የሁለተኛው የአለም ጦርነት በተጀመረ በሶስተኛው አመት እ.ኤ.አ 1941 የአሜሪካ ፕሬዝዳንት የሆነው ፍራክሊን ሩዝቬልት እና የዩናይትድ ኪንግደሙ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዊንሰተን ቸርችል ጦርነት አላይድ ፓወርስ (Allied powers) በጦርነቱ ድል እንደሚቀናቸው በማሰብ በካናዳ ሚስጢራዊ ስብሰባ አካሄዱ:: ከሚስጢራዊ ስብሰባው በኋላም ከአላይድ ፖወርስ ሀገራት ራሽያን እና የመሳሰሉ ሃገራትን ጋብዘው አለም አቀፍ ድርጅት ለማቋቋም ተስማሙ::በዚህም አንድ አለማቀፋዊ ደርጅት ተፈጠረ :: ይህ ድርጅትም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መሆኑ ነው :: ይህ በሁለቱ ሃገራት ሚስጠር የተመሰረተ ድርጅት ገለልተኝነቱ እስከምን ድረስ ነው ? ብለን ከጠየቅን መልሱ ድርጅቱ ሲፈጠር ጀምሮ እስካሁን ድረስ የአሜሪካን እና የእንግሊዝን አስትንፋስ እየተከተለ የሚሰራ ድርጅት ስለመሆኑ ቅንጣንት ያህል የሚያጠራጥር አይደለም ::
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት መስረታ ትልቅ ድርሻ የነበራት አሜሪካ እና በተጋባዥነት የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን መስራች የሆነችው ራሽያ በፖሊቲካል ኢኮኖሚው ረገድ በአለም ላይ ጎልተው ለመውጣት እሸቅድምድም የጀመሩት በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት ነው :: እሽደቅድምድማቸውም በሁለቱ ሃገራት ዙሪያ የአለም ሃገራት እንዲሰለፉ አደረገ:: በሁለተኛው የአለም ጦርነት እና በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምስረታ አብረው የቆሙት አሜሪካ እና ራሽያ ሁለተኛ ላይስማሙ ፍችም ፈጸሙ ::
ከላይ ለመግለፅ እንደሞከርኩት የተባበሩት መግስታት ድርጅት የመመስረት ጥንስስ የተጠነሰው ፣ የተደፈደፈው እና ተብጥብጦ ለመጠጥ የበቃው የአሜሪካ እና የእንግሊዝ መሪዎች የጋራ ሚስጥራዊ ስብሰባ ካደረጉ በኃላ ነበር :: ከዚህ ጋር ተያይዞ ድርጅቱ በዋናነት አሁን ላይ የሁለቱ ሃጋራት በአለም ህዝብ ላይ ያላቸውን ፖለቲካ ፍላጎት መጫኛ እያደረጉ እየተጠቀሙበት መሆኑን እያየን ነው :: በነገራችን ላይ በድጅርቱ ውስጥ የሃገራት እኩልነት የሚባል ነገር የለም :: በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ ካሉ አባል ሃገራት ውስጥ ድምጽን በድምጽ የመሻር መብት ያላቸው አምስት ሃገርት ብቻ ናቸው :: ይህ በድርጅቱ ውስጥ ያሉ ሃገራትን ያበላለጠ ስለመሆኑ አንዱ ማሳያ ነው ::
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ ደግሞ ብዙ ክፍሎች መኖራቸው ይታወቃል :: አሜሪካ እና አጋሮቿ ይህን እነኝህን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ያሉ ክፍሎችን በመጠቀም የፈለጉትን ይጠቅማሉ ያልመሰላቸውን ደግሞ ከመሬት በታች በመክተት ይረግጡበታል:: ለምሳሌ በቅርቡ ግብፅን ለማስደሰት ሲባል በኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ዙሪያ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ታሪክ ልማት እንደ ስጋት ሆኖ በጸጥታው ምክር ቤት ዋና የመወያያ አጀንዳ ሆኖ ሲቀርብ ታይቷል ::
አሜሪካ እና ምዕራባዊን በመንግስታቱ ደርጅት ባሉ የተለያዩ ክፍሎችን በመጠቀም ና ለሰብአዊነት የቆሙ በማስመሰል የሃገራትን ሉዓላዊነት ይጥሳሉ፤ ሃሳባቸውንም የሚቃወሙ መሪዎችንም ያመክናሉ::ይህ ዕጣ ከደረሳቸው አፍሪካዊ መሪዎች መካከል ቶማስ ሳንካራ ፣ ሙሃመድ ጋዳፊ ፣ ፓትሪስ ሉሙምባ ፣ ክዋሜ ንኩሩማህ ተጠቃሽ ናቸው ::
ቶማስ ሳንካራ
የ20ኛው ክፍለ ዘመን የጸረ ኢፔሪሊያሊስት ታጋይ በመባል የሚታወቀው የፓን አፍሪካን ፊት አውራሪ ቶማስ ሳንካራ ታህሳስ፣ 1949 ዓ.ም በሰሜን አፐር ቮልታ ተወለደ :: ሳንካራ ሀገሩ ቡርኪና ፋሶ ከፈረንሳይ ቅኝ አገዛዝ ተላቃ ነፃነቷን ስታገኝ የ12 ዓመት ልጅ ነበር። የፓን አፍሪካ አብዮታዊ መሪ ሻምበል ቶማስ ሳንካራ በ1983 ዓ.ም በመፈንቅለ መንግሥት ስልጣን ከያዘ ከጥቂት ጊዜ በኋላ አፐር ቮልታ የሚለውን የሀገሩን መጠሪያ ቡርኪና ፋሶ ወይም “የቀና ሰዎች ሀገር” ሲል ቀየረ። መንግሥቱን ከቀድሞዋ ቅኝ ገዢ ፈረንሳይ በግልጽ በማራቅ ተራማጅ ያላቸውን ሶሻሊስት ፖሊሲዎችን አስተዋወቀ። ሳንካራ በስልጣን በቆየባቸው አራት ዓመታት፣ በተለይ ቅድሚያ የሰጠው አላግባብ የሚባክን የመንግሥት ወጪን በመቀነስ እና በጤናና በትምህርት ከቡርኪና ፋሶ ሕዝብ ብዙውን ክፍል የሚሸፍኑትን የገበሬዎችን ህይወት ማሻሻልን ነበር።
ነገር ግን አብዮታዊው መሪ ቶማስ ሳንካራ ለአህጉራዊ ችግር አህጉራዊ መፍትሄ ማስቀመጡና የአገሬን ችግር ለመፍታት የማንም ተላላኪ መሆን አያስፈልገኝም የሚል ጠንካራ አቋም በመያዙ የአፍሪካ ፖለቲካል ኢኮኖሚ እድገት ስጋት የሆነባቸው ምዕራባዊን በፍርሃት ቆፈን ውስጥ ገቡ :: ወጣቱን እና ተስፈኛውን መሪ ለመጣል አቀዱ :: የ20ኛው ክፍለ ዘመን የጸረ ኢፔሪሊያሊስቱን እና የፓን አፍሪካውን ፊት አውራሪ ቶማስ ሳንካራ በምዕራባዊን የተንኮል ጥርሶች ተነክሶ በሚያሳዝን እና ልብን በሚሰብር ሁኔታ እንዲገደል ተደረገ :: ረጅም ራእይ የነበረው ቶማስ ሳንካራም ለሀገሩና ለህዝቡ በማሰቡ በኢምፔሪያሊስት ኃይሎች በአጭሩ ተቀጨ::
ፓትሪስ ሉሙምባ እና የምዕራባዊያን ሴራ
የቤልጄም ቅኝ ተገዢ የሆነችው ኮንጎ እ.ኤ.አ በሰኔ 30 ቀን 1960 ነጻነቷን ተቀዳጀች:: በድል ማግስት የፓትሪስ ሉሙምባ ፓርቲም በሃገሪቱ የተካሄደውን ምርጫ አሸነፈ:: የኮንጎዎች አብሪ ኮከብ እና በኮንጎዎች ታሪክ ከልብ የማይጠፋው ፓትሪስ ሉሙምባ የመጀመሪያው ጠቅላይ ሚኒስቴር ለመሆን ቻለ :: ይህ በእንዲህ እንዳለ በቅኝ ግዛት ወቅት በኮንጎዎች ላይ ያደረሰችው እልቂት እና ሰቆቃ ከመጤን ያልቆጠረችው የፓትሪስ ሉሙባን አካሄድ ለመቃውም የቀደማት የለም:: “በችኮላ ለመሻሻል ብላችሁ የወደፊታችሁን አታበላሹ:: ደግሞም ይበልጥ መሥራት መቻላችሁን ርግጠኛ እስካልሆናችሁ ድረስ ቤልጅየም የሰጠቻችሁን መዋቅር አትለውጡት:: ወደኛ መምጣትን አትፍሩ፤ ከጎናችሁ እንሆናለን፤ ምክርም እንለግሳችኋለን::”
በዚህ የንጉሱ ንግግር ደሙ የፈላው ታጋይ ፓትሪስ ሉሙምባ የቤልጄሙን ንጉስ መርዝ የቋጠረ ንግግር በመቃወም “… ምንም እንኳ ዛሬ የኮንጎ ነጻነት ቀንን በእኩልነት ከተስተካከልናት ወዳጅ ሀገር ቤልጅየም ጋር አብረን ብናከብርም ማንኛውም የኮንጎ ዜጋ ለዚህ ድል የበቃው ለአመታት በጽናት ታግሎ በጦርነት ደሙን አፍሶ መሆኑን መቼም የሚረሳ አይደለም :: ትግሉን በምናደርግበት ወቅት በምግብ ዕጦትም ሆነ በእንግልት ተሸንፈን የተውነው ጦርነት አልነበረም:: በዚህም ነጻነታችንነ ማረጋገጥረ ችለናል :: ስለሆነም እጅጉን እንኮራለን :: ይህ የሚደነቅና ተገቢ ትግል በግዴታ ለተጫነብን አሳፋሪ ባርነት ማብቃት አስፈላጊም ነበር:: ” ሲል ተናገረ ::
ይህን የሰሙ የአሜሪካ እና የጥቅም ሸሪኮቿ በሉሙምባ ጠንካራ ንግግር ተደናገጡ :: ተናደዱም :: ምዕራባዊንም በበላይነት በሚያሽከረክሯቸው ጋዜጠኞችም የሉሙምባን ንግግር እንደሃጢያት በመቁጠር አስተጋቡት :: ቤልጄምም በቅኝ ግዛት ወቅት በኮንጎ ህዝብ ላይ ያደረገችው አረመኔአዊ ተግባር ይቅር በሉኝ ማለት ሲገባት ይባሱኑ ለኮንጎዊያን የነጻነት ፣ እኩልነት ፣ እድገት ፣ ተስፋ ብርሃን በፈነጠቀው መሪ ላይ ጥርሷን ነከሰች:: አሜሪካም በተሰወረ የክፋት ውጥን ፓትሪስ ሉሙምባን “ነብር አየኝ በል” አለችው ::
አሜሪካ እና ቤልጄም በሰውር በፈጠሩት ሸፍጥ እ.ኤ.አ በ1960 በኮንጎ የወታደሮች ዓመፅ ተቀሰቀሰ:: ከአመጹ በስተጀርባው የቤልጅየም እጅ እንዳለበት ከሉሙምባ አዕምሮ የተሰወረ አልነበረም:: የኮንጎ ቀውስ እየተባባሰ ሲመጣ ሉሙምባ የካታንጋና የደቡብ ካሳይ ተገንጣዮችን ለመቋቋም የሚያስችለውን ርዳታ ከአሜሪካና ከተባበሩት መንግሥታት ጠየቀ:: ሉሙምባ ኮንጎን አንድ ለማድረግ ብዙ ቢጥርም ሰሚ አላገኘም:: መልስ የተነፈገው ሉሙምባ ፊቱን ወደ ሶቭየት ኅብረት አዞረ:: ወቅቱ ቀዝቃዛው ጦርነት የተፋፋመበት ስለ ነበር አሜሪካ በዓይነ ቁራኛ ትከታተለው ጀመር::
ከበፊቱንም አሜሪካ የኮንጎን እንደ ነጻ ሀገር መመሥረት ያአልተዋጠላት ስለነበር በኮንጎ ምድር የቤልጅየም የበላይነት እንዲኖር አብዝታ ትስራ ነበር:: በዚህ ጊዜ ነው እንግዲህ አሜሪካ በቤልጅየም አጋዥነት የዩራንየምን ንጥረ ነገር ከኮንጎ ምድር ወደ ሀገሯ በማፍለስ አቶሚክ ቦንብ በገፍ ማበልጸግ የጀመረችው:: ስለዚህ የሉሙምባ ወደ ሥልጣን መምጣት አሜሪካ እንደ ልብ የምትፈነጭበትን የኮንጎ ማዕድናት ሊያሳጣት ሆነ:: በዚህ ላይ ደግሞ የሉሙምባና የሶቭየት ኅብረት ቅርርብ ለጤና አልመስላት አለ:: የአሜሪካ ውሳኔ አንድና አንድ ነበር :: የዝሆን ሞት ዋናው ምክንያት ጥርሱ ነው እንዲሉ አሜሪካም የኮንጎን ማዕድንን አንደፈለች ለማድረግ ፓትሪስ ሉሙምባን ለመግደል ወሰነች::
በተቀጣጠለው የኮንጎ አመፅ ሰበብ ቤልጅየም ‘የዜጎቼን ደኅንነት ያሳስበኛል ’ በማለት ስድስት ሺሕ የሚሆኑ ወታደሮቿን ወደ ኮንጎ “ካታንጋ” አስገባች:: ሉምባም የቤልጀምን ተንኮል ለአለም ህዝብ አሳወቀ :: ነገር ግን ከራሳቸው ጥቅም ውጭ ማንም ምንም ቢሆን የማያስጨንቃቸው አሜሪካ እና ጭራቸውን እየቆሉ የሚከተሏት አውሮፓዊያን ኮንጎ በቤልጅየም እጅ እየደማች እና ለመሞት እያጣጣረች እያዩ እናዳላዩ ሆኑ :: ዝምታንም መረጡ::ምዕራባዊን በሚያደርገጉት ጫና ምክንያት በኮንጎ የተቀሰቀሰው መታደራዊ አመፅ ተባባሰ :: ይህን ተከትሎ የኮንጎ ሰዎች በአውሮፓውያኑ ላይ ጥቃት መሰንዘር ጀመሩ::
የሉሙምባ አማሟት
በምዕራባዊያን የሚደገፈው ሞቡቱ ሴሴ ሴኮ የሚመራው የመፈንቅለ መንግሥት ሉሙምባ በመኖሪያ ቤቱ እንዳለ እንዲታፈን አደረገ:: ሉሙምባም ለሃገሬ በማለቱ በምራባዊያን ሴራ በመፈንቅለ መንግስት ተይዞ ታሰረ:: ሶቭየት ኅብረት ሉሙምባ እንዲፈታ ስትል ለተባበሩት መንግሥታት አሳወቀች:: የተባበሩት መንገስታት ደርጅትም የቤተሰብ ማህበር ስለሆነ የሉሙምባ እገታ ሰሚ ሳያገኝ ቀረ:: የሥልጣን ጥመኛው ሞቡቱ ሴሴ ሴኮ ግን “ሉሙምባ ለኮንጎ ሕዝብ ዕልቂት ጥፋተኛ ነው” በሚል ፈረጀው:: በዚያው በተያዘበት ቀን ምሽት ሉሙምባ ወደ ካታንጋ ሊረሸን ተወሰደ::እንደ እ.ኤ.አ በጃንዋሪ 17, 1961 ኮንጎን ወደፊት የማሻገር ህልሙን እንደያዘ በከፋት ጥርሶች ተበላ ::
ሉዶ ዴ ዊቴ የተባለው የሥነ ማኅበረሰብ ምሁሩ (The Assasination of Lumumba) በሚል ባሳተመው የምርምራ ፅሁፍ ሉሙምባ፣ በገዳይ ቡድኖች ወደ ካታንጋ ጫካዎች ተወስዶ መረሸኑን አመላክቷል:: የስና ማህበረሰብ ምሁሩ ጨምሮ እንዳመለካተውም ስለ ፓትሪስ ሉሙምባ ግድያ ምንጭና ፍንጭ እንዳይገኝ በሚል የገዳዩ ቡድን መሪ የሆነው ጌራልድ ሶቴ ከወንድሙ ጋር በመሆን የሉሙምባን አስክሬን ከተቀበረበት በማውጣት ሰውነቱን በሳላ መጋዝ በመቆራረጥ በሰልፈሪክ አሲድ እንዲሟሟ አደረጉት:: ገራልድ ሶቴ የገደላቸውን ሰዎች አካል በናሙናነት የማስቀረት ልማድ ስለነበረው ከሉሙምባ አካል ጥርሱንና ጣቱን መውሰዱን የአሟሟቱን ሚስጢር ተዳፍኖ እንዳይቀር አድርጓል::
በዚህ የግድያ ዕቅድ ውስጥ የአሜሪካ እጅ (ሲ.አይ.ኤ) እንዳለበት የሲ.አይ.ኤው ዳይሬክተር አለን ዱልስ“ሉሙምባ ሥልጣን ከጨበጠ የተመሰቃቀለ ነገር መምጣቱ የማይቀር ነው” በማለት የሉሙምባ መገደል አስፈላጊ መሆኑን ተናግሯል:: ኮንጎንም እስካሁን ድረስ ልትወጣው የማትችለው መቀመቅ ውስጥ በመክተት አሁን ላይ ከ27 አገራት በላይ በኮንጎ በሰላም አስከባሪነት ስም ገብተው የኮንንጎን ህዝብ ሃብት እየዘረፉ ይገኛሉ::
ሞአመር ጋዳፊ
ሌላው በአሜሪካ እና አጋሮቿ በክፋት ጠርስ ከተወገዱ አፍሪካዊን መሪዎች መከካል የሰሜን አፍሪካው አብዮተኛ ኮሎኔል ሞአመር ጋዳፊ በጉልህ ይጠቀሳል:: ስለጋዳፊ አፍሪካዊያን፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ የምዕራባዊያን ሴራ እያወቁም ሆነ ሳያውቁ አንደ አምባገነን መንግስት ይቆጥሯቸው ነበር :: ነገር ግን እውነት እና ውሃ እያደር ይጠራል እንዲሉ አሁን ላይ ምዕራባዊን በኢትዮጵያ ላይ እየፈጸሙት ያለውን ግፍ በጥሞና ለሚመለከት ሞአመር ጋደፊ ላይ የተደረገውን የምዕራባዊያን ሸፍጥ በጉልህ መመልከት ይቻላል::
ጋዳፊ ስልጣን እንደያዘ ሊቢያ ያላትን ነዳጅ ሃብት መጠቀም እንድትችል አደረገ:: ከነዳጅ የሚገኘውን ገቢም ለትምህርት ፣ለጤና ፣ ለማህበራዊ ወዘተ ጉዳዮች ላይ በማዋል በአጭር ጊዜ የሊቢያዊን ህይወት መለወጥ ቻለ:: የሊቢያዊን እድገት ደግሞ ብዙ የመርከብ እንቅስቃሴ እና ንግድ የሚበዛቀበትን የሜዲትሪያን ባህር ቀጠና ላይ ትልቅ ተፅኖ መፍጠር ቻለ:: የህ ደግሞ ምዕራባዊንን ክፉኛ ያሳሰባቸው ገባ :: በዚህም ምዕራባዊን ለአብዮተኛው የጥፋት ወጥመድ ዘረጉለት :: ለሊቢያ ህዝቦች ያሰቡ በመምስል አብዮተኛውን ኮሎኔል ጋዳፊ ምዕራባዊያን በሚቆጣጠሯቸው ሚዲያዎች በመጠቀም የአለማችን ቁጥር አንድ አምባገነን አድረገው ሳሉት :: በአለም ላይ ያሉ ሃገራትም አብዛኛዎቹ አንድም ስለጉዳዩ ሳይገባቸው ሁለትም ሆነ ብለው ምዕራባዊያንን ለመስደሰት ሲሉ በሚዲያዎቻቸው አብዮተኛውን መሪ ኮሎኔል ሞአመር ጋዳፊ የአለማችን ቁጥር አንድ አምባገነን በማስመሰል እና በመተባበር ኡኡኡ አሉ:: ሊቢያዊያንም በምዕራባዊን ተታለሉ:: ከድህነት ያወጣቸውን አብዮተኛ መሪያቸውን የአረብ የጸደይ አብዮት በተሰኘው አብዮት ሰልቅጠው በሉ::
አብዮተኛውን መሪ ለማጥፋት የመጡት አሜሪካ እና ወዳጆቿ የሊቢያ ህዝብን ከድህንት የወጣውን መሪ መግደላቸው ሳያነስ እና በግጭቱም ሊቢያዊን የነበራቸውን የነዳጅ ዘይት መዝረፋቸው አልበቃ ብሎ ይባሱኑ ሊቢያዊያንን እርስ በርስ በማባላት የጦር መሳሪያ ሸቀጦቻቸውን ማራገፊ በማድርግ ሊቢያን ወዳማትወጣው መቀምቅ ውስጥ ወረወሯት::ካለፈው በኋላም ቢሆን አሜሪካ በሊቢያ ላይ የፈጸመችው ድርጊት አግባብ እንዳልነበረ ባራክ ኦባማን ጨምሮ ሌሎች ባለስልጣናት መናዘዝ እየጀመሩ ነው::
ክዋሜ ንኩሩማህ
ሌላውን አፍሪካዊ መሪ ክዋሜ ንኩሩማህን እንመልከት:: በ1960ዎቹ መጀመሪያ ላይ በርካታ የአፍሪካ ሃገራት ነጻነታቸውን አገኙ :: ይሁን እንጂ ሃገራቱ በሁለት ጎራ ተከፋፈሉ:: አንደኛው ቡድን ‹‹የካዛብላንካ ቡድን›› ነበር:: የዚህ የቡድን አባላት በፖለቲካና በኢኮኖሚ የተዋሃደች የአፍሪካ ፌደሬሽንን የመመስረት ዓላማና የግራ ዘመም ፖለቲካ አቀንቃኝ በሆኑ መሪዎች የተዋቀረ ነበር:: በዚህ ጎራ የተሰለፉት አገራት ጋና፣ አልጄሪያ፣ ጊኒ ፣ ሞሮኮ ፣ ግብጽ ፣ ማሊ እና ሊቢያ ሲሆኑ የቡድኑ መሪም የወቅቱ የጋናው ፕሬዝደንት ክዋሜ ንክሩማህ ነበሩ:: ሁለተኛው ቡድን ደግሞ ‹‹የሞንሮቪያ ቡድን›› ነበር :: የዚህ ቡድን አባላትም የአፍሪካ አገራት በኢኮኖሚያዊና በሕዝብ ለሕዝብ ትስስሮች ተባብረው መዝለቅ ከቻሉ ፖለቲካዊ ውህደት በጊዜ ሂደት ሊደረስበት ይችላል ብሎ የሚያምን ነበር። በዚህ ጎራ የነበሩት አገራት ሴኔጋል ፣ ናይጄሪያ ፣ ላይቤሪያ ፣ ኢትዮጵያ እና አብዛኞቹ የፈረንሳይ ቀኝ ግዛት የነበሩ አገራት ሲሆኑ የቡድኑ መሪም የወቅቱ የሴኔጋል ፕሬዝደንት ገጣሚና ፈላስፋው ፖለቲከኛ ሊዮፖልድ ሴዳር ሴንጎር ነበሩ፡
እዚህ ላይ አንድ ነገር ልብ ሊባል ይገባል :: ይህም ክዋሜ ንኩሩማህ የሚመሩት የካዛብላንካ ቡድን የግራ ዘመም መሆኑን ነው :: ይህ ማለት ክዋሜ ንኩሩማህ የአሜሪካኖች ተቃራኒ ነበሩ ማለት ነው :: ከዚህ ባሻገር ለምን አሜሪካ በኩዋሜ ንኩርማህ ጥርሳቸውን ነከሰች ካልን ፕሬዝዳንቱ በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት ከሶቬት ህብረት ጋር መቆማ ነበር :: ከዚህ ጋር ተያይዞ በአሜሪካ የሚገኘው በFort Hays State University ; The United States and the overthrow of Kwame Nkrumah በሚል በተጠናው ጥናት ክዋሜ ንክሩማህ በቬትናም ሰላም ለማምጣት ተልኮ ወስደው ቬትናም እንዳሉ አሜሪካ በአቀነባበረችው ሴራ እ.ኤ.አ ፌብሩዋሪ 24, 1966 የመፍንቅለ መንግስት እንደተካሄደባቸው ተመላክቷል::
ኢትዮጰያኖችም አሁን ላይ ምዕራባዊያን የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን እና መሰል መንግስታዊ እና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተጠቅመው ከህወሓት ጋር የቆሙበት ዋናው ሚስጥር ኢትዮጵያን በማፈራረስ እና ራሳቸው 360 ዲግሪ የሚያሽከረክሩት መንግስት በመመስረት ኢትዮጰያኖችን ሊወጡት ወደ ማይችሉት መቀመቅ ሊያወርዱ በማሰብ መሆኑን በመረዳት ሁሉም ኢትዮጰያዊ ከምንግዜውም በላይ በመተባበር ሀገር ውስጥ የበቀለውን ትህነግ የተባለ የምዕራባዊን የጥፋት ጋሪ መሰባበር ያስፈልጋል:: ሰላም!!!
ሙሉቀን ታደገ
አዲስ ዘመን ነሐሴ 16 ቀን 2013 ዓ.ም