ተስፋ ማህበራዊና ልማት አቀፍ ማህበር በአዲስ አበባ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ አራት ወረዳዎች በተመሳሳይ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ አራት ወረዳዎች በድምሩ ስምንት ወረዳዎች ላይ አረጋውያንን እና ህፃናትን እየደገፈ ይገኛል። በኦሮሚያ ቡራዩ፤ ወለጋ መስመር ደን ወረዳ እንዲሁም በአማራ ክልል ደብረ ማርቆስ፤ ደጀን ብቸናና ሞጣ ቢሮ ከፍቶ እየሰራ ይገኛሉ። በዚህም ከአስራ አምስት ሺህ በላይ ህጻናትን፤ ከሶስት ሺህ በላይ አረጋውያንንና ከስምንት ሺህ በላይ ህጻናት አሳዳጊዎችን በመለየት የተለያዩ ድጋፎች በመስጠት ላይ ይገኛል። ለመሆኑ ማህበሩ ከየት ተነስቶ የት ደረሰ ስንል የማህበሩ ስራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት መለሰ አነጋግረን የሚከተለውን ይዘን ቀርበናል።
ተስፋ ማህበራዊና ልማት አቀፍ ማህበር የተመሰረተው በ1993 ዓ.ም ነው። የተመሰረተውም ኮልፌ አጣና ተራ አካባቢ ይኖሩ በነበሩ ወጣቶች ነው። እነዚህ ወጣቶች በ1993 ዓ.ም ማህበሩን በህጋዊ መንገድ እንደ ተቋም እንዲመሰረት ከማድረጋቸው በፊት ሃያ ሆነው በመሰባሰብና «ኮልፌ ከልጅነት እስከ እውቀት አብሮ አደግ የወጣቶች የመረዳጃ እድር» መስርተው ኮልፌ አካባቢ ክበብ እየሰሩ በአካባቢያቸው ለነበሩ ለሚያውቋቸው አዛውንቶች ድጋፍ ያደርጉ ነበር።
አካባቢው የውትድርና ማሰልጠኛ የነበረበትና ለታጠቅ ጦር ሰፈርም ቅርብ የነበር በመሆኑ አብዛኛው የአካባቢው ነዋሪ ህይወት ከውትድርናው ጋር የተቆራኘ ነበር። እናም በ1983 የመንግስት ለውጥ ሲመጣ ብዙ መስዋእትነት የከፈሉ በርከት ያሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ያለ ስራ በመቅረታቸው በአካባቢው በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚኖረው ማህበረሰብ ቁጥር ከፍተኛ ነበር። በዚህም የተነሳ አንዳንድ አረጋውያን በአስርና ሃያ አምስት ሳንቲም የጀመሩትን እድር አምስትና አስር ብር ማዋጣት እየተሳናቸው ከእድሩ እየተሰናበቱ በልመና የሚቀበሩም ነበሩ። እነዚህ በወር አስርና አምስት ብር መክፈል አስቸጋሪ የሆነባቸው ሰዎች የቤት ውስጥ ኑሯቸው ምን ያህል ከባድ እንደሚሆን በመረዳት ነበር ወጣቶቹ የበጎ አድራጎት ስራቸውን የጀመሩት።
ስራውን ከጀመሩት በኋላ ደግሞ አንዳንዶቹ ጎረቤት በይሉኝታ ምግብ አቅርቦላቸው እየሄደ እነሱ መብላት ስለማይችሉ አጠገባቸው እያዩት ይሻግት ነበር። ይህ ገጠመኝ ሁሉንም የማህበሩን አባላት የረበሸ ሲሆን ዳዊት በዚህ ወቅት በልጅነቱ በለጋስነታቸው ሳይቀር የሚያውቃቸው አዛውንቶችን የአልጋ ቁራኛ ሆነው ሲያይ በተፈጠረበት ጭንቀት ጸበል እስከ መግባት ደርሶ ነበር። በወቅቱ እነሱም ከዛው አካባቢ ከድሃው ማህበረሰብ የተገኙ በመሆናቸውና አረጋውያኑ የሚያስፈልጋቸውን ያህል በራሳቸው አቅም መርዳት የማይችሉ በመሆናቸው ለድጋፋቸው መነሻ ያደረጉት በአካባቢያቸው ያሉ ራሳቸው አረጋውያኑ የመሰረቷቸውን እድሮች ነበር።
በዚህም መሰረት በቅድሚያ እድሮች ስራቸውን ባላቸው አቅም ከቀብር አስፈጻሚነት በቁም ወደ መታደግ እንዲቀይሩ ሶስት እድሮችን ላይ በመለየት ማስተማሩን ይጀምራሉ። የእነዚህን እድር መሪዎች በማነጋገርም ወጣቶቹ «ኮልፌ ከልጅነት እስከ እውቀት አብሮ አደግ የወጣቶች የመረዳጃ እድር» በሚል ያቋቋሙትንም ማህበር በመጨመር ድጋፍ መስጠቱን ይጀምሩታል። ህጋዊ ፈቃዱንም በ1994 ዓ.ም ያገኝና ስራውን አጠናክሮ ይቀጥላል።
ድጋፉ ይደረግ የነበረው እዛው አካባቢ በመሆኑ አብዛኞቹ ተደጋፊዎች በስም ብቻ ሳይሆን ሙሉ ታሪካቸውም የሚታወቁ ነበሩ። «ከጥቂት ዓመታት በፊት ሆያ ሆዩ ጨፍረን እጃቸውን ዘርግተው ሳንቲም ዳቦ ይሰጡን የነበሩ አረጋውያን ዛሬ የእኛን እጅ ሲጠብቁ ሁለት ስሜት ይፈጥርብን ነበር» የሚለው ዳዊት። አንደኛው የእነሱ በተለይ የአንዳንዶቹ በጣም በሚያሳዝን ሁኔታ የአልጋ ቁራኛ ሆነው ማየት የሚፈጥረው የሚረብሽ ስሜት ሲሆን፤ ሌላው ሁለተኛው ደግሞ እኛ ደርሰንላችኋል ስንላቸው ከእነሱ ላይ የሚነበበው ደስታ የሚፈጥርብን ሀሴት ነው ይላል።
ይህም ሆኖ ዳዊት ሁሌም በአንድ ነገር ደስተኛ ነው። በመንግስትና በህብረተሰቡ ድጋፍ እስካሁን የሚፈልጉትን ባያሟላላቸውም የሚሰጣቸው ነገር ግን አጥቶ አያውቅም። ከሰፈሩ ወጣት ጀምሮ በበዓሉም ሆነ ባዘቦቱ ከጎኑ የሚቆምለት አጥቶ አያውቅም። መልካም ስራ የክፉ ቀን ስንቅ ናት የሚለው ዳዊት ሁላችንም የትውልድ ባለእዳዎች ነን በአቅማችን በየአካባቢያችን ያሉትን መደገፍ አለብን። ይህን የምናደርገው ለራሳችን ብለን ነው። ነገ የማንኛችንም እጣ ፈንታ በፈጣሪ እጅ ነች ምን እንደምንሆን አናውቅም ይላል።
ወቅቱ የኤች አይ ቪ ስርጭት የተስፋፋበት በመሆኑ አብዛኞቹ አረጋውያን ደግሞ የልጅ ልጆቻቸውን እየለመኑ የሚያሳድጉም ነበሩ። እናም በ1994 ዓ.ም የፋሲካ በዓልን መነሻ በማድረግ ለሰላሳ ህጻናትና ለሰባ አረጋውያን እዛው ባሉበት ድጋፍ በማድረግ ማህበሩ ቋሚ ስራውን ሀ ብሎ ለመጀመር በቅቷል። ስራውን ሲጀምርም ጧሪ ቀባሪ ያጡ፤ ወላጅ ያጡና ለችግር የተጋለጡ ህጻናትን እንዲሁም ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩ ወገኖችን መደገፍን አላማው አድርጎ ነበር። ለዚህ ደግሞ ተስማሚ የሆኑት እድሮች ለአባላቶቻቻው ነግረው እያንዳንዱ ሰው በወር ሁለት ብር ተጨማሪ እንዲከፍል አደረጉ። ዋናው አላማም መመሪያ ቃሉም «ከቀብር ባሻገር» የሚል ነበር። በወር አንድ ሰው ሃያ አራት ብር ማግኘት ለተስፈኞቹ ወጣቶች ብዙ ትርጉም ነበረው። ማህበሩን የእድር አባል በመሆን በቅርብ ሲከታተሉ የነበሩት ሰዎች የደርግ ሰራዊት አባላት ስለነበሩ በወቅቱ በመንግስትም በኩል ደርግ ኢሠፓ በሚል በጥሩ እንዳይታዩ አድርጓቸው ነበር።
በወቅቱ የኤች.አይ.ቪ ስርጭቱ ከፍተኛ ስለነበር የዓለም የምግብ ፕሮግራምና ሄልፕ አች. ኢንተርናሽናል የሚባል ድርጅት ለቫይረሱ ተጠቂዎችና ለህጻናት በሚል የምግብ ድጋፍ ያደርግ ነበር። ነገሩን ሲያስተውሉት
አንድ አጋር አልያም በጎ አድራጊ ሲመጣ አቅሙ በፈቀደ ለተወሰነ ጊዜ ድጋፍ አድርጎ ይሄዳል። ሌላ ይመጣል፤ ሌላውም እንዲሁ አድርጎ ይሄዳል። ታዲያ እስከመቼ ተጠብቆ የሚል ሀሳብ ፈጠረባቸው። እያደረጉት ያለውም ድጋፍ በማህበረሰቡ በኩል ያለውን የጠባቂነት መንፈስ እያሳደገው መጣ። እናም የያዙት መንገድ መስተካካል እንዳለበት ተገነዘቡ። እስከ 1996 ድረስ በዚህ ሁኔታ የቀጠሉ ቢሆንም አንዲት አጋጣሚ ደግሞ አቅጣጫቸውን መቀየር እንዳለባቸው ታስተምራቸዋለች።
አንድ ቀን አንዲት እናት ልጇን እንዲመከርላት ወደ ዳዊት ታመጣዋለች። እናም እባካህ ዳዊት አልታዘዝ አለኝ፤ አስቸገረኝ፤ አንተን ይሰማሀልና ምከርልኝ ትለዋለች። ዳዊት ልጁን ለመገሰጽ ለምን እንደዚህ እንደሚያደርግ ሲጠይቀው። ወጣቱ «ዴቭ እሷ ዝም ብላ ነው የምትጨቀጭቀኝ፤ የምታበሉኝ እናንተ፤ ደብተር እስኪርብቶ ልብስ የምትገዙልኝ እናንተ፤ ምንም ሳታደርግልኝ በገባሁ በወጣሁ ቁጥር ትጨቀጭቀኛለች» ይለዋል። ይህን ጊዜ ዳዊት ይደነግጣል። ምን እየሰራን ነው? እናትና ልጅ እያጣላን እያቀያየምን ነው ማለት ነው? የሚል ነገር ይፈጠርበታል። እናም ቢያንስ ምግቡ በቤተሰብ ትብብርም መዳረስ እንዳለበት ይወስናሉ።
መስራት እየቻሉ በገንዘብ እጥረት ለተወሰኑት በስራቸው የብድርና ቁጠባ ተቋም በማቋቋም በእድሮች ዋስነት በአራት በመቶ ወለድ ስልጠና በመስጠት ማሰራት ጀመረ። ይህን የሚያደርገው ተደጋፊዎቹ በሚፈልጉት መልኩ ብቻ ሲሆን ተስፋ የሚያደርገው ገንዘቡ ለሌላ እንዳይውል የሚፈልጉትን በአይነት ማቅረብና ቁጠባ እንዲጀምሩ ማብቃት ብቻ ነው። ይህ ሲሆን ልጆች ላላቸው በመንግስት ትምህርት ቤት የሚያስፈልገውን ወጪ አሟልቶ ማስተማር የተስፋ ሃላፊነት ነበር። ከቤተሰቡ የሚጠበቀው ምግቡን ማሟላት ብቻ ነበር።
አረጋውያኑም ከሚቀርብላቸው ምግብ ባለፈ የሚጠብቁት ነገር ነበራቸው። በአንድ ወቅት ሰማኒያ አምስት ብር በማውጣት ቡናና ዳቦ ይዘውላቸው የሄዱት እናት በተለይ በዓል ሲሆን ዳቦ ቆርሰው፣ ሰው ጠርተው መብላት ብቻ ሳይሆን እንደቀደመ ኑሯቸው ብሉ ብለው መጋበዝም እንደሚፈልጉና ይህንንም ፍላጎታቸውን እንዳሟሉላቸው በደስታ ይነግሯቸዋል። ከዚያም ጊዜ አንስተው በአረጋውያኑ ቁጥር ልክ በየዓመት በዓሉ ለሁሉም ባሉበት የሚያስፈልጋቸው ከተሟላ በኋላ አንዳንድ ድፎ ዳቦ ይዘው እንዲሄዱ ማድረግ ይጀምራሉ። ይህ የሚደረገው ደግሞ እያንዳንዱ በጎ አድራጊ ኢትዮጵያዊ ቃል እየገባ የሚያመጣው ነው።
አንዳንዶቹ ሰዎች በርካታ ችግር ያለባቸው ሆነው የአካባቢው ነዋሪ አለፍም ሲል ልጆቻቸው እንዳያውቁ የሚፈልጉ ስለነበሩ እነዚህንም በስውር ማስተናገድ ለእነዳዊት ሌላው ተግዳሮት ነበር። ዳዊት ዛሬ የስኳር ህመም የገጠመው ሲሆን አረጋውያኑን ከሚከታተሉት መካከል የእሱንም ጤንነት የሚንከባከቡ ዶክተሮች አሉ።
ከዚህ በተጨማሪ በአዲስ አበባ ብቻ ባሉ አንድ መቶ በጎ ፈቃደኞች የባሰ ችግር ያለባቸውን አረጋውያን በየቤታቸው እየሄዱ ይንከባከባሉ። እንክብካቤው አካላዊ ብቻ ሳይሆን ያለባቸውን የስነ ልቦና ጉዳት የሚጠግኑም ናቸው። ተስፋ «አንድም ህጻን፣ አንድም አረጋዊ ወደ ጎዳና እንዳይወጣ የበኩላችንን እንወጣ» የሚል መርህ ይዞ የሚንቀሳቀስ በመሆኑ፤ ቤት የፈረሰባቸውን፣ ቤት ያድሳል። ከፍራሽ አንሶላ ጀምሮ የጎደለባቸው ካሉ ያሟላል። በዓልንም ከአርቲስቶችና በጎ ፈቃደኞች ጋር በመሆን አረጋዊያኑ ባሉበት እንዲያከብሩ እያስደረገ ይገኛል።
የኮሮና መከሰት ትልቅ ተግዳሮት የፈጠረ ቢሆንም በየወሩ ይከፈላቸው የነበረውን አምስት መቶ አሳጥቷቸዋል። በምግብና በንጽህና መጠበቂያ እንዲሁም በጤና አገልግሎት በኩል ህብረተሰቡ በጣም ይሳተፍ ስለነበር የጎደለ ነገር አልነበረም። በተለይ ዘይት፣ ፓስታ፣ መኮሮኒ ጠፍቶ አያውቅም፤ ይህም ሆኖ የተወሰኑትን አረጋውያን ኮሮና ወደማይቀርበት ወስዷቸዋል። ጤና ሚኒስቴርም የኮሮና ምርመራም ሆነ ክትባት ሁለቱንም ዙር ባሉበት ሰጥቶላቸዋል።
ከጤና ተቋማትም ጋር ጠንካራ ግንኙነት የተፈጠረ በመሆኑ ከኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር አረጋውያኑ የኮሮና ምርምራና ክትባት ባሉበት እንዲያገኙ ተደርጓል። ከጳውሎስ ሆስፒታል ጋር በመነጋገር ዘወትር ቅዳሜ በተንቀሳቃሽ ክሊኒክ ሀኪሞች ያሉበት ድረስ እየመጡ ለአረጋውያኑ እንክብካቤ ያደርጋሉ። በዚህም በተለይ የስኳር የደም ምርመራና ህክምናና ድጋፍ ይደረጋል። እለት በእለት የሚያመጡትን ለውጥ እድሮች ሲገነዘቡት ቁጥራቸው እየጨመረ መጥቶ በአሁኑ ወቅት ስልሳ ስምንት ደርሷል። ዛሬ ማህበሩ የራሱ ህጋዊ ፈቃድ ያለው ቢሆንም የማህበሩ ጠቅላላ ጉባኤ አባላትና መሪዎችም የእነዚሁ እድሮች ሃላፊዎች ናቸው።
ለቀጣይም ማህበሩ ባለ አራት ወለል የተለያዩ አገልግሎቶች የሚሰጥ ህንጻ ለማሰራት አስፈላጊውን ዝግጅት አድርጎ የተቀመጠ ቢሆንም የቦታ ጉዳይ ግን እንቅፋት ሆኖበት ይገኛል። የህንጻው ግንባታ ቀዳሚ አላማ ዘላቂ ከማንም በማይጠበቅ እርዳታ ተደጋፊዎቹን ለመታደግ የገቢ ማስገኛ በመፍጠር በዘላቂነት ለመስራት ዳቦ ቤትና ሌሎች ነገሮችንም ለመስራት ነበር። ለዚህም ለክፍለ ከተማው የቀበሌና ሌሎች የመንግስት መገልገያ የነበሩ ነገር ግን የተለቀቁትን በመለየት የቦታ ጥያቄ አቅርበውበት የነበረ ቦታ ምላሽ እየተጠበቀ እያለ የጠየቁት ቦታ ለሌሎች ሰዎች ተሰጥቷል።
ክፍለ ከተማው በብዙ ነገር ሲተባበርን ቆይቷል። አሁንም ቦታውን የሰጠበት የራሱ ምክንያት ይኖረዋል። ሰዎቹም መደገፍ ያለባቸው ይሆናሉ። ነገር ግን እነዚህን አዛውንትና ህጻናት በዘላቂነት ለመታደግ የተጀመረውም ስራ ትልቅ ትኩረት የሚሻ ነው። ለህንጻ ግንባታው ደግሞ በፕላን ዝግጅትም በግንባታም ሊተባበሩ ፈቃደኛ የሆኑ በጎ አድራጊዎችም የቦታውን መፈቀድ እየተጠባበቁ ይገኛሉ፡፡
ራስወርቅ ሙሉጌታ
አዲስ ዘመን መስከረም 14/2014