥሮስ)
gechoseni@gmail.com
አዲስ ዘመን ጥር 11/2014