ቅዳሜ ታህሳስ 9 ቀን 2014 ዓ.ም የኢትዮጵያ የከፍተኛ ትምህርት ኢንስቲትዩት ከጀርመኑ ጂ.አይ.ዜድ እና ሌሎችም ጋር በመተባበር፣ በከፍተኛ ትምህርት አመራር ጥበብ ለሶስት አመት ሲሰጥ የነበረውን ስልጠና ያጠናቀቁ የሁለተኛው ዙር ሰልጣኞችን በስካይላይት ሆቴል (አዲስ አበባ) አስመርቋል።
ስልጠናው በተግባር የተደገፈ፣ በሞጁል የታገዘ እንደነበር በእለቱ የተገለፀ ሲሆን፤ ሰልጣኞች ወደ ተቋሞቻቸው ሲመለሱ ወደ ተግባር እንደሚለውጡትና በየተቋሞቻቸው ያሉ ችግሮችን በአግባቡና በእውቀትና ክሂሎት ላይ በተመሰረተ አሰራር በመፍታት ውጤታማ እንደሚሆኑ በእለቱ የመዝጊያ ንግግር ያደረጉት የትምህርት ሚኒስቴር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊ የሆኑት ሰለሞን አብርሃ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
ይህ በአራት ምድብ (Cohort)፣ ሶስት ዙር የተለየውና ከ46 ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ 377 (ከ40 በመቶ በላይ ሴቶች) የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አመራሮች የተመረቁበት ስልጠና በተቋማቱ ውስጥ በየደረጃው ያሉ አመራሮች (ከፍተኛ፣ መካከለኛለና መሰረታዊ አመራሮች) ላይ ያተኮረ ሲሆን፤ አላማውም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የሚያጋጥሙ፣ እየተወሳሰቡም በመሄድ ላይ የሚገኙ ችግሮችን እንዴት መፍታት እንደሚቻል በእውቀትና ክሂሎት የተደገፈ አመራርና አሰራርን ተግባራዊ ማድረግ፤ እንዲሁም በየተቋማቱ ሰላማዊ የመማር-ማስተማር ሂደት እንዲኖር ማስቻል ነው። ወደዚህ ፕሮግራም ከመግባታችን በፊት ለአንባቢያን የተወሰነ ዳራን ለመስጠት ያህል ድህረ 1983 ዓ.ም ያለውን በብዛት ላይ በማተኮሩ በትምህርት ጥራት ላይ ችግር እንደነበረበት ሲነገርለት ስለቆየው የአገሪቱ የትምህርት ፖሊሲ ቆንጠር አድርገን እንመልከት።
በአንድ ወቅት የአዲስ አድማሱ ዮሀንስ አዲሱን የትምህርት ፍኖተ ካርታ አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት የሰነዱን ይዘት በተመለከተ “ለተሳከረው የአገራችን ትምህርት መፍትሄው ‘ከእውቀት የራቀ ትምህርት’ ነው?” በማለት ከጠየቀ በኋላ “ከሦስተኛ ክፍል ተማሪዎች መካከል፣ ግማሽ ያህሉ (ማለትም 50%)፣ አንዲት አጭር ዓረፍተ ነገር አንብበው ለመገንዘብ የሚያስችል እውቀት እንኳን የላቸውም። ሩብ (25%) ያህሉ ደግሞ አንዲትም ቃል ማንበብ አይችሉም። [ይህ] ውድቀት… በእጣ ፋንታ ሰበብ የወረደ ክፉ መዓት፣ ባልታወቀ ፍጡር የተወረወረ እርግማን አይደለም… ‘ከእውቀት የራቀ የማወቅ ክሂሎትን እናስተምራለን’ በሚል የተሳከረ አስተሳሰብ የተቃኘ ትምህርት… ” በማለት አስተያየቱን ማስፈሩን ተከትሉ የተለያዩ ሰዎችም አስተያየታቸውን መሰንዘር ጀምረው ሀሳቦች ሲንሸራሸሩ ነበር። ይህ፣ እዚህ የጠቀስነው የዮሀንስ አስተያየት እጅግ በጣም ከብዙዎቹ አስተያየቶች አንዱ ነው።
ይህ እና ሌሎች መሰል አስተያየቶች የአስተያየት ሰጪዎቹ ተቆርቋሪ ግለሰቦች ሀሳብ ብቻ አይደለም። የጉዳዩ ባለቤት የሆነው ትምህርት ሚኒስቴርም የሚስማማበት ሀሳብ ነው።
በትምህርት ሚኒስቴር የአመራርና አስተዳደር ጀነራል ዳይሬክተር ሰለሞን አብርሃ (ዶ/ር)ም በዚህ የሚስማሙ ሲሆን፤ በመግቢያችን ላይ በጠቀስነው የምረቃ በአል መዝጊያ ሥነስርአት ላይ የነበረው የትምህርት ስርአት ተደራሽነት ላይ እንጂ ጥራት ላይ ባተኮረ መልኩ አለመሰራቱን መግለፃቸው እየተነጋገርንበት ላለነው መሰረታዊና አንገብጋቢ ጉዳይ አንዱ ማሳያ ነው።
“ላለፉት 28/9 ዓመታት አገልግሎት ላይ የዋለው የአገሪቱ የትምህርት ፖሊሲ አገሪቱ ሕገ መንግሥት እንኳ ሳይኖራት፣ የምትመራበት ርዕዮተ-ዓለም ምን እንደሆነ በቅጡ ሳይታወቅ፣ ሁሉም ባለ ድርሻ አካላትና በወቅቱ የነበሩ የፖለቲካ ኃይሎች በአግባቡ ሳይመክሩበትና ምርጫ ተካሂዶ ቋሚ መንግሥት ሳይመሰረት በይድረስ ይድረስ፣ የአንድን የፖለቲካ ቡድን ፍላጎት ማዕከል አድርጎ፣ ይሁንታ (mandate) በሌለው አካል የተዘጋጀ” ተብሎ በሰፊው የሚተቸውና እስከ ዛሬ ድረስ እየተሰራበት ያለው የአገሪቱ የትምህርት ፖሊሲ (“አዲሱ የትምህርት ፖሊሲ” በሚል ተዘወትሮ የሚጠራው) በአብዛኛው ብቻ ሳይሆን “አንድም ጠንካራ ጎን” የሌለው እስኪመስል ድረስ ሲወቀስ የኖረ አነታራኪ ሰነድ ነው። ይህ ደግሞ የዐቢይ አስተዳደር ኃላፊነቱን ከተረከበ ወዲህ በተደረጉ ጥናቶ እየተረጋገጠ ነውና የተጋነነ አስተያየት አድርጎ ለመውሰድ ያስቸግራል። ስለ ጉዳዩ የበለጠ ለማወቅ በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር (ዛሬ የለም) አማካኝነት ተደርገው የነበሩ ጥናቶችን መመልከት ይቻላል።
በአዲሱ የትምህርት ፍኖተ ካርታ ላይ ሰፍሮ እንደሚገኘው አገሪቱ የምትከተለው የትምህርት ፍልስፍና፤
“(1) ዜጐች በራሳቸው የሚተማመኑ፣ ብቁና በምክንያታዊ ትንተና የሚያምኑ፣ በሙያቸው ብቃት ያላቸው በአለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪና ብቁ ዜጋ አድርጐ አጠቃላይ ሰብእናቸውን መገንባት፤ (2) ሥራ ፈጣሪዎች፣ አዳዲስ ግኝቶችን አፍላቂዎች፣ ጠንካራ የሥነ ምግባርና ግብረ ገባዊ እሴቶችን የተላበሱና ለሕግ ዘብ የቆሙ ዜጐችን ማፍራት (3) ብዝሃነትን ላካተተው አገራዊ አንድነትና ሠላም ዘብ እንዲቆሙ ማድረግ” የሚል ነው።
ይህን የትምህርት ፍልስፍና እውን ለማድረግ በርካታ ስራዎች መሰራት ያለባቸው ሲሆን አንዱም የአመራር ብቃት ላይ መስራት መሆኑ አይካድም። በተለይም ከግጭት አፈታት ጋር በተያያዘ የአመራር ሚና ቁልፍ ከመሆኑ አኳያ ዘርፉ ለአፍታም ችላ ሊባል የሚችል አይደለም። በተለይ ወደ ኋላ መለስ ብሎ ለተመለከተና የአንዳንድ ዩኒቨርሲቲ አመራሮች ሳይቀሩ በብሄር ግጭት ውስጥ ገብተው፣ ከመፍትሄ አካልነት ይልቅ የችግሩ አካል ሆነው ግጭቱን ከእሳቱ ወደ ረመጡ ሲያሸጋግሩ የነበሩ መሆናቸውን ላስታወሰ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አመራሮች እንደዚህ አይነት ስልጠና እንደሚያስፈልጋቸው ደመ ነፍሱ ይነግረዋል። ከዚህ አንፃር ትምህርት ሚኒስቴር ይህንን ክፍተት ለመሙላት እየወሰደ ያለው እርምጃ የሚያበረታታ ሆኖ ነው የሚገኘው።
በተለይም ዶ/ር ሰለሞን አብርሃ ይህ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አመራሮችን የማብቃት ፕሮግራም በመጪው አምስት አመት ውስጥ በተከታታይ የሚሰጥ ሲሆን ለዚህም ዝግጅቱ አልቋል ካሉት አኳያ ሲታይ በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን ውስጥ ያሉ ችግሮች መቋጫ ሊያገኙ ነው የሚል ተስፋን ማጫሩ አይቀርምና ተስፋ አለ ብቻ ሳይሆን “አዲስ ምእራፍ” ማለትም ይቻላል።
ባለፉት አመታት የአገሪቱ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ይዞታ ምን እንደሚመስል ላስታወሰ፤ ከመደበኛው የመማር ማስተማር ሂደት በተቃራኒ ዜናው ሁሉ የተማሪዎች የእርስ በርስ ብሄር ተኮር ግጭት ብቻ ሆኖ እንደነበር ለተገነዘበ፤ ይህ አሁን በመንግሥትና ተቋማቱ የተወሰደውና ወደ ፊትም ይወሰዳል ተብሎ የሚጠበቀው እርምጃ በየትኛውም መመዘኛ ቢሆን ሊበረታታ የሚገባው ሆኖ ይገኛል።
በዚሁ ጉዳይ ላይ በምረቃው ስነስርአት ላይ ተገኝተን ተመራቂ የአመራር አካላትን ያነጋገርን ሲሆን፤ በተለይ ከአዲስ ዘመን ጋር ቆይታ ያደረጉት፣ በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የኢንፎርማቲክስ ትምህርት ቤት ዲንና መምህርት የሆኑት ፈጠነች መስቀሌ ሃሳባቸውን በማካፈል ቀዳሚዋ ነበሩ።
እንደ የምድብ(?) (Cohort 10) ሰልጣኟ መምህርት ፈጠነች መስቀሌ አስተያየት ስልጠናው ምንም የሚወጣለት፤ ምንም የሚጎድለው አይደለም። በጣም አስፈላጊና በየትኛውም ደረጃ ያለ አመራር ሊወስደው የሚገባ ስልጠና ነው።
እኛ ምንም እንኳን በተለያዩ መመዘኛዎች ተወዳድረን እዚህ የአመራር ቦታ ላይ የተቀመጥን ቢሆንም ከአመራር እውቀትና ክሂሎት አኳያ የወሰድነው ስልጠናም ሆነ ሌላ ነገር የለም። በመሆኑም ይህ ስልጠና ለእኛ በጣም አስፈላጊ የነበረ ስልጠና ነው የሚሉት መምህርት ፈጠነች፤ ከስልጠናው በአመራር ወቅት ብዝሀነትን እንዴት ማስተናገድ እንዳለብን፣ እንደ ምን አድርገን ልንይዘው እንደሚገባን፤ አስፈላጊ በሆነበት ወቅት ውሳኔ እንዴት መስጠት እንዳለብንና ሌሎች በርካታ ከአመራር ጋር የተያያዙ እውቀትና ክሂሎት እንደገበዩም ይናገራሉ።
ይህ ስልጠና ለሁልጊዜውም መቀጠል እንዳለበት የሚናገሩት መምህርቷ፤ ምክንያታቸውም ይህ ቦታ በየአምስት አመቱ የምንለቀውና በአዲስ ሰው የሚያዝ (የሚተካ) የኃላፊነት ቦታ ነው። እኔ ከአምስት አመት በኋላ ስለቅ የሚተካው ሰው ደግሞ አሁን ስልጠና የወሰደ ሰው አይደለም። በመሆኑም እሱም ይህ ስልጠና ሊኖረው ይገባል። ይህ ካልሆነ ሁኔታውን ሁሉ ወደ ነበረበት፣ ወደ ድሮው ነው የሚመልሰው። ይህ ደግሞ መሆን የለበትም። የአመራር ብቃቱ በዘላቂነት መቀጠል ያለበት ከሆነ አስተባባሪዎች፣ ዲፓርትመንት ኃላፊዎች ወዘተ ሁሉ ይህንን ስልጠና መውሰድ አለባቸው በማለት ያስረዳሉ።
“ስልጠናውና በስልጠናው ያገኛችሁት እውቀት በከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቻችን ውስጥ እስከ ዛሬ ሲታዩ የነበሩ ችግሮችን ይፈታል ብለው ያምናሉ?” ለሚለው የአዲስ ዘመን ጥያቄም በእርግጠኝነት እንደሚፈታው ይናገራሉ።
ሌላውና ከአዲስ ዘመን ጋር ቆይታ ያደረጉት የጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ባልደረባ ሲሆኑ ከመምህርነታቸው በተጨማሪ የአይሲቲ ዳይሬክተር ናቸው።
ዳይሬክተርና መምህሩ አቶ ጀማል አይድሪስ እንደሰጡን አስተያየት ከሆነ፤ ስልጠናው ምንም የማይወጣለት ጠቃሚና ምንግዜም መሰጠት ያለበት ስልጠና ነው። በተለይ የትምህርት ጥራትን ከማስጠበቅ፣ ግጭትን ከማስወገድና መፍታት፣ ከውሳኔ አሰጣጥ አኳያ እጅግ አስፈላጊ የሆነ ስልጠና ነው።
ይህ በሶስት ዙር የወሰድነው ስልጠና በአይነቱ ልዩ ነው። በመሆኑም ብዙ እውቀት፤ ብዙ ጥቅም፤ ከፍተኛ ግንዛቤ ነው ያገኘንበት። በተለይ በአመራር (ሊደርሺፕ) አካባቢ ላለ ሰው ጥቅሙ በርካታ ሲሆን ስራን ከማሻሻልና የተሻለ የመማር ማስተማር አካባቢን ከመፍጠር አኳያ ከፍተኛ ጥቅም አለው። ለአንድ ለተወሰነ አካል ብቻ ሳይሆን ለአጠቃላይ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብም ጥቅሙ ከፍተኛ ነው። ብዙ ነገሮችን ይቀይራል። ግጭቶችን ይፈታል። ለአሁን ብቻ ሳይሆን ለወደፊቷ አገራችን ሳይቀር በጣም ጠቃሚ የሆነ ስልጠና ነው። ከፍተኛ የሆነ የለውጥ መሳሪያ ነው። ወደ ፊትም ሊቀጥል ይገባል ሲሉም ፋይዳውን ይናገራሉ።
ዶ/ር ሰለሞን አብርሃ በእለቱ የበአሉ ማጠቃለያ (መዝጊያ) ንግግራቸው እንዳስገነዘቡት፤ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አመራሮች ያለ ምንም የአመራር ሙያ በቀጥታ ከአካዳሚው ነው የሚሰየሙት። ይህ ክፍተት ፈጥሯል። በየተቋማቱም የአመራር መጓደልን አስከትሏል። አመራሮች በየጊዜው የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመፍታት ሲቸገሩ ሁሉ ነበር። በመሆኑም አሁን በየደረጃው ላሉ አመራሮች ጊዜውና ዘርፉ የሚጠይቀውን ስልጠና መስጠት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል። ለዚህም ነው የዚህ አይነቱ ስልጠና አስፈላጊ ሆኖ የተገኘው። በተለይ በመጪው አምስት አመት ለዚህ ዘርፍ ልዩ ትኩረት የተሰጠ በመሆኑ ስልጠናውና የአመራር አካላትን የማብቃቱ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል።
ማጠቃለያ፣ እንደ ደቡብ ኮሪያ፣ ቻይና እና ሲንጋፖር የመሳሰሉ አገራት በአገራቸው ልማትን ማምጣት የቻሉት ለትምህርትና ስልጠና ልዩ ትኩረትን በመስጠታቸው መሆኑ የባለሙያዎችን ምስክርነት ያገኘ እውነት ነው። አሜሪካ በሩሲያ (በስፔስ ሳይንስ) ስትበለጥ ሮጣ ያገላበጠችውና ባስቸኳይ የከለሰችው ስርአተ ትምህርቷን እንጂ ሕገ መንግሥቷን አለመሆኑ ስለትምህርት ሲነሳ ሁሌም ሳይታለፍ የሚነገር እውነት ነው። ከዚህ አኳያ መንግሥት አሁን እያደረገ ያለው የትምህርት ጥራትን የማስጠበቅና የህግ የበላይነትን የማስከበር ተግባር አጠናክሮ ሊቀጥልበት ይገባል እንላለን። የአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮም ባለፈው ሀሙስ በዴሎፖል ሆቴል ያደረገው ግምገማዊ ውይይትም የዚሁ አካል ነውና ይበል የሚያሰኝ ነው።
በሽብር ቡድኑ የወደሙ ትምህርት ቤቶች መልሰው ይገነባሉ።
ኢትዮጵያ አሸንፋለች!!!
ግርማ መንግሥቴ አዲስ ዘመን ሰኞ ታኅሣሥ 18 ቀን 2014 ዓ.ም