መስከረም ከትርጉሙ ጀምሮ ታሪኩ ብዙ ነው። ይሁን እንጂ የእኛ ትኩረት ወቅቱን ታሳቢ ባደረገ መልኩ አንድ ጉዳይ ሲሆን እሱም ከትምህርት ቤቶች መከፈት ጋር በተያያዘ የተደረገውን ዝግጅት የሚመለከት ይሆናል።
መስከረም በኢትዮጵያዊያን ዘንድ በጉጉት የሚጠበቅ ቀዳሚ ወር ሲሆን፤ በተለይ በተማሪዎች ዘንድ “በናፍቆት” የሚለው ከሚገልፀው በላይ የሚጠበቅ ነው። በመሆኑም በዚህ ጽሑፍ የትምህርት ቤቶችን መከፈት ከዝግጅታቸው ጋር አያይዘን ማንሳት ፈለግን፡፡ ምክንያቱም አሁን ያለንበት ወቅት ይዞብን ከመጣው አሳሳቢ ችግር አኳያ ዓመቱ ከሌሎች የተለየና ተገቢ ጥንቃቄን የሚፈልግ በመሆኑ ነው።
እንደሚታወቀው ዘመኑ ይዞት የመጣውና ከፊታችን የተጋረጠው ከባድ አደጋ ኮቪድ-19 (ኮሮና ቫይረስ) ነው። ይህ ገዳይ ቫይረስ ማንንም የማይምርና ለማንም የማይቦዝን ይሁን እንጂ በተለይ ትምህርት ቤቶችን በመሳሰሉ ሰዎች ተሰባስበው በሚገኙበት ቦታ ላይ ከሌሎች ስፍራዎች በተለየ ሁኔታ ልዩ ዝግጅትንና ክትትልን ይፈልጋሉ። በመሆኑ በአዲስ አበባ በሚገኙ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች ተዘዋውረን ያለውን አጠቃላይ ሁኔታ የተመለከትን ሲሆን የሚመለከታቸውም አስተያየታቸውን ይሰጡን ዘንድ አነጋግረናቸዋል።
በመጀመሪያ ያቀናነው 1ሺህ 300 ተማሪዎችን ወደሚያሰተናግደው አንጋፋው ምኒልክ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሲሆን፤ ተቀብለው ያነጋገሩንም የትምህርት ቤቱ ምክትል ርዕሰ መምህር ኤፍሬም ምትኩ ናቸው፡፡ ያደረጉትን ዝግጅትና የተማሪዎችን አቀባበል በተመለከተም የሚከተለውን ብለውናል።
ኮቪድን በተመለከተ በሽታው ተከሰተ ከተባለበት ወቅት ጀምሮ ከመዘጋጀትና አስፈላጊውን የመከላከል ስራ ሳንሰራ ቀርተን አናውቅም። ከጤና ባለሙያዎች የሚተላለፈውን መልእክት መሰረት በማድረግ የኮቪድ ፕሮቶኮልን በጠበቀ መልኩ የመከላከል ስራውን ስንሰራ ነው የቆየነው። ዘንድሮም ተጠናክሮ የቀጠለው ይሄው አሰራር ሲሆን፤ በቂ ዝግጅትም ተደርጎበታል፡፡
ኮቪድን ከመከላከል አኳያ ከጤና ሚኒስቴር እና ከትምህርት ሚኒስቴር (ቢሮ) ደብዳቤዎች ይመጣሉ። እኛ ሁሉንም እያጣጣምን በመስራት ላይእንገኛለንም፡፡ ዝግጅታችንም ቢሆን የሚጀምረው ከመሰረታዊ የመከላከያ ቁሶች አቅርቦት ነው፡፡ ግብረ ሰናይ ድርጅቶችን በማነጋገር ከበጀት ውጪ በሆነ መልኩ ለማስጀመሪያ የሚሆን የፊት ማስክ፣ ሳኒየታይዘር፣ ሳሙና ወዘተ አዘጋጅተናል። ሲያልቅ ደግሞ ለጋሽ ድርጅቶችን በመጠየቅ እንዲሰጡን እናደርጋለን። ካልሆነም ከበጀት ወጪ አድርገን የምንገዛ ይሆናል፡፡
ከንፅህና መጠበቅ ጋር በየተያያዘ በሁለቱም በሮች ተማሪዎች እየታጠቡ እንዲገቡ ለእጅ መታጠቢያ ዘመናዊ ባለ 25 ጡት ቧንቧ አስገብተናል። ለመምህራንና ሰራተኞችም እንደዚሁ ስድስት ጡቶች ያሉት ቧንቧ አስገብተናል።
ክትባትን በተመለከተ መምህራን፣ የአስተዳደር አካላትና ሰራተኞች ፀረ-ኮቪድ ክትባት እንዲወስዱ ከመንግስት በወረደው መመሪያ መሰረት ከአጠቃላይ መምህራን 25 በመቶ የሚሆኑት የመጀመሪያውን ዙር ክትባት ወስደዋል። ሌሎችም በየአካባቢያቸው እየወሰዱ ነው። ክትባቱን እየወሰዱ ሰርተፊኬት እያመጡም ያሉ መምህራን አሉ።
ተማሪዎችን በተመለከተ ትምህርት ቤት ጥቅምት 2 ቀን ይከፈታል። እኛ ደግሞ ጥቅምት አንድ ከተማሪዎች ጋር አጠቃላይ ውይይት አለን። ለተማሪዎች ገለፃ ይደረጋል። በዚህ ገለፃ ውስጥ ደግሞ ልዩ ትኩረት ከሚሰጣቸው መካከል አንዱ ይሄው ኮቪድ-19ን የመከላከሉ ጉዳይ ነውና ዝግጅታችን ይህንን ይመስላል።
ዘንድሮ የመማር ማስተማሩ መርሃግብር ወደ ነበረበት ቅድመ ኮቪድ ሁኔታው ይመለሳል ለሚለው እስካሁን (ባለፈው ረቡዕ ነው ያነጋገርናቸው) ቁርጥ ያለ መመሪያ (ደብዳቤ) አልደረሰንም። በእኛ በኩል ሁለቱም አይነት መመሪያ ቢመጣ በሁለቱም (በቅድመ ኮቪድ የነበረው የመማር ማስተማር ሁኔታና ድህረ ኮቪድ በነበረው አይነት አሰራር) ለመስራት በሚገባ ተዘጋጅተናል። መጠባበቂያ (አማራጭ) እቅድ አዘጋጅተናል።
ድህረ ኮቪድ የሚባለው ተማሪዎች እያሰለሱ ትምህርት ቤት በመምጣት ትምህርታቸውን የሚከታተሉበት፣ በክፍል 24፣ በአንድ ዴስክ አንድ ተማሪ የሚቀመጥበት ሁኔታ ነው። ወደ ቀድሞው ሲባል ደግሞ ሙሉ ቀን፣ ሁሉም ተማሪዎች የሚገኙበት ማለት ነውና እኛ በሁለቱም ዝግጅታችን ተጠናቋል።
ባለፈው ዓመት የመማሪያ መፃህፍትን ለመጨረስ ከፍተኛ ችግር ሆኖብን ከርሟል፡፡ መፅሀፉን መጨረስ ደግሞ የግድ ነው። በመሆኑም አምና ያጋጠመን ችግር ዘንድሮ ይሻሻላል ብለን እንጠብቃለን። ከበላይ እየተጠባበቅን ያለነውም መመሪያ ወይም ደብዳቤ ከዚሁ አኳያ ይሆናል ብለን እናስባለን፡፡
ተማሪዎችን በተመለከተ ማድረግ ያለባቸው መሰረታዊ ነገር አለ። እያንዳንዱ ተማሪ የጤና ባለሙያዎችን ምክር መስማት አለበት። ባለፈው ዓመት የነበረው ችግር ክፍል ውስጥ በወንበር አንድ ተማሪ እያስቀመጥን እያለ እነሱ ሲወጡ ግን ጥብቅብቅ ብለው ይገኛሉ። ከዚህ አይነት ተግባር መራቅ አለባቸው። የተማሪዎች እገዛ የሌለበት ሥራ የትምህርት ቤቱን ዝግጅት ጎዶሎ ያደርገዋል፡፡ ስለሆነም ተማሪዎች ይህንን ሊያስቡ ይገባል፡፡
ቀጣዩ ያየነው ትምህርት ቤት ከምኒልክ 2ኛ ደረጃ ብዙም ወደአራቀውና አምስት ኪሎ ወደሚገኘው ራዲካል አካዳሚ (የግል) ትምህርት ቤት ሲሆን፤ እንደደረስንም ተቀብለው ያነጋገሩን የራዲካል ትምህርት ቤቶች ጀነራል ማኔጂንግ ዳይሬክተር ወይዘሮ አዜብ ብርሃኔ ናቸው። እሳቸውንም በዚሁ በተለይ በኮቪድ-19 መከላከል ዙሪያ የተደረገውን ዝግጅት እንደሚከተለው አብራርተውልናል።
ራዲካል አካዳሚ ብዙ ቅርንጫፎች አሉት። ይሄኛው ከመዋዕለ ሕጻናት እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ ትምህርት ይሰጥበታል። በትምህርት ሚኒስቴር በተወሰነው መሰረት ዘንድሮ አጠቃላይ እስከ 2ሺህ ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር ይጠብቃል።
ኮቪድን በተመለከተ ችግሩ ዓለም አቀፍ ነው። እኛ ጋር ደግሞ ከ2012 ጀምሮ የተከሰተ ስለሆነ በቂ ልምድ ወስደናል። መደረግ ያለባቸውን ከሌለባቸው ለይተናል። መወሰድ ያለባቸው እርምጃዎች ስለሚታወቁ በዛው መሰረት ተዘጋጅተናል።
ምንም እንኳን በክረምቱ ምክንያት ትምህርት ቤት ዝግ ሆኖ ቢቆይም ተማሪዎቻችን ከኮቪድ እራሳቸውን እንዲጠብቁ በማድረግ በኩል የመገናኛ ዘርፎችን ሁሉ (ቴሌግራምን ጨምሮ ያሉ ድረ ገጾችን) በመጠቀም ከወላጆች ጋር ያልተቋረጠ ግንኙነትና ክትትል አለን። ባዘጋጀነው የነባር ተማሪዎች ወላጆች “አድሬስ ቡክ” ላይ የተመዘገበ የሁሉም ተማሪዎቻችን አድራሻ ስላለን በዛ አማካኝነት ግንኙነት ስናደርግ ቆይተናል። በማንኛውም ትምህርትን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ እናማክራቸዋለን። ከእነዚህ ጉዳዮች መካከል ደግሞ አንዱ ከኮቪድ እንዴት አድርገው እራሳቸውንና የአካባቢያቸውን ማህበረሰብ መጠበቅ እንዳለባቸው የምንመካከርበት ነው፡፡ በዚሁ መሰረት ክረምቱን ስንሰራ አሳልፈናል።
ከ2012 እና 2013 ዓ.ም የወሰድነው ልምድ አለ። ተማሪዎች እርስ በእርስ ከመነካካት እንዲርቁና እራሳቸውን ከበሽታው እንዲጠብቁ ማድረግ አንዱ ተግባር ነው። በኮቪድ ፕሮቶኮል መሰረት መስራት የትምህርት ቤታችን መርህ ነው። በእሱ መሰረት እየሰራን ነው።
አሁን ትምህርት ቤት መክፈቻን በተመለከተ ሙሉ ቀን ይሆናል አይሆንም የሚለው ጉዳይ በግልፅ የታወቀ ነገር የለም። የደረሰን መመሪያም ሆነ ደብዳቤ የለም (ባለፈው ማክሰኞ ነው ያናገርናቸው)። ምንም ሆነ ምንም ግን ተማሪዎቻችንን ከኮቪድ ለመከላከል አስፈላጊውን ዝግጅት ሁሉ አድርገናል።
ከአካባቢያችን ካሉ የጤና ተቋማት ጋር የቅርብ ግንኙነት አለን። በዚሁ ግንኙነታችን አማካኝነትም ስለ ኮቪድ-19 አስፈላጊውን መረጃ እናገኛለን። በመረጃው መሰረትም እንሰራለን። የትምህርት ቤቱን ማህበረሰብ ሰብስበው ሁሉ አወያይተዋል። ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ ተሰርቷል። መምህራን መከተብ እንዳለባቸው ግንዛቤ ተይዟል፤ የተወሰኑና የመከተብ እድሉ በቅርብ ያላቸው መምህራንም እየተከተቡ ሰርተፊኬት አምጥተዋል። ሌሎች መምህራንም እንዲከተቡ እየተደረገ ነው። በመሆኑም አብዛኞቹ መምህራኖቻችን ክትባቱን እየወሰዱ ይገኛሉ።
ለተማሪዎችና ለአጠቃላይ የትምህርት ቤቱ ማህበረሰብ በሚሉ ኮቪድን ይከላከላሉ ተብለው በባለሙያ የተዘረዘሩትን በሙሉ አሟልተን እየጠበቅን ነው። የንፅህና መስጫ ቁሶች ገብተዋል። ማስክ፣ ሳኒታይዘር ወዘተ ተገዝቷል። በተለይ ትምህርት ቤቶች ኮቪድን ከመከላከል አኳያ ከፍተኛ ሀላፊነት አለባቸው። ከዚሁ ሀላፊነታቸው አኳያ መዘጋጀትና የመከላከሉን ስራ መስራት ይጠበቅባቸዋልም፡፡ በሁሉም ትምህርት ቤቶች የኮቪድ ፕሮቶኮል በተከበረ መልኩ ቢሰራ ጥሩ ነው የሚል አስተያየት አለኝ፡፡
ለተመሳሳይ ቅኝት ቀጥለን ያመራነው ከመሀል ከተማ በስተምስራቅ፣ ላንቻ አካባቢ ወደሚገኘው ሌላ የግል ትምህርት ቤት ነው። ትምህርት ቤቱ “ሶሊያና አካዳሚ” ይባላል፡፡ በሳይክል የተከፋፈለ ነው፡፡ ከመዋዕለ ሕጻናት እስከ ስምንተኛ ክፍል ያቀፈ ሲሆን፤ በአዲሱ ዓመት የትምህርት ቤቱ አከፋፈትና ኮቪድ-19ን ከመከላከል አኳያ ተቋሙ ያደረገውን ዝግጅት በተመለከተ ማብራሪያ እንዲሰጡን የትምህርት ቤቱን ርእሰ መምህር ዶክተር ጌታሁን ክንፉን አግኝተን አነጋገርናቸዋል፡፡ የሚከተለውንም ብለውናል፡፡
በእኛ በኩል አስፈላጊውን ዝግጅት አድርገናል። ከዚህ በፊት የነበረውን ዝግጅታችንን በተጠናከረ መልኩ ቀጥለናልም። ኮቪድ-19ን ከመከላከል አኳያ መመሪያውን ሙሉ ለሙሉ መሰረት ባደረገ መልኩ ተዘጋጅተን ተማሪዎቻችንን እየጠበቅን ነው።
ዘንድሮ ወደ ነበረበት ቅድመ ኮቪድ የመማር ማስተማር ሁኔታ ይመለሳል የሚል አለ። ከዚህ አኳያም ቢሆን የእኛ ዝግጅት የተሟላ ነው። ለተማሪዎቻችን በወንበር አንድ ተማሪ ተቀምጦ እንዲማር በሚለው ነው የተዘጋጀነው።
ክትባትን በተመለከተም ሁሉም ሰው ስለ ክትባቱ ግንዛቤ እንዲኖረው የማድረግ ስራ ተሰርቷል። በመሆኑም ሁሉም የትምህርት ቤቱ መምህራንና ሰራተኞች ክትባቱን ለመውሰድ ዝግጁ ናቸው። ክትባቱን የሚሰጡት የህክምና ባለሙያዎችም በየትምህርት ቤቱ እየሰጡ ነው። አሁን እየሰጡ ያሉበትን ተቋም ሲጨርሱ ቀጥሎ ተራው የእኛ ነው።
ከንፅህናና መከላከያ ቁሶች ጋር በተያያዘ ምንም አይነት ችግር የለም። ሁሉም ዝግጁ ሆኗል። ተማሪዎችም በወላጆቻቸው በኩል እንዲያውቁት ተደርጓል። በመሆኑም እነሱም አስፈላጊውን ሁሉ አድርገው እንደሚመጡ ተስፋ ይደረጋል። እኛም እያየን ነው የምናስገባው። በመሆኑም የተለየ ችግር ያጋጥመናል ብለን አናስብም።
ማጠቃለያ
በአጠቃላይ የዘንድሮው የትምህርት ዘመን የመማር ማስተማር ተግባር ሊጀመር ቀናት ናቸው የቀሩት። ሁሉም በተለይም ተማሪዎች በጉጉት የሚጠብቁት ከጓደኞቻቸው ጋር የመገናኘት ሁኔታም እንደዛው። በመሆኑም ከላይ በተመለከትናቸው ትምህርት ቤት አመራሮች እንደተብራራው ኮቪድ-19ን ከመከላከል አኳያ አስፈላጊው ዝግጅት ሁሉ ተደርጓል። በሌሎችም እንደዛው ነው ተብሎም ይታሰባል።
ተማሪዎች ይህ የየትምህርት ቤቶቻቸው ዝግጅቶች የተሟሉ እንዲሆኑ የእነሱም ጥረት ያስፈልጋልና መመሪያዎችን ተግባራዊ በማድረግ፤ አላስፈላጊ መጠጋጋትን በማስወገድ ኮቪድን በጋራ የመከላከሉ ተግባር አጋዥ በመሆን እራሳቸውን፣ ጓደኞቻቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ከቫይረሱ እንዲከላከሉ እናሳስባለን። መልካም የትምህርት ዘመን!!!
ግርማ መንግሥቴ
አዲስ ዘመን መስከረም 17 ቀን 2014 ዓ.ም