ልጅነት እና ዕድገት
አርቲስት እንዬ ታከለ በቀድሞ አጠራሩ በጌምድር ክፍለ ሀገር ጎንደር ማሩ ቀመስ ደንቢያ ቆላድባ የትውልድ ሀገሯ የልጅነት ቀዬዋ ነው። እናቷ ወ/ሮ ብርጭቆ ፈንታሁን አባቷ ደግሞ አቶ ታከለ አወቀ ይባላሉ። ልጅነቷን አቀማጥሎ ፍልቅልቅና ቆንጆ አድርጎ ያሳደጋት ማሩ ቀመስ ደንቢያ ባለ ስሜት እና ደስተኛ የሆነ ልጅነቷን የዓለም ቋንቋ ለሆነው ዜማና ባህላዊ ጭፈራ አስገዛው።
የአፍላ ቁንጅናዋን ጊዜ አይን ውስጥ የምትገባ ቀለማም ፈርጥ አደረጋት። በቅፅል ስሟ “ከበሮ ጠረኛ” እስክትባል አደረሳት ። የልጅነት አበባየሽ ሆይ ይሁን የጥምቀት ታቦት ሽኘታ፣ ሰርግ ይሁን ብቻ ከበሮ በአለበት እንዬን ማጣት የማይቻል ሆነ።
የእኩዮቿ ይሁን የአጃቢዎቿ እጀባና ደስታ ውስጧ ያለውን የተዝናንቶ ስሜት በጭፈራ ሌላው ላይ ማጋባት የሰርክ ውሎዋ አደረገላት ። የእንዬ ታከለ የአፍላነት የልጅነት የትምህርት ህይወቷን በተለየ አሳመረላት፤ ከእኩዮቿ ተለይታ ሞገስ የሰጣት አቅሟ ጭፈራዋ ሆነ።
ቀጠለና የእንዬ ታከለ አፍላ ኮረዳነት እንደ ወግ ልማድ ባህሉ ዕድሜዋ አስራዎቹ ደረሰና በሁለት በሶስት ጉዳይ ተወጠረ። ጋብቻ፣ ትምህርት፣ ጭፈራ (ተሰጥዖ) የልጅነት ውሳኔ በሁሉም መንገድ ስሜት የሚጫነው ነውና ስሜቷ ደንገላሳ ያስጨፍራታል፤ የአካባቢው ባህሉና ወጉ ከቤተሰብ ጋር ተባባሮ ጫናውን አበረታባት።
በህይወቷ ላይ ሊወስን ከተነሳሳው ያለእድሜ ጋብቻ አስገዳጅ ልማድ ሸሽታ ሀገሯ እና ባህሏ ከአስታጠቃት አገረኛ ጭፈራ (ውዝዋዜ) ፍቅር ጋር ፍቅር ወድቃ አሻፈረኝ አለች። የሙሉ ጊዜ ዘፋኝነትና ጭፈራ ደግሞ በትውልድ ሀገሯና አካባቢው ተቀባይነት የሌለው ሞያ ነው፤ ለባህልና ለበዓል አጃቢነቱ ባለፈ ክብር የሚሰጠው ክዋኔ አይደለም። የእንዬ ፍላጎት ለቤተሰቡ የቤተሰቧ ፍላጎት ለእንዬ ያልተወደደ ሆነ።
ኪነት እና እንዬ ታከለ
በዚህ ጊዜ “ከቤት ዶሮ ሲታረድ ውጭ ቆቅ ይያዛል” እንዲሉ የአዲሱ አብዮት መፈንዳት እና የጊዜያዊ የወታደራዊ መንግስት የመደርጀትና የማደራጀት ፍላጎትን ተከትሎ ኪነት ይሉት ድንቅ ማሳ ለጥበብ እርሻ እየተዘጋጀ ነበር።
የጥበብ ምርቱ ያምር፣ ፍሬው ያፈራ ዘንድ መልካም ዘር ምልመላው በታላቁ የመሰንቆ ንጉስ አባባ ይርጋ ዱባለ እና ቀለመወርቅ ደበበ ሲጀመር እንዬ ታከለ የበቃ እና የነቃ ችሎታ ታየባት፤ የሚያድግ የሚፈካ አቅሟም መልማዮቿን አሳመነ።
የበኋላው የታላቁ ፋሲለደስ ኪነት አባል አደረጋት። ከተለያየ የበጌምድር ክፍለ ሀገር ከተገኙ ተመልማዮች ጋር የመላ ኢትዮጵያዊያን የባህል ጭፈራ እንዲያጠኑ ሲደረግ መሃለኛውን ወሳኝ የመድረክ ስፍራ እንዬ ታከለ ተቆጣጠረችው። የመድረኩ ዋናው መብራት ሆነች።
በሀገር ውስጥ የወቅቱ ታላላቅ የሚባሉ የኪነት መድረኮች የፋሲለደስ ኪነት ሁነኛ የመድረክ ፈርጥ መሆኗን በበርካታ ታዳሚዎች ፊት አስመሰከረች። ከዛ ወዲያማ ምኑ ቅጡ …ኪነት በመላ ሀገሪቱ እያበበች ስትሄድ ለእንዬ ታከለ እና እኩያ የኪነት አባላት የተሰጥዖቸው ምቹ ስፍራ በሚስብና በሚያጓጓ ግብዕት ተሟላ።
ሁሉም ስጦታቸውን ያለስስት በማውጣት በባለሞያ እገዛ ችሎታቸውን እያዳበሩ ብሔራዊ የኪነት መልካቸውን በሁሉም መስክ ገነቡ። ኢትዮጵያዊነትን በራሷ ቱባ ባህልና ጭፈራ ሞሸሯት። በአራቱም አቅጣጫ የተገኘውን ቋንቋ የባህል ዜማ፣ ግጥም፣ ጭፈራ፣ አለባበስ ስርዓትና ወግ በማጥናት በሁሉም መድረክ ላይ በአክብሮት ከወኑት።
ሀገረ አቀፍ የባህል አምባሰደርነታቸው ሲረጋገጥ ፊት ለፊት በድምቀት ሁሉን በሚወክል በአለላ የህብር ቀለም ከሚታዩት ውብ የመድረክ ፈርጦች የጭፈራና ውዝዋዜ አርማዎች መካከል እንዬ ታከለ “የእስክስታዋ ንግስት ” ወጣ ገባ ባልሆነ መልኩ በሁሉም የታዳሚ ልብ ውስጥ ለዘላለም ነገሰች።
ዓለም አቀፍ የመድረክ ዕድል
“ዘመን ካለ ዘመነኛም አለ” እንዲሉ እንዬን ለዘላለም ዘመነኛ የሚያደርግ ዓለምን ለማመስገን የታሰበበት የባህር ማዶ የመድረክ ዕድል ተዘጋጀ። የጉዞ ስሙ “ህዝብ ለህዝብ” ተባለ። በዓለም መድረክ ሌላ ጣዕም ሌላ ተወዳጅ የደስታ ቅመም የሚተዋወቅበትና ወዲያውም ኢትዮጵያውያንም እንደማንኛውም ዓለም የራሳቸው ስልተ ምት ያላቸው የራሳቸው የሙዚቃ መሳሪያ ያላቸው የራሳቸው ውዝዋዜ ጭፈራዎቾ አይነት እንዳለቸውና የራሳቸው አለባበስ በአጠቃላይ የደስታ ስሜትን ተጋርተው ለሌሎች በሚገባ ማጋራት የሚችሉ መሆኑን ለማሳየት ሰፊ ዕድል ያለው መሆኑን አዘጋጆቹ በመገንዘባቸው ዓለምን በዜማ በቃል እና ጭፈራ ለማመስገን ታተሩ።
ጉዞው ተሳካ ፤ የህዝብ ለህዝብ አባላት ሁሉ ከዓለም ምስጋናና አድናቆት ተቸሩ። እንዬ ታከለም እውቅናዋ ከሀገሯ ኢትዮጵያ አልፎ በማህበራዊ ሚዲያው ሳይሆን በፊት ለፊት የዓለም መድረክ ክዋኔ ፈርጥነቷን፣ ልዩ ተስጥዖዋን ፣ በአይረሴ ውዝዋዜና ጭፈራዋ ስልተምት ስምረት የታዳሚው ሁሉ አይን ላይ ተስላ በመቅረት ኢትዮጵያን አስተዋወቀች ራሷን አሳወቀች።
የአብዮትና የኪነት ውድቀት
ከደርግ መንግስትና ከአብዮቱ ማብቃት ጋር ኪነትና የኪነት ትሩፋቶች አደጋ ላይ ወደቁ። ፋሲለደስ ኪነት እና ሌሎች መሰል የኪነት ቡድኖች ራሳቸውን እና የነ እንዬን ህይወት ያለምንም ዋስትና በተኑ። ኪነትና የፈካው ህልሟ ህልም እልም ሆኑ።
የፋሲለደስ ኪነት ሌላ ዕድል
“ሳይደግስ አይጣላም “ሆነ እና የደርግ ወታደራዊ መንግስት ሲወድቅ ወደ ሀገር ከገቡት የፖለቲካ ቡድኖች መካከል በኢትዮጵያ አንድነት እና ሉአላዊነት ከደርግ ጋር ልዩነት ከሌላቸው አንዱ ኢዲዩ (የኢትዮጵያ ዲሞክራቲክ ህብረት) ነበር ።
የተበተነውን የፋሲለደስ ኪነት አባላትን፣ ታዋቂ የሆኑ ሌሎች ቡድኖችንም ሆነ የኪነት አባላትን ከየአሉበት አሰባስቦ አንድነት የባህል ቡድን በሚል በኢዲዩ ሥር እንዲሰባሰቡ በወቅቱ በኢዲዩ የማእከላዊ ኮሚቴ አባል በነበሩት አቶ አብርሃ በየነ ሰብሳቢነት አዲስ አበባ ላይ ዳግም የፋሲለደስ ኪነት ነፍስ ዘራ። ከአባላቱ መካከል የእስክስታዋ ንግስት እንዬ ታከለ አንድዋ ነበረች።
እንደገና የተሰባሰበው የኪነት ቡድን የመጀመሪያ የተሟላ የመድረክ ስራውን ሱዳን (ካርቱም) ለሚገኙ ቁጥራቸው ከሃምሳ ሺህ በላይ ለሆኑ ኢትዮጵያዊያን በተሳካ ደረጃ በማቅረብ ስራውን ጀመረ።
ቀጥሎም ወደ ሰሜን አሜሪካ ለመድረክ ሥራ አቀና። የኪነት ቡድኑ አባላት በተለያዩ ምክንያቶች እዛው አሜሪካ ኑሯቸውን ሲያደርጉ እንዬ ታከለም እዛው አሜሪካ ኑሮዋን አደረገች።,
እንየ ታከለ በዴንቨር ኮሎራዶ ስቴት ኑሮዋን ከአደረገች በኋላ በተቻለ መጠን ውስጧ ያለውን የሀገርና የባህል ፍቅሯን ለማንፀባረቅ የባህል ሬስቶራንት እና ምሽት ቤት ከፍታ ባህሏን በማስተዋወቅ ለረጅም ዓመታት ሰርታለች።
የእንዬ ታከለ ጥሪ ወደ ሀገር ቤት
የሀገሪቱ የስራ ሃላፊዎች በአሜሪካ ተገኝተው ለኢትዮጵያ ልማትና እድገት የበኩላችሁን አግዙን በማለት ለዲያስፖራው ጥሪ አቀረቡ። በጥሪው መድረክ ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ እንዬ ታከለን ያዩ የስራ ኃላፊዎች አደነጋገጥ የሚያስገርም ነበር። በሁሉም አእምሮ ውስጥ ተስላ የምትኖረው እንዪ ከሰማይ እንደወረደች ተቆጠረ። ምክንያቱም የት ትኑር የት ትግባ አብዛኛው ሰው አያውቅም ነበር።
እንዬ ታከለን በአካል የአገኟት የክልልና የፌደራል ባለስልጣናት ከታላቁ የህዳሴ ግድብ ጋር ታላቅ ቦታ በመስጠት ለግንባታው ስኬት ህዝቡ ለእርሷ ያለውን አድናቆት ፍቅርና ናፍቆት ተጠቅማ ሀገሯን ዳግም ከፍ እንድታደርግ ጥሪ አቀረቡላት።
እንዬ የሀገሯ አርማ የባህሏ አምባሳደር ናትና ድጋሚ ባገኘችው ከህዝብ ጋር የሚያገናኛትን ወርቃማ ዕድል በማሰብ አሁንም ህዝቡን ለሚጠቅምና ኑሮውን ለሚለውጥ ጉዳይ ግንባር ቀደም ሆና እአአ በ2015 ወደ ኢትዮጵያ ከ20 ዓመታት የባህር ማዶ ኑሮ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ መመለስ ችላላች።
ከበርካታ ዓመታት በኋላ ወደ ሀገሯ ስትመለስ በትንሽ በትልቁ በገጠር በከተማው በሁሉም አቅጣጫ የተደረገላት በፍቅር የታጀበ ደማቅ አቀባበል ለዘላለም በምስጋና እና በአክብሮት አብሯት እንደሚኖር በወቅቱ በተዘበራረቀ ስሜት ገልፃዋለች።
እንዬ ታከለ እውነትም የመቼም የመድረክ ፈርጥ ሆና በእስክስታ ንግስትነቷ ህዝብ ልብ ውስጥ እየኖረች መሆኑን አስባው አልማው ከምታውቀው በላይ ሆኖ ዳግም ስታገኘው ማለት የምትችለው ጠፍቶባት በእንባ እየራሰች በህዝቡ ፊት ፈጣሪዋን ደጋግማ እንድታመሰግን ተገዳለች።
የእንዬን ሥራ እስክስታዋን በቀጥታ የታደሙ የዕድሜ አቻዎቿ እና ታላላቆቿ ብቻ ሳይሆኑ ክዋኔዋ ተቀርፆ በተለያየ አገጣሚ ለማየት የቻሉ ወጣቶች ሳይቀሩ ከዚህ ክልል ከዚያ ክልል ሳይባል ያሳዩዋት ፍቅር እና አከብሮት ለሰራቸው እና ለደከመችበት የራሷ ሥራ ድጋሚ ክብር እንድትሰጥና በትውልዱ ውስጥ ገና በቅብብል እንደምትኖር ማረጋገጫ ሆኖላታል።
እንዬ በሀገር ቤት
ይህን ሰሜት የፈጠራበት የህዝብ አቀባበል ጠቅልላ ወደ ሀገሯ እንድትገባና ከሃያ ዓመታት በላይ ሥሩን ለአጣው ቅጣንባሩ ለጠፋበት የሁሉም ብሔር ባህላዊ ጭፈራ የማስተካከልና ወደ ቱባ ባህሉ ጭፈራው ለመመለስ ጊዜው አሁን ነው በሚል ቀጣዩን የባህል አምባሳደርነቷን በሚያሳይ ደረጃ ግዴታዋን ለመወጣት በትውልድ ሀገሯ ጎንደር አርቲስት እንዬ ታከለ የባህል ምሽትን ከፍታለች። በዚህም ልጆችን በየጊዜው በማደረጀትና በማሰልጠን ለአርቲስቶቹ ትክክለኛውን ሞያና የሞያ ስነ ምግባር በማላበስ ለታዳሚው የናፈቀውን ቱባውን የሁሉም የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰብ ጭፈራ እንዲቀርብ በማድረግ ከባለቤቷና ማናጄሯ አቶ አብርሃ በየነ ጋር ለማሳካት ችላለች።
ጥንዶቹ ሁለት ልጆች የወለዱ ሲሆን፣ ስማቸውም ነብዩ አብርሀ እና አደይአበባ አብርሀ ይባላሉ። የአደይ አበባ ስም የወጣው እንዬ ታላቅ ብቃት አሳይታ የዝና ማማ ላይ ከወጣችበት የህዝብ ለህዝብ ጉዞ ታሪክ ጋር በተገናኘ ነው።
አሁን ላይ እንዬ ከስራ ውጭ ብዙም ከቤት የማትወጣ ሲሆን፣ የእረፍት ጊዜዋንም በአብዛኛው ከባለቤቷ አቶ አብርሀ እና ከልጆቿ ጋር ሻይ ቡና በማለት ነው የምታሳልፈው። ከዚህም ባለፈ እና ተወዛዋዥነቷ ሰውነቷ ከእንቅስቃሴ መለየት አይወድምና ጂምም ታዘወትራለች።
በመጨረሻም መልእክት ካላት እንድታስተላልፍ ጋበዝናት። ሁሉም ነገር የሚኖረው ሀገር ስትኖር ነውና ለሀገሬ ሰላም እመኛለሁ አለችን። በእርግጥም ከዚህ የሚልቅ መልእክት የለምና እኛም በዚሁ ተሰናበትናት። አብዛኛውን መረጃ ያገኘነው የአርአያ ሰው ሽልማት በተሰኘው የሽልማት ስነስርአት ላይ ከቀረበው መረጃ ነው።
አቤል ገ/ኪዳን
አዲስ ዘመን ህዳር 12 ቀን 2014 ዓ.ም